እሑድ 8 ኦገስት 2021

ሞት በጥር ነሐሴ መቃብር

 "ሞት በጥር ነሐሴ መቃብር"

በደረሰ ረታ


እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም አባቷ ኢያቄም እናቷ ሐና በመባል የሚጠሩ ሲሆን የተጸነሰችሁ እንዲሁ በሐጢያት ሳይሆን " ብዙ ተባዙ ምድርንም ምሉዋት" በተባለው አምላካዊ ሕግ እንጂ። ኦሪት ዘፍጥረት 1፥28

ኦ ድንግል አኮ በፍትወት ደነሰ ዘተፀነስኪ ድንግል ሆይ " ዘርዕ ዘይወፅእ እምስካበ ተአዳዌ ሕግ ይከውን ለቅጥቃጤ ወለሐሳር" ለሐሳር ለመከራ የተጸነስሽ አይደለሽም።

አላ በሩካቤ ዘበሕግ እምሐና ወኢያቄም ተወለድኪ፤ ከሐና ከኢያቄም ሕጋዊ በሆነ ሩካቤ ተወለድሽ እንጂ።

የእመቤታችን ቅድመ አያቶች (በጥሪቃ እና ቴክታ ) ባለጸጎች ነበሩ። ልጅ ግን አልነበራቸውም።

ሕልም አይተው እንደ ህልሙ መሰረት ቴክታ ጸነሰች፤ ሄእማንን ወለደች።

ሄኤሜን ዴርዴን፣ ዴርዴ ቶናህን፣ ቶናህ ሲካርን፣ ሲካር ሄርሜላን፣ ሄርሜላ ሐናን ወለደች።

ሐናም ለአቅመ ሔዋን ስትደርስ ነገዱ ከይሁዳ የሆነ ኢዩአቄምን አገባች። እርሷም እንደ አያቶቿ መካን ሆነች።

ሐና ልጅ ስላልነበራት እጅግ ታዝን ነበረ አንገቷንም ደፋች። ከዕለታት በአንደኛው ቀን ከቤተ እግዚአብሔር ሄዳ እጅ ነሳች። ስትመለስ ርግቦች ሲጫወቱ አይታ ፈጣሪዋን " ሁሉን ሁለት ሁለት አድርገህ ፈጥረሃል ሐና ባሪያህን ግን ድንጋይ አድርገህ ፈጥረሃታል። " በማለት አምርራ አለቀሰች።

ሐናና ኢያቄም ከቤተ እግዚአብሔር ሱባኤ ገብተው የሰው መሳቂያ መሳለቂያ እንዳይሆኑ ዕድሜ ዘመናቸውንም አንገታቸውን ደፍተውም እንዳይኖሩ ተማጸኑ፣ ወንድ ልጅ ቢወልዱ ለቤተ እግዚአብሔር አገልጋይ እንደሚሆን ሴት ልጅ ቢወልዱ መሶበ ወርቅ ሰፍታ፣ ሐር ፈትላ ትኖራለች ብለው ስለት ተሳሉ።

ወዲያው ነሐሴ ሰባት ሐና የዓለሙን መድኅን የወለደችውን ማርያምን ጸነሰች። እመቤታችንም ገና በእናቷ ማኅጸን ሳለች ብዙ ተአምራትን ታደርግ ጀመር። ይህን የሰሙ አይሁድ በምቀኝነት ተነሱባቸው። በድንጋይ ወግረው በእሳት ፈጅተው ሊገድሏቸው መከሩባቸው። የእግዚአብሔር መልአክም በማህጸን ካለችው የዓለም መድኃኒት እንደሚወለድ ያውቅ ነበረና ወደ ሊባኖስ ተራራ ሂዱ ብሏቸው በዚያ እያሉ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተወለደች።

የእመቤታችን መጸነስ እንደ እንግዳ ደራሽ እንደ ውሃ ፈሳሽ የነበረ ነገር ሳይሆን በአባቶች ትንቢት ሲነገር የኖረ ነበር። እመቤታችንም በተወለደች ዕለት ብርሃን ወርዷል፤ተድላ ደስታ ሆኗል።

የእመቤታችን አስተዳደግ ልቡናቸውን እንዳደነደኑ የዕብራውያን ሴቶች ልጆች እንዳደጉት በቧልት በጨዋታ በዋዛና በፈዛዛ አልነበረም። በንጽሕና በቅድስና ሆና በቤተመቅደስ አድጋለች እንጂ። ምድራዊ ኅብስትን፣ ምድራዊ መጠጥን ተመግባ ጠጥታ አይደለም። ሰማያዊ ኅብስትን ተመግባ ከሰማየ ሰማያት የተቀዳ ሰማያዊ መጠጥን ጠጥታ አደገች እንጂ።

በእናት በአባቷ ቤት ሶስት ዓመት ከኖረች በኋላ የስለት ልጅ ናትና ሦስት አመት ሲሆናት አፏ እህል ሳይለምድ ልቧ ሰው ሳይወድ በቃላቸው መሰረት ወስደው ቤተመቅደስ ለካህኑ ዘካሪያስ ሰጡት በቤተመቅደስ ትኖር ዘንድ ቤተመቅደስ አስገቧት፣ በቤተመቅደስ ቅዱስ ሩፋኤል ኅብስት ሰማያዊ ፅዋዕ ሰማያዊ እየመገባት አስራ ሁለት ዓመት ኖራለች።

ዕድሜዋ አስራ አምስት አመት ሆኗታልና ጎልማሳ ስለሆነች አይሁድ ካህኑ ዘካርያስ ከቤተመቅደስ እንዲያስወጣት ዘበዘቡት እርሱም ለእግዚአብሔር አመለከተ። የአከባቢው ሰው ይጠብቋት ዘንድ እጣ ቢያወጡ በዮሴፍ ወጣበት፣ እምቢ ቢል ርግብ በራሱ ላይ መጥታ አረፈችበት፣ ዕጣ ቢጣጣሉም ደግሞ በዮሴፍ ወጥቶበታል። ምስክርነት በሶስት ይጸናል እንዲሉ እመቤታችንን የመጠበቁ ነገር በዮሴፍ ጸናበት። ሕዝቡም " በዚህም ቢሉ በዚህ እመቤታችን ላንተ ደርሳለችና ግብር ገብተን እንደሰጠንህ ግብር ገብተን እስክንቀበልህ ድረስ ይዘሃት ሂድ" አሉት። ሳይወድ በግድ ይዟት ሄደ። ዮሴፍ እመቤታችንን ወደ ቤቱ ይዟት ከሄደ በኋላ ወደ ዓለም ኑሮ አልተመለሰም። በንጽሕና በቅድስና ሲጠብቃት ኖረ።

አዳም ከበደለ ጊዜ ጀምሮ በአብ ሕሊና ስትታሰብ ኖራለችና እግዚአብሔር አብ ንጽሕና ቅድስናሽን ባየ ጊዜ አብሳሪውን  ብርሃናዊ መልአክ ቅዱስ ገብርኤልን ወደርሷ ላከው እርሱም እንዲህ አላት። " መንፈስ ቅዱስ ይመጽእ ላእሌኪ፤ ወኃይለ ልዑል ይጼልለኪ፤ ውእቱሰ ንጹሕ እምነ ሠለስቱ ግብራት ዘወእቶሙ ዘርዕ ወሩካቤ ወሰስሎተ ድንግልና እለ ሥሩዓን በእጓለ መሕያው ወእሙራን ቦሙ። ..." መንፈስ ቅዱስ ያድርብሻል፤ ኃይለ ልዑል ወልድም ከሦስቱ ግብራት ይከለክልሻል። አካላዊ ቃል ከአባቱ እሪና ሳይለይ ካንቺ ተዋሐደ።ከምልአቱ ሳይወሰን ፀነስሽው። አካላዊ ቃል ካንቺ ከሥጋሽ ሥጋ ከነፍስሽ ነፍስ ነስቶ ሰው ሆነ።

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በዐርባ ዘጠነኛው ዓመተ ምሕረት በዘመነ ሉቃስ ጥር ሃያ አንድ ቀን በስልሳ አራት አመቷ ዐረፋለች።

ሐዋርያት አስከሬኗን ባጎበር አድርገው ወደ ጌቴሴማኒ ሊቀብሯት ይዘዋት ሲሄዱ አይሁድ ለምቀኝነት አያርፉምና አስክሬኗን በእሳት አቃጥለን እናጥፋት ብለው ተማከሩ።

ታውፋንያ የተባለው ኃይለኛ ሰው ፈጥኖ መጥቶ የአልጋውን ሸንኮር ያዘው መልአከ እግዚአብሔርም በረቂቅ ሰይፍ ሁለት እጆቹን ቆረጠው። ነገር ግን ቅዱስ ጴጥሮስ በጸሎቱ ሁለት እጁን ቀጥሎለታል።

ሐዋርያት በዚህ ተደናግጠው ቢበተኑ ወንጌላዊው ዮሐንስ ከመልአክ ጋር አስክሬኗን በገነት ዕፀ ሕይወት ሥር አስቀምጠዋታል።

ቅዱስ ዮሐንስ ተመልሶ መጥቶ ሐዋርያትን አይዟችሁ እመቤታችን በገነት በዕፀ ሕይወት ሥር ናት ብሎ አጽናናቸው።

ሐዋርያት ቶማስ ዐይቶ እኛ ሳናይ ልንቀር ነውን? ብለው በነሐሴ መባቻ በዕለተ ሰኞ ሱባዔ ገብተዋል። ሁለተኛውን ሱባዔ እንደጨረሱ በአሥራ አራተኛው ቀን መልዐኩ የእመቤታችንን አስክሬን ሰጥቷቸው ዕለቱን ቀብረዋታል።

በሶስተኛው ቀን ማክሰኞ ነሐሴ አሥራ ስድስት ቀን ተነሥታ ዕለቱን ዐርጋለች።

ቶማስ በወቅቱ አልነበረም፤ ከሀገረ ስብከቱ ከሕንድ(ሕንደኬ) በደመነ ተጭኖ ሲመጣ እመቤታችን ስታርግ አገኛት። ከደመናው ሊወድቅ ነበረ።

እጅግ አዝኖ እመቤቴ ሆይ ቀድሞ ጌታዬ ልጅሽ ከትንሣኤው ለየኝ አሁን ደግሞ አንቺም ልትለይኝ ነበረ አላት።

አይዞህ ዕርገቴን ያየህ አንተ ብቻ ነህ፤ ጓደኞችህ ሐዋርያት አላዩም ለእነርሱም የማረጌን ነገር አንተ ንገራቸው አለችው። እንዲያምኑህም ይኸው ሰበኔን እንካ አሳያቸው ብላ ሰደደችው።

ቶማስም ሐዋርያትን የእመቤታችን ነገር ጠየቃቸው፣ ቀበርናት አሉት፤ ሞት በጥር ነሐሴ መቃብር እንዴት ይሆና? አላቸው።

እነርሱም አጥበን ገንዘን የቀበርናትን እኛን ካላመንክ ማንን ልታምን ነው? ከዚህ ቀደምም የልጇን ማረግ አላምን ብለህ በመጠራጠርህ እና ካላየሁ አላምንም ብለህ እጅህን ከተወጋው ጎኑ ሰደህ እጅህ ተኮማተረ። አሁንስ ምን ፈልገህ ነው የምትጠራጠረው ብሎ ቅዱስ ጴጥሮስ ጠየቀ።

ጓደኞቹም እንዲያምን ከመቃብሩ ስፍራ ወስደው ጉድጓዱን ቆፍረው አስከሬኗን ሊያሳዩት ባሉ እንደ ልጇ ከመቃብር የለችም። ሐዋርያት ከመቃብር አስከሬኗን ቢያጡ ደነገጡ።

ቶማስም አታምኑኝም ብዬ እንጂ ስታርግ አግኝቻታለሉ ለባልንጀሮቹ የእመቤታችንን የማረግ ነገር ነገራቸው። እንዲያምኑትም ሰበኗን ሰጣቸው። እነርሱም ገንዘው የቀበሩትን ሰበኗን ቢያዩ አመኑ፤ ለበረከት ይሆናቸውም ዘንድ ሰበኗን ተካፍለው ድውይ ሲፈውሱበት፣ ሙት ሲያስነሱበት ኑረዋል።

ሞት በጥር ነሐሴ መቃብር።

ቶማስ ማረጓን ብቻውን አይቶ እኛ ሳናይ እንቀራለን ብለው በዓመቱ በነሐሴ አንድ ሱባኤ ገቡ። ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነሐሴ አስራ ስድስት እመቤታችንን መንበር፣ ቅዱስ ጴጥሮስን ተራዳኢ ካህን፣ እስጢፋኖስን ዲያቆን አድርጎ ቆርቦ አቁርቧቸዋል። እርሷንም አቆረባት።

እኛም በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የምንገኝ ክርስቲያኖች የሐዋርያትን ፈለግ ተከትለን ሱባኤ ገብተን ተገለጭልን እንላታለን። የበቁትን እየተገለጠች ታነጋግራቸዋለች። የኔ አይነቱን ሐጢያተኛ በበረከት እጆቿ ሕይወታችንን፣ ሥራችንን፣ ቤተሰባችንን፣ ወዘተ ትባርካለች።

ማርያም ማለት መርህ ለመንግሥተ ሰማይ ማለት ነው። ምእመናንን እየመራች ገነት መንግሥተ ሰማያት ታገባለችና።

አንድም ፍጽምት ማለት ነው። ለጊዜው መልክ ከደም ግባት አስተባብራ ይዛ ተገኝታለች። ፍጻሜው ግን ንጽሐ ልቡና አንድ አድርጋ ይዛ ተገኝታለችና።

አንድም ጸጋ ወሀብት ማለት ነው። ለጊዜው ለናት ለአባቷ ጸጋ ሀብት ሁና ተሰጥታለች። ፍጻሜው ግን ለሁላችን ተሰጥታለችና። አንድም ልዕልት ማለት ነው አርአያ ማለት ልዑል ማለት እንደሆነ። እመቤታችንንም መትሕተ ፈጣሪ መልዕልተ ፍጡራን ይላታልና። ተፈሥሒ ቤተ ይሁዳ ወተሐሠዪ ቤተ እስራኤል ተለአኪተ እግዚአብሔር ወሰብእ ማኅበረ መሃይምናን ወሕዝብ ማለት ነው።

አንድም ማሪሃም ማለት እግዝእትነ ብዙኃን ማለት ነው። አብርሃም ማለት አበ ብዙኃን ማለት እንደሆነ። ያንም በዕብራይስጥ እንጂ ይለዋል ብሎ ማርያም ማለት ቅሉ እግዝእተ ብዙኃን ማለት ነው።

ይቆየን።

አሜን








ማክሰኞ 25 ሜይ 2021

የጌታ ቃል ትዝ አለው

 " የጌታ ቃል ትዝ አለው " የሉቃስ ወንጌል 22፥61

በደረሰ ረታ

ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስን ክርስቶስን " ሌሎች ቢክዱህ እንኳን እኔ አልክድህም " ብሎት ነበረና ጌታም " ዶሮ ሳይጮህ ሶስት ጊዜ ትክደኛለህ " አለው።

ጊዜው ሲደርስ ጌታን ያዙት ወደ ሊቀካህናቱ ቤትም ወሰዱት

• ጴጥሮስም ርቆ ይከተለው ነበር።
• ጴጥሮስ በመካከላቸው ተቀመጠ።
• ይህ ደግሞ ከእርሱ ጋር ነበረ አለች።
• አንቺ ሴት፥ አላውቀውም ብሎ ካደ።
• አንተ ደግሞ ከእነርሱ ወገን ነህ፡ አለው።
• ጴጥሮስ ግን፡— አንተ ሰው፥ እኔ አይደለሁም፡ አለ።
• ሌላው አስረግጦ፡— እርሱ የገሊላ ሰው ነውና በእውነት ይህ ደግሞ ከእርሱ ጋር ነበረ፡ አለ።
• ጴጥሮስ ግን፡— አንተ ሰው፥ የምትለውን አላውቅም፡ አለ።
• ያን ጊዜም ገና ሲናገር ዶሮ ጮኸ።
• ጌታም ዘወር ብሎ ጴጥሮስን ተመለከተው፤
• ጴጥሮስም፡— ዛሬ ዶሮ ሳይጮኽ ሦስት ጊዜ ትክደኛለህ እንዳለው የጌታ ቃል ትዝ አለው።
• ጴጥሮስም ወደ ውጭ ወጥቶ ምርር ብሎ አለቀሰ።
የቅዱስ ጴጥሮስ አቋም ከችኩልነቱ የተነሳ ወላዋይ ይመስላል፤ ችኩልነቱ እና ባለማገናዘብ የሚመልሳቸው መልስ ከፍቅር የመነጨ ነው።

መጠራጠር እና ክህደቱ የተፈጠረው ግን በፍርሃት፣ ከነበረበት ስፍራ፣ ከወቅታዊ ሁኔታው የተነሳ ነበር።

1. ጌታን ሲይዙት ርቆት መከተሉ
2. ሲበርደው እሳት ለመሞቅ ጌታን ከያዙት ወገን ከመካከላቸው መቀመጡ
3. የጌታን ወደዚህ ዓለም የመምጣት ዓላማ በአግባቡ ሳይለይ የልብ መሻቱ
እነዚህ ተደማምረው ቅዱስ ጴጥሮስ መጀመሪያ ጌታን አላውቀው፣ ቀጥሎ ራሱን ክዶ አይደለሁም፣ በመጨረሻም ጌታን ሊክደው እና አላውቀውም እንዲል አድርጎታል።

ከዘረኛ ጋር ስንውል ዘረኛ፣ ከነፍሰ ገዳይ ጋር ስንውል ነፍሰ ገዳይ፣ ከመንፈሳዊ ጋር ስንውል መንፈሳዊ እንሆናለን። ወፍጮ ቤት የዋለ አይደለም የገባ ሰው ዱቄት ሳይነካው አይወጣምና።

" ቃሌ ከሚያልፍ ሰማይና ምድር ቢያልፍ ይቀላል " ያለ አምላካችን ያለው ቃል ተፈጸመ። ዶሮ ሳይጮኽ ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታን ሶስቴ ካደው።

ጌታም ዘወር ብሎ ጴጥሮስን ተመለከተው።

ጴጥሮስም የጌታ ቃል ትዝ አለው፦ ።" ዶሮ ሳይጮኽ ሶስት ጊዜ ትክደኛለህ "

ጴጥሮስም ወደ ውጪ ወጥቶ (ከወንበዴዎቹ ተለይቶ፣ ጌታን ሊገሉት ከሚፈልጉት አጠገብ ርቆ፣ እሳት ከሚሞቅበት ቦታ ተነስቶ ) ምርር ብሎ አለቀሰ።

የቅዱስ ጴጥሮስ መራር ለቅሶ የንሰሐ ለቅሶ ነበረ።

እኛስ?

ከቅዱስ ጴጥሮስ የሕይወት ተሞክሮ ምን ተማርን?

ጌታን በቅርበት ነው የምንከተለው ወይንስ በርቀት?

ውሎአችን ከነማን ጋር ነው?

አውቀን አምነን ነው እየተከተልነው ያለነው፣ በስሜት ነው፣ ከቤተሰቦቻችን ስለወረስን ነው፣ ወይንስ እንዴት ነው?

አሁናዊ ማንነታችን ምን ይመስላል?

ብዙዎቻችን የቅዱስ ጴጦሮስ አይነት ሕይወት ያለን ይመስለኛል፤ መመላለስ ነገር ግን መራር የንሰሐ ሕይወት የሌለን። እንደዛ ከሆነ እንመለስ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የሰማነው የጌታ ቃል ትዝ ይበለን።

አካሄዳችንን እናቅና ( ቤተክርስቲያን መሄድ የምንፈራ፣ ማስቀደስ የምንጠላ፣ መጾም የማንችል፣ የጸሎት ሕይወት የሌለን፣ ማመን የማይታይብን፣ ውሎና አዳራችን ከማይመስሉን ጋር የሆነ፣ ከማያምኑት ጋር ወዳጅነት የመሰረትን ) እንመለስ።

ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታውን እንዲክድ ያደረገው፦
መፍራቱ፣
ከማያምኑት ጋር መቀመጡ፣
ጽኑ እምነት አለመኖሩ፣
ወዘተ ናቸው ለመካድ እና መሪር እንባን እንዲያነባ ያደረጉት።

ስለዚህ እኛም ፍርሃትን የሚያርቅ ጽኑ ፍቅር እንዲኖረን ጌታን ቀርበን እንወቀው። ከማያምኑት ጋር ውሎአችንን አናድርግ፣ ( ከላም ጋር የዋለች ጊደር ምን ተምራ ትመጣለች እንዲባል) ውሎአችንን እናስተካክል።

አንዳንዶቻችን በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አዳኝነት፣ አምላክነት፣ አማላጅ አለመሆኑን፣ ማመናችንን፣ ክርስቲያን መሆናችንን ለመደበቅ እንጥራለን፣ የአንገት ማኅተማችንን እንደብቃለን፣ መጾማችንን ሳይቀር እንዋሻለን። ( የዘፈን ዳርዳሩ ... እንደሚባለው እንዳይሆን እፈራለሁ። )

በጌታ ቃል ራሳችንን እንመልከት። አንዳንዶቻችን ታሪክ ቀመስ እንሆናለን በልጅነቴ ሰንበት ተማሪ ነበርኩ፣ ዘማሪ ነበርኩ፣ ዲያቆን ነበርኩ፣ ቆራቢ ነበርኩ፣ መምህር/ አባ እገሌን አውቀዋለሁ፣ የቄስ ልጅ ነኝ ወዘተ እንላለን። አሁን የት ነን? እንደ ቅዱስ ጴጥሮስ ራሳችንን እንይ። እሳት ሐጢያትን እየሞቅን፣ ጌታን አሳልፈው ከሰጡ፣ ከሸጡ፣ ከገደሉ ጋር ነን? ወይስ ቃሉ ከሚነገርበት አትሮኑስ ስር ነን?

በጌታ ቃል ራሳችንን ካየነው ምንም ጥያቄ የለውም በድለናል። ( ሁሉ በደለ እንዲል የአምላካችን ቃል። ) ክደናል የሚያስብል ደረጃ ላይ ነን። እንደ ቅዱስ ጴጥሮስ ፈጥኖ የሚመለስ ልብ፣ የሚጸጸት ልብ፣ ወደ ንሰሐ የሚመለስ ልብ ካለን ንሰሐ እንግባ፣ አምርረን እናልቅስ፣ ያሳለፍነው ዘመን ይበቃናል እንበል።

የቀማን መልሰን፣ የበደልን ክሰን ወደ ንሰሐ ሕይወት እንገስግስ።

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምህረት ዐይኑ ይመልከተን።

አሜን።
ይቆየን።

መልካም የሕማማት ሳምንት ይሁንላችሁ።
❤❤######################❤❤

የእለት ተለት ጽሑፎቼን ለመከታተል ከዚህ በታች ባሉት ሁሉ እገኛለሁና ይከታተሉኝ። ከተመቸዎት ለሌሎች ያጋሩት።
My Facebook page link (በፌስቡክ ገጽ እንገናኝ)

https://www.facebook.com/deresse2020/

Main facebook account (ዋናው የፌስ ቡክ ገጼ ይቀላቀሉት)

https://www.facebook.com/DeresseReta

Follow me through telegeram (በቴሌግራም ሊከታተሉኝ ከፈቀዱ) ሁሉም ምልከታዬን የማጋራባቸው ማህበራዊ ድረ ገጾች ናቸው።

https://t.me/deressereta

ከአሥር አመት በላይ ከ50ሺ በላይ አንባቢዎች ያሉት መጦመሪያም አለ።

www.deressereta.blogspot.com

https://anchor.fm/deresse-reta/episodes/ep-ev5j5o

ሥራን አውቆ መሥራት

 ሥራን አውቆ መስራት


አንድ ሰው በቅርስ ጥበቃ ተቋም በጥበቃ አገልግሎት ተቀጥሮ እየሰራ ሳለ አንድ ቀን በቅርስ ማዕከሉ ውስጥ ሲንቀሳቀስ ብዙ ዘመናትን (1500ዓመታት) ያስቆጠረ ብርጭቆ ሰበረ።

ተቆጣጣሪው በጣም ተበሳጩ ተቆጡ ጥበቃው ምን እንደሚያበሳጫቸው ግራ በመጋባት ጠየቀ።

ኃላፊው እንዴ ብርጭቆኮ ነው የሰበርከው ብርጭቆው ደግሞ 1500 ዓመት ያስቆጠረ ትልቅ ቅርስ ነው አሉት።
ጥበቃውም ግራ ከመጋባት ውስጥ ወጥቶ ዘና በማለት እንደውም እንዲህ ያረጀ ብርጭቆ እዚህ ምን ይሰራል። እንደውም በአዲስ እተካዋለሁ አይጨነቁ በማለት ሊያረጋጋቸው ሞከረ።

ሰውየውም እጅግ ተበሳጩ። ቁጣቸው ጨመረ።

የሥራ ኃላፊውን ያስቆጣቸው ጥበቃውን ያረጋጋው ጉዳይ ምንድነው?

ጥበቃው ቅርስን ያህል ነገረ ሰብሮ እንዲህ ያረጋጋው ምን አይነት የጤና ሁኔታ ላይ ቢሆን ነው? ትሉ ይሆናል።

እስኪ ስለ እነዚህ ሁለት ሰወች በማውራት ጊዜ ከምናባክን ስለ እያንዳንዳችን እናስብ።

እኛ ምን አይነት ሰወች ነን?

ቁጡ?

ግዴለሽ?

ዝምተኛ?

እስኪ ምን ያስቆጣናል? ምንስ ዝም ያስብለናል? ግዴለሽ የሚያስደርገንስ ምንድን ነው?

ግድየለሽነት የጤናማነት ምልክት አይሆንም ሲወድቅም፣ ሲሰበርም፣ ሲጠፋም ግዴለሽ ከሆንን ጥቅሙ አልገባንም አልያም ችግር አለ።

አንዳንዶች ምናልባት ተስፋ ከመቁረጥ ግድየለሽ ሊሆኑ ይችላሉ። የፈለጉትን ከማጣት፣ በጣም የተማመኑበት ነገር ሲከዳቸው፣ ቃል ሲታጠፍባቸው፣ አምነው ሲከዱ ወዘተ ለግድየለሽነት ምንጭ ሊሆን ይችላል።

ምን ያስቆጣናል?

በተለምዶ እውነተኛ ሰው እውነቱን በምሬት ሲናገር ቁጡ ይባላል። ሌሎች ደግሞ " የሌባ አይነደረቅ መልሶ ልብ አድርቅ " እንዲሉ ጥፋታቸውን ለመደበቅ ይቆጣሉ። ጥቂቶች ደግሞ የግንባራቸው ሥጋ ቅርጽ (መሸብሸብ/ ኮስተር እንደ ማለት) ቁጡ ያስብላቸዋል።

እኔን መሰሎች ደግሞ ስራ ሲበላሽ እና ያለ አግባብ ሲሰራ በተለይ እንደ ቅርስ ጥበቃው ሰራተኛ ለደሞዝ ብቻ ገብተው በሚወጡ፤ ነገር ግን የሚሰሩት ሥራ ዓላማው ካልገባቸው ሥራቸውን በአግባቡ ካልተወጡት ያስቆጣል።

ዝምተኞችን ስንመለከት በአጭሩ ለመፈረጅ ቢያስቸግርም ሥራው ቢሰራ ባይሰራ፣ ቢበላሽ ባይበላሽ ምንም የማይመስላቸው "ያው በገሌ ነው" ብለው እንደ ድመት የሚያስቡ። ተናግሬ ሰው ከሚቀየመኝ ዝም ብዬ ተመሳስዬ አልኖርም ብለው የሚያስቡ ናቸው። እንደዚህ አይነት ለኔ ልዝብ ነው።

ለነገሩ ሁሉም ነገር ስለተናገሩት፣ ዝም ስላሉት አይፈታም አንዳንዴ ሲናገሩ የሚፈታ እንዳለ ሁሉ ዝም ሲሉት የሚፈታም አለና።

እኛ እንደ ተቋም እንደ አገር የተሰጠንን ሥራ የምንሰራው እንዴት ነው? እንደ ጥበቃው ሳይገባን ነው ወይስ እንደ ቅርስ ጥበቃ መስሪያ ቤት ኃላፊ በያገባኛል፣ በኔነት፣ ሥራው ገብቶን ነው?

ከትንሣኤ ማግስት

 የትንሣኤ ማግስት ቀናት

በደረሰ ረታ

ሰኞ ፦ ማዕዶት መሻገር ማለፍ በሲኦል ወደ ገነት በጨለማ ወደ ብርሃን የመሻገራችን ነፍሳት ከሲኦል የመውጣታቸው መታሰቢያ ነው። ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ የመምጣቱ አላማ ይኸው ነውና።

በባህሪው ሞት በመንግሥቱ ሽረት የሌለበት አምላክ የሞተው ለዚህ ነውና።

በዚህ በትንሣኤ ማግሥት ሰኞ በዚህ ዕለት በፋሲካችን በክርስቶስ ትንሣኤ ከድቅድቅ ጨለማ ወደ ሚደነቅ ብርሃን፣ ከሞት ወደ ሕይወት፣ ከሲኦል ወደ ገነት፣ ከሃሳር ወደ ክብር መሻገራችንን እናስባለን፡፡


ማግሰኞ፦ ማግስተ ሰኞ ቶማስ ሲባል ቶማስ ጌታን አይቶ ማመኑ ጌታዬ አምላኬ ብሎ መመሥከሩ

እንደምናውቀው ቶማስ በጌታችንም ሆነ በእመቤታችን ትንሣኤ ወቅት በአገልግሎት ምክንያት አልነበረም ወንድሞቹ ሐዋርያት ነበሩ ስለ ትንሣኤዋ የነገሩት ነገር ግን አላመነም። በጌታ ትንሣኤ ጌታን ቢጠራጠር እርሱ ስለመሆኑ ጌታ ማረጋገጫ የሰጠው ሲሰቀል የተወጋ ጎኑን እንዲያይ ነበረ። እጁን ወደ ተቸነከረበት ቢሰደው ጣቶቹ እሳት እንዳየ ጎማ ተኮማተሩበት። አምኖም መሰከረ። ዮሐ. 20፡27-29

በዚህ እለት ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ አለማመናችንን እንዲረዳ፣ አምነንም እንድንመሰክር እንዲረዳን እናስበዋለን።

ረቡዕ፦ አልአዛር ሲባል ጌታ አልአዛርን ከሞት እንዳስነሳው እናስባለን።

አልአዛርን ከሞት እንዳስነሳው ስናስብ ክርስቶስ የሞትን ስልጣን የሻረ የሕይወት ራስ፤ የመቃብርን ሥርዓት ያጠፋ ትንሣኤ፡ ድልም ያረገ ዘለአለማዊ ንጉሥ መሆኑን እንመሰክራለን፡፡

በዚህ ወቅት ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያውያን በብዙ ጭንቅና መከራ፣ በሞትና በሕይወት መካከል ስለምንገኝ፣ ኢትዮጵያዊ ማንነታችን እንደ ጉም በንኖ እየጠፋ ስለሆነ ጌታችን ለእኛም ትንሣኤ ልቡና እንዲያድለን እንለምነዋለን።


ሐሙስ፦ አዳም ሐሙስ ይባላል ለአዳም የሰጠው ተስፋና የተገባለት ኪዳን እንደተፈጸመ አዳምና ልጆቹ ነጻ እንደወጣን ይታሰብበታል።

በበለስ ምክንያት ከገነት እንደወጡ ሁሉ የአለም መድኀኒት ጌታችን ለአለመ ድህነት ከወጣንበት ገነት እንመለስ ዘንድ ከአምስት ቀን ተኩል በኋላ ለአዳም በገባው ቃል መሠረት አድኖናልና።

አርብ ፦ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ይባላል ቤተ ክርስቲያን በክርስቶስ ሞትና ትንሳኤ መመስረቷ ይሰበካል።

በዕለት አርብ ቤተክርስቲያን በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ስለመመስረቷ ይሰበካል፡፡ ክርስቶስ ስለ እርሱ ራሱን አሳልፎ ሰጥቶ ቤዛ ሆኖ በደሙ አንጽቶ በትንሣኤው ድል ሰጥቶ ቤተክርስቲያንን እንዳከበራት ይነገራል፡፡

ቤተክርስቲያን ስንል ሕንፃውን ሳይሆን አማኞችን ነው፤ ክርስቶስ ለሕንፃ አልሞተምና፡፡

ቅዳሜ፦ ቅዱሳት አንስት ሲባል የጌታን አካል ሽቱ ለመቀባት ጨለማ አቋርጠው ወደ መቃብር መምጣታቸው፣ ትንሳኤውን ቀድመው ማየታቸው ይሰበክባታል።

እሁድ፦ ዳግም ትንሳኤ ሲባል ለደቀ መዛሙርቱ ለ3ተኛ ጊዜ መገለጡንና ሰላምን መስበኩ ይሰበካል።

ማጠቃለያ

እንደ ክርስቲያን በአብይ ጾም ወቅት የምናሳየው መንፈሳዊ ማንነት ፍሬ የሚያፈራበት ነው። ከአብይ ጾም በኋላ ከትንሣኤው ማግሥት በቤተክርስቲያን ምሥጢር ብዙ መታሰቢያ ነገሮች አሉት አንዱ ሐምሳው ቀናት ከጾም የምንከለከልበትና አርብ እና ረቡዕ ሳይቀር የፍስክ ምግቦችን የምንመገብበት ነው።

ከዚህ በቀረው ከላይ የዘረዘርናቸው ምሥጢራትን ቤተክርስቲያን ለመጀመሪያው ሳምንት ስያሜ ሰጥታ አመሥጥራ ታስተምራለች።

እኔም ከብዙ በጥቂቱ፣ ከረጅም በአጭሩ፣ አምልቼ አስፍቼ ሳይሆን በማይም አቅሜ አቅርቤያለሁ።

እንደ ክርስትናችን የሁለት ወር መንፈሳዊ ተግባራችን የሚያፈራበት ነው። ጾም፣ ጸሎታችን፣ ስግደት፣ ምጽዋታችን፣ መውደቅ መነሳታችን ያበቃለት ሳይሆን በእምነት የዘራነው መንፈሳዊ ዘር አብቦ የሚያፈራበት ነው።

ነገር ግን አብዛኞቻችን መንፈሳዊነት ያለቀ ሥጋዊነት የተጀመረ እናስመስለዋለን። ፋሲካ ሲሆን ሥጋዊነት እንዲሰለጥንብን አይደለም።

ጾም እና ንሰሐ ገብቶ ቀኖና መቀበል ቢቀር ሌሎች ተግባራት አይቀሩም። ስለዚህ የትንሣኤ ማግሥት የልቡና ትንሣኤ እንዲሆንልን እመኛለሁ።

ይቆየን።
አሜን።

ሐሙስ 29 ኤፕሪል 2021

ጸሎተ ሐሙስ

 ምሴተ ሐሙስ / ጸሎተ ሐሙስ


" እኔ ለእናንተ እንዳደረግሁ እናንተ ደግሞ ታደርጉ ዘንድ ምሳሌ ሰጥቻችኋለሁና። "

የዮሐንስ ወንጌል 13፥1-15 ፣ ማቴዎስ 26፥1-
(በደረሰ ረታ)

በሕማማት ሳምንት በዕለተ ሐሙስ ጌታ ደቀመዛሙርቱን እግር ያጠበበት ነው፤ ሌሎቹ ፈቅደው ወደው ሲታጠቡ ቅዱስ ጴጥሮስ አታጥበኝም ብሎ አስቸግሮት ነበረ። ምሥጢሩን እና ምሳሌውን አላስተዋለም ነበረና።

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አስተምሮ መክሮ ገስጾ መልሶታል። እርሱም ለመመለስ ልቡ ቅርብ ነበረና እሺ በጄ ብሎ ታጥቧል።

ይህ ዕለት የትህትና ዕለት ነው። ጌታ እግራቸውን አጥቦ ሲጨርስ እኔ መምህር ስሆን ዝቅ ብዬ የተማሪዎቼን / የደቀመዛሙርቴን እግር ካጠብኩ እናንተም እንዲሁ አድርጉ ብሎ አስተማራቸው።

ቅዱስ ያሬድም ስለዚች ዕለት ይለናል፦

“ሐዋርያቲሁ ከበበ
እግረ አርዳኢሁ ሐጸበ
ኮኖሙ አበ ወእመ
ወመሀሮሙ ጥበበ”

ሲተረጎም፦ ሐዋርያቱን ሰበሰበ፤ የደቀ መዛሙርቱንም እግር አጠበ፤ እንደ አባትና እናት ኾናቸው የትሕትና ጥበብን አስተማራቸው። ማለት ነው።

ከዚህ ዕለት ብዙ የምንማረው ነገር ቢኖርም አንዱና ዋነኛው የጌታን ትሕትና ነው። ጌታ ሲሆን እግር አጠበ። በተግባር ያሳየ የትህትና መምህር ነው።

ቅድስት የሆነች ኦርቶዶክሳዊት ተዋህዶ ቤተክርስቲያናችን በየአመቱ ይህን ምሥጢር በጸሎተ ሐሙስ ታከናውናለች። ከቅዱስ ፓትሪያርኩ ጀምሮ ዐዕይንተ እግዚአብሔር ካህናት በእርሱ ምሳሌ የምዕመኑን እግር ወገባቸውን ታጥቀው ዝቅ ብለው ያጥባሉ። ምሳሌ ነው።

መምህረ ትህትና ኢየሱስ ክርስቶስን ቅዱስ ጴጥሮስ እግሩን አልታጠብም ብሎ እንዳስቸገረ እንዲሁ መምህራንን ቅድስ ቤተክርስቲያንን አስተምሮቷን አንቀበልም የሚሉ ለሥርአቷ የማይገዙ ደንዳና ልብ ያላቸው አሉ። እንደ ቅዱስ ጴጥሮስ ያሉ ትምህርት ሲያገኙ የሚመለሱ አሉ። እነዚህን አስተምራ ትመልሳለች እንደ ይሁዳ ያሉትን ልበ ደንዳኖች አውግዛ ትለያለች።

እኛም አስተምህሮቷ ገብቶን እና የምሥጢሩ በረከት ተገብቶ ይድረሰን።

የሰው ልጅ ክቡር እና እኩል ቢሆንም ቅሉ። ካለንበት እንዳለንበት ደረጃ በትህትና ዝቅ ብለን ልንታዘዝ፣ ልናገለግል ይገባናል።

ትሕትና የመንግሥተ ሰማያት መወጣጫ መሠላል ናትና ትሕትናን ገንዘብ እናድርግ። እርፍ የጨበጠ መሰላል ላይ የወጣ ከመጨረሻው እስኪደርስ ድረስ ወደኋላ አይልምና ዘወትር ትሕትና አይለየን።

ይሕ ቀን ሌላ ተግባር ተከናውኖበታል። በአልአዛር እና ኒቆዲሞስ ቤት ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ለደቀመዛሙርቱ ይህ ነገ የሚፈሰው ደሜ፣ የሚቆረሰው ሥጋዬ ነው ጠጡ ፥ብሎ ሰጣቸው። ምሥጢረ ቁርባንን የጀመረበት ዕለትም ነው። የአዲስ ኪዳን ተግባር የተጀመረበት ዕለት ነው።

ሥጋውን ደሙን ከመቀበላቸው አስቀድሞ በእግራቸው በኩል ሕሊናቸውን፣ ሰውነታቸውን፣ ነፍሳቸውን አጽድቶ አጥቦ ለቁርባን አቀረባቸው።

እኛም ርስት መንግሥተ ሰማያትን የሚያወርሰውን ሥጋውንና ደሙን እንድመገብ ንሰሐ ገብተን ጸድተን እና ነጽተን እንቀረብ፤ ለዚህም እግዚአብሔር ይርዳን።

አምላካችን ዐይን ያላየውን፣ ጆሮ ያልሰማውን፣ በሰው ልቡና ያልታሰበውን፣ እግዚአብሔር ለሚወዳቸው ያዘጋጀውን ርስት መንግስተ ሰማያትን ያውርሰን።

ይቆየን።
አሜን።

ሰኞ 26 ኤፕሪል 2021

ሰሙነ ሕማማት ሰኞ ( መርገመ በለስ)

 ሰሙነ ሕማማት ሰኞ ( መርገመ በለስ)

ማቴዎስ 21 : 10 - 19

ከእለተ ሆሳእና ማግስት ኢየሱስ ክርስቶስ ተራበ ይለናል። ፍጹም ሰው መሆኑን ለማጠየቅ ተራበ ተብሎ ተጻፈ። ስለተራበም ረሃቡን ማስታገሻ ምግብ ፈለገ። አንዲት በለስ ተመልክቶ ወደርሷ አመራ። ከቅጠልም ብቻ በቀር ምንም አላገኘባትምና " ለዘለዓለሙ ፍሬ አይገኝብሽ አላት " በሌሊትም ያንን ጊዜውን ደረቀች።

ወንጌላዊው ማቴዎስ በሰሙነ ሕማማት ሰኞ ስለተፈጸመው ተግባር ሲጽፍ ጌታ የረገማት በለስ ወዲያው እንደ ደረቀች የጌታ ደቀመዛሙርትም ይህን አይተው እንደተደነቁ ይነግረናል።

በሌሊቱ የተረገመችው በለመለመችና ፍሬ በምታፈራበት ወቅት ነበረ። ይህን ሲያስረግጥልን ቅዱስ ማርቆስ በምዕራፍ 11 ቁጥር 13 ላይ " የበለስ ወራት አልነበረምና " ይለዋል።

ታዲያ ቅዱስ ማርቆስ የበለስ ወራት እንዳልሆነ ካረጋገጠልን ጌታ ስለምን ከበለሲቱ ፍሬ ፈለገ? የሚል ጥያቄ ያስነሳል።

አባቶቻችን እንዲህ ብለው ይኸን ጥያቄ ይመልሱታል። ከበለሷ ፍሬ መፈለጉ፥
• አንዳንድ በኩረ በለስ አይታጣም ብሎ ነው ይላሉ፣
• አንድም አላዋቂ ሥጋን እንደ ተዋሃደ ለማጠየቅ ነው ይሉናል፣
• አንድም አውቃለሁ ብሎ ሥራውን አይተውምና በዚያው ሥራውን ለመሥራት ነው።
ቅዱስ ማቴዎስ እና ቅዱስ ማርቆስ የጻፉለት በለስ ምሳሌ አላት። በበለስ የተመሰለው:-
፩. እስራል ናት

በበለሷ በረሃብ ሰአት የሚባላ መልካም ፍሬ ሊያገኝባት በወደደ እና በፈቀደ ጊዜ እንዳላገኘባት ሁሉ በእስራኤልም እንዲሁ ሃይማኖት፣ ምግባር ባገኝባቸው ብሎ ሄደ። አንዳች አላገኘባቸውም እስራኤል ከመባል በቀር። ደግ ሰው አይገኝብሽ ብሎ ረገማት። ያን ጊዜ ደግ ሰው ጠፋ።
" አቤቱ አድነኝ ደግ ሰው ጠፍቷልና " እንዲል ልበ አምላክ ንጉስ ዳዊት።

በለሷ እንደ ደረቀች እስራኤልም የተሰጣቸው የመመለሻ 40 ዘመን ሲያልቅ ምድረ እስራኤል ጠፋች።

፪. ህገ ኦሪት ናት

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ እስራኤል ሰው ፣ ምግባር ፣ ሃይማኖት ፣ በጎነት ፣ፍለጋ እንደ ሄደ ነገር ግን የሚገድል እንጂ የሚያድን ህግ ሆኖ አላገኘውም።

ህገ ኦሪት ሰውን አልጠቀመምና ህገ ኦሪትን አሳለፈው። ሻረው።

ቅዱስ ጳውሎስ ወደ ሮሜ ሰወች በላከው መልዕክቱ ምዕራፍ 8፥2 ላይ " በክርስቶስ ኢየሱስ ያለው የሕይወት መንፈስ ሕግ ከኃጢአት ከሞት ሕግ አርነት አውጥቶኛልና። " እንዲል ሕገ ኦሪት የሞት ሕግ ነበረ ማለት ነው።

ኦሪት ሕግና ሥርአት ነበራት የማይጠብቋትን መቀጣጫ ናት።

፫ . ኃጢአት ናት

ኃጢአት እንደ በለስ ቅጠል ሰፍታ በዚህ ዓለም ሞልታ አግኝቷታልና ረገማት። ኃጢአት በሶስት ነገር በበለስ ተመስላለች።
1. አዳምን ከገነት ያህል ቦታ እንዲወጣ እግዚአብሔርን ከመሰለ ጌታ የለየችው ዕፀበለስ ናትና።
2. የበለስ ቅጠል ሰፊ እንደመሆኑ መጠን የኃጢአትም መንገድ ሊጓዙበት የሚያመች ሰፊ መሆኑን ሲያጠይቅ።
3. በለስ ሲበሉት እንደሚጣፍጥ ሲቆይ እንዲመር ኃጢአትም ሲሰሩት ለሥጋ ደስታን የሚሰጥ ፣ ስሜትን የሚያረካ ነገር ግን ፍፃሜው ሞት እና መከራ ያለበት ህይወት ነው።
ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ክብር ይግባውና ስለ ናትናኤል ሲናገር " ፊሊጶስ ሳይጠራህ ከበለስ በታች ሳለህ አየሁህ አለው " ዮሐንስ 1፥49

በለስ የኃጢአት ምሳሌ ነውና ኃጢአት ሰርተህ በበለስ ስር በተሸሸግህ ጊዜ አውቅሃለሁ ማለቱ ነበር። በአንድ ወቅት ናትናኤል የሰው ሕይወት አጥፍቶ በበለስጨስር ቀብሮ ነበረና።

በለስን መርገሙ ኃጢአትን መርገሙ ነው። መርገሙ ከዚህ በኋላ በሃጢአት አንዳች ሰው አይያዝ ማለቱ ነው።

ለዚህም ነው አባቶቻችን በቀመራቸው የሕማማትን ሰኞ መርገመ በለስ ብለው መሰየማቸው።

ምድራችን የሰው ልጅ ከኃጢአት ርቆ ከእግዚአብሔር ተጣብቆ የሚኖርባት ትሆንልን ዘንድ የእግዚአብሔር አምላካችን ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን።

ይቆየን።
አሜን።


የእለት ተለት ጽሑፎቼን ለመከታተል ከዚህ በታች ባሉት ሁሉ እገኛለሁና ይከታተሉኝ። ከተመቸዎት ለሌሎች ያጋሩት።
My Facebook page link (በፌስቡክ ገጽ እንገናኝ)

https://www.facebook.com/deresse2020/

Main facebook account (ዋናው የፌስ ቡክ ገጼ ይቀላቀሉት)

https://www.facebook.com/DeresseReta

Follow me through telegeram (በቴሌግራም ሊከታተሉኝ ከፈቀዱ) ሁሉም ምልከታዬን የማጋራባቸው ማህበራዊ ድረ ገጾች ናቸው።

https://t.me/deressereta

ከአሥር አመት በላይ ከ50ሺ በላይ አንባቢዎች ያሉት መጦመሪያም አለ።

www.deressereta.blogspot.com

https://anchor.fm/deresse-reta/episodes/ep-ev5j5o

ረቡዕ 21 ኤፕሪል 2021

አቤቱ የሆነብንን አስብ

 "አቤቱ የሆነብንን አስብ" ሰቆቃው ኤርሚያስ 5 : 1


ኢትዮጵያ እንደ አገር ሕዝቦቿም እንደ ሕዝብ በአራቱም አቅጣጫ ያልሆነባት ነገር የለም። ሕዝቦቿ አንዱን መከራ ተሻገርን ሲሉ ሌላ መከራ ይደቀንባቸዋል።

የተፈጥሮ ሲባል ፣ ሰው ሰራሽ ፣ ሰው ሰራሹን አለፍን ሲሉ ሌላ ይደቀናል።


ወደ መንግስት ጮኽን ወደ አንተ አንጋጠጥን መልስ አላገኘንም። አቤቱ እባክህ ቸሩ ሩህሩህ ይቅር ባይ አምላካችን ሆይ የሆነብንን አስብ።


• ሴት ልጅ እስከ ጽንሷ ተገድላ ከሜዳ ላይ ተጥላለች፣

• ህጻናት ያለወላጅ ቀርተዋል፣

• አባት በሚስቱ እና በልጆቹ ፊት ተገድሏል፣

• ልጃገረዶች ተደፍረዋል፣

• ወጣቶች ተሰደዋል ተገድለዋል፣

• የሰው ልጅ እንደ እንስሳ ተቆጥሯል፣

• አሟሟታችን ከእንስሳት አንሷል፣

• ተገድለን ቁልቁል እየተሰቀልን፣

• ሞተን መቀበር ቅንጦት ሆኗል፤ አቤቱ የሆነብንን አስብ።

• በአሕዛብ ፊት መሰደቢያ ሆነናል፣

• የመገናኛችን ቤተመቅስ ተቃጥሏል አጥር ቅጥርህ ተደፍሯል፣

• አምላኬ ሆይ፥ በፊትህ የምንለምን ስለ ብዙ ምሕረትህ ነው እንጂ ስለ ጽድቃችን አይደለምና ጆሮህን አዘንብለህ ስማ፤ ዓይንህን ገልጠህ ጥፋታችንና ስምህ የተጠራባትን ከተማ ተመልከት። አቤቱ፥ ስማ፤ አቤቱ፥ ይቅር በል፤ አቤቱ፥ አድምጥና አድርግ፤ አምላኬ ሆይ፥ ስምህ በከተማህና በሕዝብህ ላይ ተጠርቶአልና ስለ ራስህ አትዘግይ።" ትንቢተ ዳንኤል 9 : 16 - 19

እስላም ክርስቲያኑ በአንድነት ጸሎት አውጆ ከፊትህ ተንበርክኳል ወደ አንተ ይጮዃል ያነባል። አቤቱ የሆነብንን አስብ።


ረሐብ ቸነፈር በሽታ አንበጣ ጦርነት ስድት በዚህ ያልጠና ሰውነት እንዴት ይቻለናል?


ስለህጻናቱ ስትል ማረን፣ ጤዛ ልሰው ድንጋይ ተንተርሰው ስለሚማልዱት ብለህ ማረን፣ በጾም በጸሎት በፊትህ በአንድነት ስለወደቁት ብለህ ማረን፣ ይልቁንም ከሴቶች ሁሉ ስለተለየችው ጸጋን ስለተሞላችው ቅድስት ድንግል ማርያም ስትል ማረን፣ ስለአለሙ ሁሉ ስትል በቀራንዮ አደባባይ ስለቆረስከው ስጋህ ስላፈሰስከው ደምህ ብለህ ማረን ይቅርም በለን።


የሰው ልጅ ወደ ልቡ ይመለስ ዘንድ በዘር ከመከፋፈል ይልቅ ከአንድ አዳም መፈጠሩን ያስብ ዘንድ ሁሉም አንድ መሆኑን የቋንቋው እንደ የቀለሙ መለየት ልዩነት እንዳያደርግ በዚህም ተከፋፍሎ እንዳይተላለቅ እባክህ ፍቀድ።


በሽታውን አስታግስልን፣

ለነፍሰ ገዳዮች ልብ ስጥልን፣

የተጨነቁትን ልባቸው የተሰበረውን አካላቸው የጎደለውን አጽናናልን፣ ነፍስ ከሥጋቸው በክፉዎች ያለፉትን ማረፊያ በአንተ ዘንድ አዘጋጅላቸው፣ ለወዳጅ ዘመዶቻቸው ፍጹም መጽናናትን አድልልን።


አቤቱ የሆነብንን አስብ።


ቤተመቅደስ ሲቃጠል ግድ ይበልህ።


እኛ ቤተመቅደሶችህ ስንገደል ግድ ይበልህ።


በስም የተጠራን ልጆችህ እረኛው እንደተመታ መንጋ ስንበተን፣ ስንሳደድ ግድ ይበልህ።


እንባችን በላያችን ደርቋልና በግፍና በበደል ደማችን በከንቱ ፈሷልና የምህረት ዐይንህ ወደኛ ይመልከት።


አቤቱ ሆይ ፥የሆነብንን አስብ።


አሜን።

ይቆየን።


የእለት ተለት ጽሑፎቼን ለመከታተል ከዚህ በታች ባሉት ሁሉ እገኛለሁና ይከታተሉኝ። ከተመቸዎት ለሌሎች ያጋሩት።

My Facebook page link (በፌስቡክ ገጽ እንገናኝ)


https://www.facebook.com/deresse2020/


Main facebook account (ዋናው የፌስ ቡክ ገጼ ይቀላቀሉት)


https://www.facebook.com/DeresseReta


Follow me through telegeram (በቴሌግራም ሊከታተሉኝ ከፈቀዱ) ሁሉም ምልከታዬን የማጋራባቸው ማህበራዊ ድረ ገጾች ናቸው።


https://t.me/deressereta


ከአሥር አመት በላይ ከ50ሺ በላይ አንባቢዎች ያሉት መጦመሪያም አለ።


www.deressereta.blogspot.com 


https://anchor.fm/deresse-reta/episodes/ep-ev5j5o

ሰኞ 19 ኤፕሪል 2021

መንፈስ ወደ ምድረበዳ ወሰደው

 መንፈስ ወደ ምድረበዳ ወሰደው


ልበ አምላክ ዳዊት "ወደ ቤተ እግዚአብሔር እንሂድ ባሉኝ ጊዜ ደስ አለኝ" ይለናል።
ንጉስ ስለሆነ ወደ ወንዝ ዳርቻ፣ ከአለም ጥግ ሌላው ጥግ ድረስ፣ አሉ በተባሉ መዝናዎች፣ ትላልቅ አለም አቀፍ ክንውኖች ዘንድ፣ ከቤተመንግሥቱ ሕንጻ አናት ላይ ሆኖ አየር መቀበል እና ከተማውን መቃኘት፣ የቤተመንግሥቱን ጊቢ አየር መቀበል ይችል ነበረ። ደስታን ከሚፈጥሩ ክንውኖች መካከል እነዚህ ተጠቃሾች ስለሆነ።

በጌታ ደስ ይበላችሁ እንዲል ንጉስ ዳዊትን ምድራዊው ነገር አላስደሰተውም። ይልቁንም ወደ እግዚአብሔር ቤት መሄድ እንጂ የፈለገው።

መንፈሳዊነት የሚገለጥበት ሰው ከሚያዝናናው ነገር ይልቅ ነፍሱን ወደሚያጸድቀው ነገር ያደላልና።

ቅዱሳንን መንፈስ ቅዱስ ወደ ገዳም ይመራቸው ነበረ።
መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን መንፈስ ወደ ምድረበዳ ወሰደው ይለናል። መንፈስ ቅዱስ ያላለው መንፈስ ቅዱስ ለአብና ለወልድ ሕይወታቸው ስለሆነ ነው አንድም የራሱ ፈቃድ ስላነሳሳው ነው።

ምድረበዳ አለ፤ ገዳም ለማለት ነው።

ወደ ገዳም ስንሄድ ከፈቃደ እግዚአብሔር ውጭ አይቻልም። ሰው ያስባል እግዚአብሔር ይፈጽማልና መንፈስ ቅዱስ ያነሳሳናል። ለመንፈስ ቅዱስ ማደሪያነት የተመቸ ሰውነት ሲኖረን።

ወደ ገዳም የመሄድ ዝንባሌ ያለው ሰው መንፈስ ቅዱስ የሚያነሳሳው ሰው ነው።

ላይሞላ ነገር የዓለም ፈቃድ ወደኋላ ይስበናል። በዚህ ቀን ደፋ ቀና ከምንለው፣ ከምንሄድበት መርሃግብር ሁሉ የሚበልጥ ለቤታችንም፣ ለሕይወታችንም፣ ለቤተሰባችንም የሚሆን የነፍስ ገበያ ገብይተን የምንመለስበት ሥፍራ ገዳም ነው።

መንፈስ ቅዱስ አነሳስቶ እየመራ እግራችንን ወደ ገዳም ይውሰደን። ወደ ቤተ እግዚአብሔር እንሂድ ስንባል ከምክንያታችን በላይ ነፍሳችንን የሚያስደስት ነገር ያድርግልን።

ይቆየን
አሜን።

አምላክ ከእናንተ ጋር ይሆናል

 " አምላክ ከእናንተ ጋር ይሆናል "


" በቀረውስ፥ ወንድሞች ሆይ፥ ደኅና ሁኑ። ፍጹማን ሁኑ፥ ምክሬን ስሙ፥ በአንድ ልብ ሁኑ፥ በሰላም ኑሩ፥ የፍቅርና የሰላምም አምላክ ከእናንተ ጋር ይሆናል።"
2ኛ ቆሮንቶስ 13 : 11

ለሶስተኛ ጊዜ ቅዱስ ጳውሎስ ወደ ቆሮንቶስ ሰወች በሄደ ጊዜ በመጨረሻው ምእራፍ ላይ ያስቀመጠላቸው መልእክት ነው።

ደህና ሁኑ የሚለው ቃል ሁላችንም እንደምንረዳው የስንበት የመለያየት የመጨረሻ ቃል ነው። ቅዱስ ጳውሎስ በመግቢያው እንደተናገረው " ነገር በሶስት ይጸናልና " እንዳለው ትምህርቱ በልባቸው እንዲጸና ለሶስት ጊዜ ተመላልሶ አስተምሯቸዋል።

በመቀጠልም " ፍጹማን ሁኑ " አላቸው። የሰው ልጅ በመንፈሳዊ ህይወት ሲኖር የሚደርስበት የፍጹምነት ደረጃዎች አሉና እነርሱን ለማስመዝገብ ዝም ብላችሁ ቃሉን የምትሰሙ ነገር ግን የማትተገብሩት ሳትሆኑ በሕይወት የምትኖሩ ሁኑ ሲላቸው ነው።

አንድም በቃሉ የምትሰናከሉ ሳትሆኑ ለሌሎች ምሳሌ የምትሆኑ ሁኑ ሲላቸው ነው።

አንድም እንዲሁ በከንቱ ያለምንም ዋጋ ላይ ታች የምትሉ ሳትሆኑ 30፣ 60፣ 100 ያማረ ፍሬ አፍርታችሁ የዘላለም መንግሥትን ገነትን ውረሱ ሲላቸው ፍጹማን ሁኑ አላቸው።

በመጨረሻም ሲያስተምራቸው ሲመክራቸው እንደመክረሙ ሁሉ ማሳረጊያ " ምክሬን ስሙ፥ በአንድ ልብ ሁኑ፥ በሰላም ኑሩ፥ የፍቅርና የሰላምም አምላክ ከእናንተ ጋር ይሆናል " አላቸው።

ምክሩም እንዲህ የሚል ነው " በአንድ ልብ ሁኑ፥። በሰላም ኑሩ " ወንድሞች በአንድ ልብ እና በሰላም ሲኖሩ መልካም ነውና። ፍጻሜውም ያማረ ነውና። ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ወንድሞች አስረግጦ እንደተናገረው የፍቅርና የሰላምም አምላክ ከእኛ ጋር ይሆናል።

ዓለም ለምንድን ነው ከጫፍ ጫፍ ፍቅርና ሰላም ያጣችው?

ለምንስ የዓለማችን ሃያላን አገራት መሪዎች ሰላምን ለማምጣት ያልተቻላቸው?

ለምንስ ነው የየእምነት ተቋማት መሪዎች ፍቅርና ሰላም በምድር ላይ እንዲሰፍን ማድረግ የተሳናቸው?

ለምንስ ነው አባወራዎች የቤቱ እራስ እንደመሆናቸው ፍቅርና ሰላምን በቤታቸው ጣሪያ ስር ማምጣት ያልቻሉት?

ወንድም እህቶቼ የቅዱስ ጳውሎስን ምክር ካለመስማታችን የተነሳ አይመስላችሁም። እኔ በበኩሌ ያለምንም ማመንታትና ጥርጥር ምክንያቱ እርሱ ይመስለኛል፤። ነውም ደግሞ። እስኪ ሁላችንም ሕይወታችንን እንፈትሽ ሠላምና ፍቅራችን አንጻራዊ ነው ወይስ ፍጹም ሠላምና ፍቅር ነው።

ካልሆነ ሕይወታችንን እንፈትሽ በአንድ ልብ በሰላም እንኑር። ያኔ የሰላምና የፍቅር አምላክ ልዑል እግዚአብሔር እንደ ዓለም ሰላም ያልሆነውን ፍቅር እና ሰላም ሊሰጠን ከእኛ ጋር ይሆናልና።

ሁላችንም እንደ ቃሉ ተመላልሰን በአንድ ልብ በሰላም ኖረን ዓለምና በዓለም ያለን የጎደለውን ፍቅርና ሰላም እግዚአብሔር ያድለን።

አሜን።
ይቆየን።
እያተረፉ እውቀት ለመገብየት በሁሉም ሚዲያ ይከታተሉን።

My Facebook page link (በፌስቡክ ገጽ እንገናኝ)

https://www.facebook.com/deresse2020/

Main facebook account (ዋናው የፌስ ቡክ ገጼ ይቀላቀሉት)

https://www.facebook.com/DeresseReta

Follow me through telegeram (በቴሌግራም ሊከታተሉኝ ከፈቀዱ) ሁሉም ምልከታዬን የማጋራባቸው ማህበራዊ ድረ ገጾች ናቸው።

https://t.me/deressereta

ከአሥር አመት በላይ ከ50ሺ በላይ አንባቢዎች ያሉት መጦመሪያም አለ።

www.deressereta.blogspot.com

https://anchor.fm/deresse-reta/episodes/ep-ev5j5o

እሑድ 28 ማርች 2021

በአንድ አፍ ሁለት ምላስ

 በአንድ አፍ ሁለት ምላስ

አስገዳጅ ሕግ ተግባራዊ ሊደረግ እንደሆነ ጠቅላይ አቃቤ ሕግ እና ጤና ሚኒስተር ከሰኞ ጀምሮ እንደሚተገብር የጋራ መግለጫ ሰጥቷል።

ምክንያቱ ደግሞ ከህብረተሰቡ ልቅ እንቅስቃሴ በመነሳት የኮቪድ 19 ወረርሽኝ መጠን መጨመር፣ በቫይረሱ የሚያዙ ሰወች መጨመር፣ በቫይረሱ የሚሞቱ ሰወች ቁጥር መጨመር፣ ተጎጂዎችን ተንከባክቦ ማከሚያ ሥፍራዎች መሙላት፣ የጤና ባለሙያዎች እረፍት አልባ አገልግሎት ማብቂያ ማጣት፣ የኢኮኖሚ ድቀት ወዘተ ናቸው።

በሳምንት ውስጥ ወደ 13ሺ የሚጠጉ ሰወች በቫይረሱ ተይዟል።

ይሁን እንጂ መንግሥት ቁርጠኛ አቋም እንደሌለው ማሳያዎች ብዙ መሆናቸው እሙን ቢሆንም ህብረተሰቡ ሕይወቱን በኪራይ መልክ ያገኘው ይመስል የሚጠበቀውን ያህል ጥንቃቄ እያደረገ አይደለም።

ለምሳሌ በዛሬው ዕለት በሸገር ባስ በነበረኝ እንቅስቃሴ ሰአት እንኳን ኮቪድ 19 ያለ በሠላማዊ ወቅት ሊጭን ከሚገባው በላይ ነው።

የመንግሥት መስሪያ ቤቶች በተለመደው ሁኔታ አሰራራቸው ያለምንም ጥንቃቄ በአንድ ክፍል ውስጥ ርቀታቸውን ሳይጠብቁ ተጨናንቀው መስኮት ሳይከፍቱ የእለት ተለት ተግባራቸውን እያከናወኑ ይገኛሉ።

የንግድ ስፍራዎች፣ የግብይት ስፍራዎች፣ ትምህርት ቤቶች፣ ሌሎችም ሕዝብ የሚንቀሳቀስበት ሥፍራዎች እንቅስቃሴዎች እንደወትሮው የሰው ትርምስ ይታይባቸዋል።

ይህንን በታዘብኩበት ሰአታት ውስጥ ጤና ጥበቃ ሚኒስትር እና አቃቤ ሕግ የጋራ መግለጫ እንዳወጡ ሰማሁ። በአንድ አፍ ሁለት ምላስ ብዬዋለሁ። መነሻዬም ክልከላውም ልል ቁጥጥሩም ከራሱ ስፍራ ስለሆነብኝ ነው።

ብዙዎች በሕክምና ላይ ናቸው፣ ብዙዎች ታመው ድነዋል፣ ሌሎች ሞተዋል፣ ሌሎቻችን በመያዘ እና ባለመያዝ ሁለት ምርጫ መካከል ነን። የትኛውን መምረጥ እንዳለብን የታመነ ቢሆንም ህብረተሰቡ ያለው የቫይረሱ ንቀት እና ጥንቃቄ አልባ እንቅስቃሴ ስጋት ያጭርብኛል።

መንግሥት ያቀደውን ለማሳካት ከሚረዱት አካሄዶች አንዱ የሚያስተዳድረውን የትራንስፖርት አገልገሎት ሰጪ ተቋም ሸገር ባስ፣ አንበሳ ባስ ላይ የተሳፋሪውን ቁጥር በመቀነስ ርቀትን መጠበቅ አንዱ መንገድ ነበረ። ነገር ግን ሲሆን አይታይም።

ለዚህም ነው በመነሻዬ ላይ መንግሥት ቁርጠኝነት ይጎድለዋል ያልኩት። ህዝቡም አንድ ነፍስ ብቻ እንዳለው እና አንዴ ካመለጠች መተኪያ የላትምና መልእክቴን አድርሱልኝ።

• አካላዊ ርቀታችንን እንጠብቅ
• ማስክ እናድርግ
• እጃችንን በውሃ እና በሳሙና በደንብ እንታጠብ ካልሆነም ሳኒታይዘር እንጠቀም
መንግሥትም በአንድ አፍ ሁለት ምላስ ከሚሆንብን ሕዝብህን ለመታደግ ቁርጠኝነትህን አሳየን። አስፈላጊውን እርምጃ እየወሰድክ ትውልዱን ታደግ።

ዓርብ 26 ማርች 2021

አነጋገራችሁ ሁልጊዜ በጨው እንደተቀመመ ይሁን

 አነጋገራችሁ ሁሌ በጨው እንደተቀመመ ይሁን



እንደ እግዚአብሔር ቃል አነጋገሩ ሁሌ በጨው እንደተቀመመ የሚጣፍጠኝ ዴል ካርኒንግ የሚባል ሰው አለ።


አብዛኞቻችሁ ታውቁታላችሁ ፤ የመጽሐፍ ደራሲ ነው።


ምክሮቹ፣ ተግሳጾቹ እና ዘዬዎቹ በትንሽ መጽሐፍ ተሰድራ እንደ ብሉያት እና ሐዲሳት መጻሕፍት ከዘመን ዘመን ትሻገራለች።


"የጠብታ ማር" ትሰኛለች። 


በተደጋጋሚ አንብቤዋለሁ፣ ብዙ ጊዜ ገዝቼ ለሰው በስጦታ መልክ ሰጥቼዋለሁ፣ ብዙ ጊዜ ከመጽሐፍ መደርደሪያ ላይ ጠፍቶብኛል፣ ዘወትር ለምን ብዬ ጠይቃለሁ፣ ሁሌም ሳነበው አዲስ ይሆንብኛል።


ምሥጢሩ አልገባኝም።


ይኸው ዛሬም ምሥጢሩን እየፈለኩ አንድ ነገር ብልጭ አለብኝ። " እንደ አነጋገራችን አስተሳሰባችንም በጨው እንደተቀመመ ጣፋጭ ይሆን ዘንድ።


በጨው የተቀመመ ነገር ከመጣፈጡም ባሻገር እንደ እናቶቻችን ሙያ ከሆነ አይበላሽም፣ ረጅም ጊዜ ይቆያል፣ ለብዙ ጊዜ የሚቆይ ረጅም መንገድ የሚያስጉዝ ስንቅ ይሆናል።


ከመቆየቱ ያለመበላሸቱ ድንቅ ነገር ነው። 


ጨው ሲንተራሱት ጸጉር የሚመልጥ ካልጣፈጠ ድንጋይ ነው ብለው የሚጥሉት ነገር እንዲህ ትልቅ ተግባር ሲኖረው እጅግ ድንቅ ነው። ዋጋውም ከማጣፈጫዎቹ ሁሉ እጅግ ርካሽ ነው።


የሰው አንደበትም፣ አስተሳሰብም፣ ቃላትም እንዲሁ ዋጋቸው ትንሽ ውጤታቸው ትልቅ የሆኑትን መተግበር ተስኖን አለማችን መራር ሆናለች።


አነጋገራችን እና አስተሳሰባችን ዘወትር በጨው የተቀመመ ጣፋጭ ይሁን። 


የትናንቱን እና የዛሬውን በማሰብ አስተሳሰባችንን ከማጥበብ ነገን እያሰብን ሐሳባችንን፣ ቃላቶቻችንን የጣፈጡ እንዲሁም ሰፊ እናርጋቸው።


ሰናይ እለተ ሰንበት ይሁንልን።

ይቆየን።


@deressereta

የጾም ምግብ ቤቶች

 የጾም ምግብ ቤቶች


በየከተማችን የኢትዮጵያን ቤተክርስቲያን የአጽዋማት ጊዜ ጠብቀው ምግብ ቤቶች በአዲስ መልክ ማስታወቂያ መስራት የተለመደ ነው።


አንዱን ብንመለከት የአብይ ጾምን ምክንያት በማድረግ የጾም ቡፌ፣ በየአይነቱ፣ ዓሣ አዘጋጅተናል። የምትል ትገኝበታለች። 


ማስታወቂያዎቹ ለጾም እና ጸዋሚ "ተጨንቀው" ምግብ እንደ ማዘጋጀታቸው ጥራጥሬ፣ ሽንብራ፣ ደረቅ ቂጣ አያዘጋጁም። ዝግጅቱ ለጾም ሳይሆን ለመብል ነውና።


ፍትሐ ነገሥት ስለ አጽዋማት በሚናገረው አንቀጹ አንቀጽ 15 ላይ በ572ኛው ቁጥር ላይ " በእነዚህ በታዘዙት ጾሞች ከቀኑ እስከ ዘጠኝ ሰአት ድረስ ይጹም ከዓሣ በቀር ሥጋ አይብሉባቸው። " ይላል።


ግእዙ እንዲህ ተብሎ ተጽፏል፦" ... ወኢይብልዑ ቦሙ ሥጋ ዘእንበለ ዓሣ ..." እዚህ ጋር ሊቃውንቱ እንደሚነግሩን "ዘእንበለ" ፍችው ብዙ ከመሆኑ የተነሳ ሲያጨቃጭቅ ቆይቷል። ቤተክርስቲያኒቱ ለዚህ መፍትሔ ይሆን ዘንድ ከመጽሐፍ ጠቅሳ ዓሣ የሥጋ ዘር ነውና። ደምም አለውና ጾም እንደሆነ በሲኖዶስ ደንግጋለች።


ፍትሐ ነገሥትም በዚሁ አንቀጽ ቁጥር 584 ላይ " በጾም ምክንያት ጠብ ክርክር ቢሆን መጾም ይገባል። ከመብላት በጣም ይሻላል።" ይለናል። 


ነገር ግን ጸዋሚው የቅድስት ቤተክርስቲያን ልጅ ራሱ ለምግብ ሲቀመጥ ዓሣ አልጾምም ሲል ይደመጣል። ለነፍሱ ሊያደላ በሚገባው ወቅት ለሥጋው ያደላል።


"ከዓሣ በቀር ሥጋ አይብሉባቸው።" በሚለው ቃል ዓሣን አልጾምም የሚለው "ጸዋሚ" ከፍ ብሎ " ከቀኑ እስከ ዘጠኝ ሰአት ድረስ ይጹሙ " የሚለውን አያነበውም፤። አይተገብረውም።


" ጾምስ በሕግ ውስጥ በታወቀው ጊዜ የሰው ከምግብ መከልከል ነው በደሉን ለማስተሰረይ ዋጋውን ለማብዛት እርሱን ወዶ ሕግን ለሠራለት እየታዘዘ የፈቲውን ኀይል ያደክም ዘንድ ለነባቢት ነፍስም ትታዘዝ ዘንድ " የተሰራ መንፈሳዊ ተግባር እንደመሆኑ መጠን በጾም ወቅት መከልከል ከሚገባን ነገር ሁሉ ልንከለከል ይገባናል፣ በደላችንን ለማስተስረይ ንሰሐ ገብተንም ልንጾም ይገባል፣ ወደን ፈቅደን ሕግንም ለሰራልን ልንታዘዝ ይገባል፣ ሥጋችንንም ለነፍሳችን ልናስገዛም ይገባል።


ጾም ከምግብ መክልከል ሥጋን ማድከም ነፍስን ማለምለም እስከሆነ ድረስ ምግብ ቤቶቻችን በአንጻሩ ምነው በምግብ ማስታወቂያ ለዚያውም ለመጾም በማይጋብዙ የምግብ ዝርዝሮች ጠብ እርግፍ አሉ?


የምግብ ቤቱን አነሳን እንጂ ከወትሮው በተሻለ በየሁላችን ቤት ከፍስኩ ጊዜ ይልቅ የምግብ አይነቱ በጾም ወቅት አይደለምን? ከዚህ ምን እናተርፋለን? ወይንስ እንዲሁ እንዘጭ እንዘጭ ነው?


መጾም ይገባልና ከመብላትም በጣም ይሻላልና ጾመን በረከትን እናግኝ፣ በደላችንንም እናስቀር፣ ስንጾም ብልቶቻችን ሁሉ (ዓይን፣ ጆሮ፣እግር፣ አንደበት፣ወዘተ) ይጹሙ። 


የጾም ምግብ ቤቶችም በስመ ጾም ከመነገድ ቢታቀቡ መልካም ነው፤ እኛም ስንመገብ በማካካሻ መልክ በሚመስል ባንመገብ መልካም ነው።


ስለ አጽዋማት ያለን አመለካከት ይቀየር የቄስ፣ የመነኩሴ፣ የሕጻናት፣ የሚባል ጾም የለም። እድሜው ሰባት አመት የሞላው የጤና እክል እና በንሰሐ አባቱ በኩል በተለያዩ ምክንያት ከሚፈቀድ በቀር ሰባቱም ጾሞች ሊጾሙ ይገባቸዋል።


" ከዚህ ከታዘዘው አብልጦ የጾመ ግን ዋጋው ይበዛለታል። " እንዲል።


አብዝተን ጾመን የበረከቱ ተሳታፊ ለመሆን ያብቃን። ጾሙ የሐጥያት መደምሰሻ፣ የዲያብሎስ ድል መንሻ፣ የመንግሥተ ሰማያት መውረሻ ያድርግልን።

አሜን።

ይቆየን።


@deressereta


comment እና subscribe ማድረግ አይርሱ

እነዚህን ነቢያት እኔ አላክኋቸውም

 " እነዚህን ነቢያት እኔ አላክኋቸውም "


ትንቢተ ኤርሚያስ 23 : ከቁጥር 9 ጀምሮ ብናነብ እግዚአብሔር በሐሰተኞቹ በሰማሪያ ነቢያት ምን ያህል እንደተማረረ እንመለከታለን። እነዚህን ነቢያት እኔ አላክኋቸውም እስኪል ድረስ።


ወዳጄ ብዙ ሰው ያውቅህ ይሆናል፤ ታዋቂነትህም ከአገር አገር የናኘ ሊሆን ይችል ይሆናል። ብዙ ተከታዮችም ይኖርህ ይሆናል። በዚህም የተነሳ ክብርህ ጥግ ደርሶ ሊሆን ይችላል።


ነገሮች ሁሉ ተቃንተውልህ የትናንት ሕይወትህ ተቀይሮ ሊሆን ይችላል። የመርገም አንደበትህ የምርቃት፣ የውሸት አንደበትህ የእውነት የሆነውን ቃል ትጠቅስበት ይሆናል፣ የድህነት ታሪክህ በባለጸግነት፣ ማይምነትህ በአዋቂነት ሥም ተተክቶልህ ሊሆን ይችላል፣ የትናንቱ እግረኛ ዛሬ የዘመናዊ መኪና ባለቤት ሆነህ ሊሆን ይችላል፣ በአጠቃላይ ታሪክህ ተቀይሯል።


ስለ እውነት አንተ ተቀይረሃል? 


ባለጸጋ ስትባል ነፍስህን አላጎደልካትም?


ለሌሎች የእግዚአብሔርን ቃል እንደ ወተት ስትግት አንተ ግን ቃሉን አልተጠማህምን?


ምድራውያን ሰወች ሲያከብሩህ ዋጋህን በምድር ስትቀበል በሰማይ ያለውን የአባትህን ዋጋ አልተነጠክም?


ነብይ ነኝ ስትል፣ ሐዋሪያ ነኝ ስትል፣ ወንጌላዊ ነኝ ስትል፣ አገልጋይ ነኝ ስትል፣ አጥማቂ ነኝ ስትል፣ ባህታዊ ነኝ ስትል፣ ወዘተ ብዙዎች ሁሉን ትተው ተከትለውህ አደባባዮችህ ደምቀው መድረኮችህ ጠጠር መጣያ እንኳን ጠፍቶ ሊሆን ይችላል። ወዳጄ በእግዚአብሔር ዘንድ እንደ አለመታወቅ አሳፋሪ ነገር የለም።


እግዚአብሔር በሚያውቅህ ልክ እንጂ ዋጋህን የምትቀበለው በታዋቂነትህ ልክ አይደለም።መድረክህ ስትይዝ የእግዚአብሔርን ቃል ጠንቅቀህ ማወቅህ እንጂ ታዋቂነትህ ለአድናቆትህ ሽፋን እንጂ የሚሆንህ ለመዳንህ ምክንያት አይሆንህም።


እነዚህን ነቢያት እኔ አልላኳቸውም እንደመባል አሳፋሪ ነገር የለም። አንተ ከየትኛው ነህ?


ወዳጄ አንተ የምትከተለው "አገልጋይ" ከየትኛው ወገን ነው? ተከታዮቹ ስለበዙ መድረኩ ስለደመቀ፣ ድምጹ ነጎድጓዳማ ስለሆነ፣ የልብህን መሻት ስለሚነግርህ፣ ስለማይገስጽህ፣ ወይንስ የእግዚአብሔር አገልጋይ ስለሆነ ነው?


• 2ኛ ቆሮንቶስ 11 : 13

" እንደ እነዚህ ያሉ ሰዎች የክርስቶስን ሐዋርያት እንዲመስሉ ራሳቸውን እየለወጡ፥ ውሸተኞች ሐዋርያትና ተንኮለኞች ሠራተኞች ናቸውና። "

ስለሚልባቸው በእነርሱ ላይ ያለው እናንተ እየተከተላችሁት ያለው መንፈስ የትኛው እንደሆነ መርምሩ " መንፈስን ሁሉ አትመኑ "ይላልና።

• 2ኛ ጢሞቴዎስ 3 : 1- 6

ነብያትን ነን እያሉ ምእመናንን የሚያስጨንቁ፣ ሐብትና ንብረትን የሚነጥቁ፣ ሴቶችን ከክብራቸው የሚያነውሩ፣ ቃለ እግዚአብሔርን ቁጭ ብለው ሳይማሩ ቆመው የሚያስተምሩ፣ ርኩስ መንፈስ የሚጫወትባቸው ናቸው።


ገንዘብን ከመውደዳቸው የተነሳ የማያደርጉት ነገር የለም፤ ትእቢተኞች እና ተሳዳቢዎች ናቸው። ክብራቸው በነውራቸው ሐሳባቸው ሁሉ ምድራዊና ብልጭልጩ አለም የሆነ። ጽድቅን በምድራዊ ስኬታቸው የሚያወዳድሩ ከንቱዎች ናቸው።


የእግዚአብሔርም ቃል ከነዚህ ራቁ ይለናል። ተከታዮቻቸው ግን ብዙ ናቸውና የተቀሩትም የተከታዮቻቸውን ብዛት ተመልክተው ይከተሏቸዋል። 


ጠማማ ትውልድ ምልክትን ይሻልና 'ድንቅ ተአምር' እናያለን፣ 'ፈውስ' እናገኛለን፣ በማለት በሐሰት ትርክታቸው ተታለው እዚያው ይቀራሉና ከነዚህ ደግሙ ራቁ ለማለት እወዳለሁ።


" ነገር ግን በመጨረሻው ቀን የሚያስጨንቅ ዘመን እንዲመጣ ይህን እወቅ። ሰዎች ራሳቸውን የሚወዱ ይሆናሉና፥ ገንዘብን የሚወዱ፥ ትምክህተኞች፥ ትዕቢተኞች፥ ተሳዳቢዎች፥ ለወላጆቻቸው የማይታዘዙ፥ የማያመሰግኑ፥ ቅድስና የሌላቸው፥ ፍቅር የሌላቸው፥ ዕርቅን የማይሰሙ፥ ሐሜተኞች፥ ራሳቸውን የማይገዙ፥ ጨካኞች፥ መልካም የሆነውን የማይወዱ፥ ከዳተኞች፥ ችኩሎች፥ በትዕቢት የተነፉ፥ ከእግዚአብሔር ይልቅ ተድላን የሚወዱ ይሆናሉ፤ የአምልኮት መልክ አላቸው ኃይሉን ግን ክደዋል፤ ከእነዚህ ደግሞ ራቅ። "


ሐሰተኛ ነቢያት እንደመኖራቸው መጠን እውነተኞች መኖራቸው እሙን ነው። ቃሉም ስለ እውነተኞቹ ነቢያት ሲናገር እናያለን ኤርሚያስ 1 : 5 እና ሕዝቅኤል 3 : 17 እንዲሁም የሐዋርያት ሥራ 9 : 15 ላይ ይመሰክርላቸዋል።


ከእናታቸው ማህጸን ጀምሮ የተመረጡ እንዳሉ የተለያየ አገልገሎትም እንደሰጣቸው ለሕቡም ጠባቂ እንዳደረጋቸው እናያለን።


ነቢዩ ኤርሚያስ ግን በእግዚአብሔር ተገብቶ እንዲህ እያለ ይናገራል።


" እኔ ሳልልካቸው እነዚህ ነቢያት ሮጡ፤ እኔም ሳልነግራቸው ትንቢትን ተናገሩ። በምክሬ ግን ቢቆሙ ኖሮ፥ ለሕዝቤ ቃሌን ባሰሙ ነበር፥ ከክፉም መንገዳቸው ከሥራቸውም ክፋት በመለሱአቸው ነበር። አለምሁ አለምሁ እያሉ በስሜ ሐሰትን የሚናገሩትን የነቢያትን ነገር ሰምቻለሁ። " 


ቃሉ እነዚህን ራሳቸውን ነቢያት ነን ባዮችን እግዚአብሔር እንደማያውቃቸው ያስረግጥልናል።


ስለዚህ እግዚአብሔር ቅር ከተሰኘበት መንገድ እንድንመለስ ሰውንም ከመከተል እንድንታቀብ በሐሰተኞቹም እንዳንታለል አደራ እላለሁ።


ይቆየን።


@deressereta

እግዚአብሔር ያዘዘኝን አደርጋለሁ

 "እግዚአብሔር ያዘዘኝን አደርጋለሁ እንጂ እኔ አዝዛለሁን?"


ሀብተ መርገም እና ሀብተ በረከት የተሰጠው በለአም ለባላቅ የመለሰው ምላሽ ነበረ።


እስራኤል ከግብጽ ሲወጡ አሕዛብን ድል እየነሱ ሲመጡ በባላቅ ወልደ ሶፎር አገር አጠገብ በሞዓብ ሜዳ በሰፈሩ ጊዜ የእስራኤላውያንን ጥንተ ታሪክ ያውቅ ነበረና እጅግ ፈራ።


ፈርቶም አልቀረ በአሞራውያን ላይ ያደረሱት በርሱና በሕዝቡ እንዳይደርስ በለአምን ና እና ርገምልኝ አለው።


በለአምም እስራኤላውያን የእግዚአብሔር ሰወች እንደሆኑ የተባረኩም ሕዝብ እንደሆኑ ያውቅ ነበረና፣ እግዚአብሔርም አትርገማቸው ብሎታልና ላይረግማቸው ላይሄድ ወሰነ። 


ባላቅም ከአንዴም ሁለቴ ከጥሩ ገንዘብ ጋር ሰው ላከበት ሆኖም በለአም ሳይመጣ ቀረ፤ በመጨረሻም እግዚአብሔር በራእይ ለበለአም እንዲህ አለው " መሔዱን ሒድ ነገር ግን እግዚአብሔር የገለጠልህን ተናገር እንጂ አትራገም" አለው።


እንደሄደም እስራኤላውያንን ከአንዴም ሶስቴ መረቃቸው፥ ባላቅም ተቆጣ። "ርገምልኝ አልኩህ እንጂ መርቅልኝ አልኩህን?" አለው።


"እግዚአብሔር የገለጸልኝን እናገራለሁ እንጂ ሌላ ምን ላደርግ እችላለሁ?" ብሎ በለአም መለሰለት።


በማግስቱም እንዲሁ ሆነ ሰባት ላም፣ ሰባት ዳንግሌ ሠዋለት። በለዓምም እንደ ልማዱ ያሟርት ጀመረ። ነገር ግን ዛሬም መራገም አልተቻለውም።


መጽሐፍም እንዲህ ታሪኩን ያስነብበናል፦ " እግዚአብሔር እንደ ሰው ሐሰት አይናገርም፣ በሠራውም ሥራ አይጸጸትም እኔ እስራኤልን እንድመርቅ ትእዛዝ ተቀብያለሁና በያዕቆብ ክፋት አላይበትም። እግዚአብሔር አምላክ ከእርሱ ጋራ ነውና። በያዕቆብ ላይ አስማት የለም፣ በእስራኤልም ላይ ሟርተኝነት አይቻልም። ይህ ሕዝብ እንደ አንበሳ ደቦል ነው። ያንበሳ ደቦል የሰበሰውን ሥጋውን ሳይበላ፣ ደሙን ሳይጠጣ እንዳይመለስ ይህ ሕዝብም አሕዛብን ሳያጠፋ አይመለስም" ይለናል 


ባላቅም ያሰበው ባይሳካ ያላሰበው እንዲሆንበት አልፈለገምና  በተስፋ መቁረጥ ውስጥ " መራገም ቢቀር እንኳን ባይሆን መመረቁን አትተውምን? ይህን ሕዝብ ለምን ትመርቀዋለህ?" አለው።


በርእሳችን እንዳነሳነው በለአም መለሰለት፥ " እግዚአብሔር ያዘዘኝን አደርጋለሁ እንጂ እኔ አዝዛለሁን?" አለው።


ድንቅ መልስ ነው።


ይህ ታሪክ በበለአምና በባላቅ መካከል፣ በእስራኤላውያን እና በባላቅ አገር ሰወች መካከል የሆነ የተመዘገበ ቢሆንም ቅሉ የእግዚአብሔር ቃል፣ የእግዚአብሔር ፈቃድ፣ ግን ቦታ የማይገድበው ጊዜ የማይሽረው ነውና እራሳችንን እንመልከትበት።


እኛ የማንን ፈቃድ እናደርጋለን? የሥጋን ፈቃድ ነው የነፍስን ፈቃድ እንፈጽማለን? በገንዘብ እንገዛለን ለእግዚአብሔር እንገዛለን? እንመርቃለን ወይንስ እንረግማለን?


አለማችን እንዴት ሰነበተች? ብለን በእግዚአብሔር መንፈስ ብንቃኘው  በውኑ የእግዚአብሔርን ሕዝብ የሚሳደብ፣ የእግዚአብሔርን አገልጋይ ካህናትን እና በቤቱ የሚመላለሱትን፣ እግዚአብሔር የመረጣቸውን እና የቀባቸውን የሚያንጓጥጥ ነው የሞላው ወይንስ የሚመርቃቸው?


የባላቃዊያን ሀሳብ የፈለገውን ቢሆንም የእግዚአብሔርን ፈቃድ መሻር አልተቻለውም። እግዚአብሔር የመረጣቸውን ማንም አይቃወማቸውምና። 



ኢትዮጵያ እና ኢትዮጽያዊያንም እንደዚሁ ናቸው፤። የማንም ሰልፍ አያሸንፋቸውም። የማንም ሟርት እና እርግማን አይደርስባቸውም። አንድነታቸውና ህብረታቸውም የኢትዮጵያን ጉዞ አይገታም። እግዚአብሔር ከርሷና ከሕዝቦቿ ጋር ነውና።


እንደ ፈቃዱ ተመላልሰን የእግዚአብሔር ሕዝቦች እንደተባልን ጸንተን ቆይተን እግዚአብሔር አጥር ቅጥር ይሁነን። ከጠላቶቻችን ይጠብቀን፣ የተቃጣብንን ይመክትልን፣ በመርገም ፈንታ ይመርቀን፣ መውጣት መግባታችንን በአባታዊ አይኑ ይከታተልልን።


የጠላቶቻችንን ዓይን ጨለማ ጉልበታቸውን ቄጠማ ያድርግልን።


በእግዚአብሔር ማመናችን መዘባበቻ ሳንሆን መጽናኛ ይሁነን።


የአባቶቻችን በረከታቸው ጥርጥር የሌለባት ተዋህዶ እምነታቸው በረከቷ ይደርብን።


የተጀመረውን ጾም ሥጋችንን ገዝተን፣ ነፍሳችንን አበርትተን ጠላት ዲያቢሎስን ድል የምንነሳበት የእግዚአብሔርን መንግሥት የምንወርስበት ያድርግልን።


@deressereta

እንተወው

 "እንተወው"


መጋቢ ሐኪስ እሸቱ ሁሌም በጨው እንደተቀመመ ቃላቸው ሁሌም ይጥመኛል።


እንዲህ ይላሉ፦ "እንተወው ... ካልተውንው እና የሆነብንን፣ እየሆነ ያለውን፣ ሊሆን ያለውን ካሰብን አይደለም ከሰው ጋር ያለን ጉዳይ ይቅርና ትዳራችንን እስክንፈታ ድረስ የሚሄድ ጉዳይ ነው ይላሉ።" 


እውነት ነው ካልተውነው በቀር ስለ አገራችን ፖለቲካ እና ፖለቲከኞች፣ ስለ አገራችን እምነቶች እና በእምነቱ ስም ስለሚተውኑ ሰወች፣ የኑሮ ሁኔታ እና ኑሮውን ስለሚዘውሩ ሰወች፣ ስለ ሶሻል ሚዲያው እና በሶሻል ሚዲያው እንጀራቸውን ስለሚጋግሩ ሰወች፣ ወዘተረፈ የምናውቀውን እንናገር ካልን ጓደኝነታችን አይደለም ትዳራችን ይፈርሳል።


 መንደራችን፣ ብሔራችን፣ ቤተእምነታችን፣ ቡድናችን፣ ፓርቲያችን፣ ወዘተ ይፈርሳል። 


ከመጋቢ ሐዲስ እሸቱ አለማየሁ በተማርኩት መሠረት ስለምታውቅ፣ መረጃው ስላለህ፣ ከሁነኛ ሰው ስለሰማህ፣ አትንገር ብለው ስለነገሩህ፣ ... ሁሉ ነገር አይነገርም።


አንተ የደረሰብህ ጉዳይ ፀሐይ የሞቀው አገር ያወቀው ምስክር ጥራ ብትባል አገር ምድሩ ግልብጥ ብሎ ስለሚመሰክርልህ በሕግ ፊት ፍትህ ስለምታገኝ ሁሉ ነገር አይወራም።


መረጃ ማስረጃ አቅርበህ፣ ጠበቃ አቁመህ መርታት ስለምትችል ሁሉ ነገር አይወራም።


አንዳንዴ ጊዜ የሚፈታው፣ አንዳንዴ ለምጣዱ ሲባል አይጧን እንደምታልፋት ሁሉ ዝም ብለህ ማለፍ ትተህ የምታልፈው ነገር እንዳለ መተው ግድ የሆነበት ጊዜ እንዳለ ልብ በል።


@deressereta

ጦማሩን ስለጎበኙ አመሰግናለሁ!

መልካም ነገርን ለሌሎች ማጋራት ባህላችን እናድርግ፤ ላልደረሰዉ በማጋራት ድርሻችንን እንወጣ፡፡

ትቶ እና ችሎ

  ትቶ እና ችሎ ብጹእ ወቅዱስ አቡነ መርቆርዮስ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ በደረሰ ረታ ብጹዕነታቸው ለሶስት አሥርት አመታት እኛ በማናውቀው እግዚአብሔር በሚያውቀው በብዙ መከራ በብዙ ፈተና ውስጥ ነው ያሳለፉት። ...