- የዱር አራዊቶች አቤቱታ
- ሰሞኑን በዚች በምድራችን ‹‹ጫካው ለዛፎች ብቻ›› በሚል ዛፎች ተሰባስበው በዱር አራዊቶች እና አዕዋፎች ላይ የአቋም መግለጫ አወጡ አሉ፤ ከመግለጫው ሥር እንደ አብይ ርዕሰ ጉዳይ ያደረጉት ጫካው ለእኛ ለዛፎች ብቻ ይሁን በማለት ተስማሙ አራዊቶችም አዕዋፍም ወደ ጫካው ዝር እንዳይሉ ተደረገ፡፡
ምንም እንኳን ዛፎች ይኸንን የመሰለ
የመገንጠል የራስን ክልል በራስ የማዘዝና የመግዛት /የማስተዳደር/ አቋማቸውን ቢያሰሙም ዛፎች ቅሬታቸውን በማሰማታቸው የተነሳ
በህብረት በመስማማት መብታቸውን ቢያስከብሩም የዱር አራዊትም እንደ ዜጋ መብታቸውን ለማስከበር በጋራ እንደ አንድ ልብ መካሪ
እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ በመሆን ተሰባሰቡ፡፡
የዱር አራዊቶቹ ይሰብሰቡ እንጂ በቀላሉ
አንድ አቋም መያዝ፣ ተስማምተው መብታቸውን ማስከበር፣ በአንድ ልብ ለዱር አራዊት መብት መሟገትና አልፎ ተርፎም ተቃዋሚዎቻቸውን
መርታት ተስኗቸው ስብሰባው ለሌላ ቀን ቀጠሮ ተይዞ ተበተነ በበነጋታውም እንደ ትናንቱ ተማምለውና ተገዝተው የጎበዝ አለቃ
መርጠው በየነገድ በየነገዱ በየጎሳ በየብሄሩ በየጎጡ ያሉት ተወካዮቻቸውን ልከው የዱር አራዊቶች የአቤቱታ የአቋም መግለጫ
ማውጣት ሥነ-ሥርዓት ተጀመረ፡፡
ዛሬም እንደ ትናንቱ አለመግባባት መከፋፈል
አለመደማመጥ አንተ ትብስ አንተ ትብስ መባባሉ ቀርቶ እኔ እብስ ካንተ ይልቅ እኔ እሻላለሁ፤ የጋራ ጉዳይ ቀርቶ የግል ጉዳይ፣
የጎሳ ጉዳይ፣ የብሔር ጉዳይ፣ የጎጥ ጉዳይ፣የዘር ሐረግ ጉዳይ፣ የፖለቲካ፣ የሃይማኖት፣
የቀለም ጉዳይ ወዘተ … ሰፍኖ ስብሰባው ተናጋሪ እንጂ አዳማጭ ጠፋበት የጋራ መብታቸውን፣ ለማስከበር ተሰባስበው ይባስ ብለው መጋጨት፣
ለነፍስ መፈላለግ፣ ወደ ቂምና ቁርሾ፣ እንዲህ አለኝ እዲህ አለችኝ ወዘተ … መባባል ተጀመረ፡፡
በዕድሜያቸው አንድ ጠና ያሉ ብዙ ዓመታትን ረጅም ወራትን በዱር በጫካ የመኖር ልምድ የነበራቸው አንድ የዱር
እንስሳ አንተም ተው አንተም ተው ብለው ጭቅጭቁን ካበረዱት በኋላ ሁሉም የዱር አራዊት ተወካይ የሚሰማውን የውስጥ ብሶቱን የሚናገርበት
ደቂቃ እንደሚሰጠው እና እንደሚናገር አስገንዝበው ስብሰባውን በአዲስ ሰብሳቢ ምክትል ሰብሳቢ ፀሐፊና የተወሰኑ አባላት ኮሚቴ አዋቅረው
ስብሰባውን አስቀጠሉት፡፡
አዲስ ተሻሚ ኮሚቴዎችም ስራውን በይፋ ከመጀመራችን በፊት የተፈጠረውን ችግር ከሁላችሁ እናዳምጥ ከዚያም
ለችግሩ መፍትሔ ሰጥተን ወደ ዋናው ሥራችን እንገባለን ብለው ችግሩን አንድ በአንድ መስማት ጀመሩ፡፡ ከተጠቀሱት ችግሮች መካከል
ዋና ዋናዎቹ እነዚህ ነበሩ፡- ዓላማውን የጋራ ዓላማ ከማድግ ይልቅ የግል ማድረግ፣
- መከፋፈል
- እኔ እበልጣለሁ በማለት ሌሎችን ማሳነስ
- ለሌላው ተቆርቋሪነት መጥፋት
- የፖለቲካ ልዩነት
- የሃይማኖት ልዩነት
- የጎሣ ልዩነት … ወዘተ መፍጠር
ሁሉም የዱር አውሬ የጋራ ጉዳይ የነበረውን
አቤቱታ ወደ የግል ጉዳይ ጥቅም ማስከበር ተሸጋገረ፤ ጅብ ተነስቶ ስለሌሎች የዱር አራዊቶች ያለውን ጉዳይ ወደጎን በመተው ስለጅቦች
ብቻ ማውራት ቀጠለ ቀጥሎም በፆታ በመከፋፈል ስለወንዶች ጅብ ብቻ መቆርቆር ቀጥሎም ጫካ ውስጥ እና ጉድጓድ ውስጥ ስለሚኖሩት፣ በዕድሜ
ስለገፉትና ስለ ግልገሎች፣ ከተማ አካባቢ ስለሚኖሩትና ገጠር ስለሚኖሩት እያለ እዚያው ውስጣቸው መከፋፈሉ ቀጠለ ይግረማችሁ ብሎ
በራሱ ላይ ስላደረሰ በደል ስለተሰማው ቅሬታ በምሬት በመናገር ለራሱ መብት ብቻ መሟገት ብዙኃንን የራሳችሁ ጉዳይ ብሎ እርፍ አለ፡፡
በዚሁ መልክ እነ አንበሳ፣ ዝሆን፣ ቀጭኔ፣ ጥንቸል፣ ቀበሮ ወዘተ … የየግላቸውን በማንሳት መስማማት አቃታቸው
በጋራ ሆነው በደላቸውን ለማስቆም እያደረጉት የነበረውን ጥረት ከግቡ ማድረስ አቅቷቸው ራሳቸው ከችግር ፈቺነት ወደ ችግርነት፣ ከመፍትሔ
ሰጪነት ወደ አወሳሳቢነት፣ እርስ በርስ የጎሪጥ ወደመተያየት ‹‹ድር ቢያብር …›› የሚባለውን ተረት ዘነጉት፡፡
እንዲሁ ትናንት በዱር አራዊቶች ጠላትን /አጥቂን/ በጋራ ሆነው የመከላከል ውጥናቸው ከዳር ሳይደርስ እንደቀረ
ዛሬም በዓለማችን ይልቁንም በአፍሪካ ከሰዎች ልጆች መካከል በጋራ የሚሆን ነገር የጠፋው፣ አገሬን ወገኔን ህዝቤን የሚል የጠፋው
አገርን የሚመራ ጠፍቶ የፓርቲ መሪ ብቻ እንደ አሸን የፈላው፤ ለህዝብ /ለብዙኅን/ ጥቅም የሚቆም ጠፍቶ ለራሱ ሆድ ብቻ ዘብ የቆመ
የበረከተበት፣ ለዚህ ይመስላል በአንዳንድ የአፍሪካ መሪዎች ላይ ለምልክት ያህል የቀሩት ይማሩ እንደሆነ ህዝቡ በመሪዎቹ ላይ ያመፀው
ልትመራን ካልቻልክ የኛ ጉዳይ ጉዳይህ መሆኑ ከቀረ ለሀገር ሳይሆን ለግል ክብርና ዝናህ የግል ምቾትህንና ኃብትህን ለማደለብ ከሆነ
ስልጣን በቃህ ብለው ደማቸውን አፍሰው ሥጋቸውን ቆርሰው አጥንታቸውን የከሰከሱት እና እብሪተኞች መሪዎቻቸውን ለዘላለም ከስልጣን
የማይወርዱ ይመስሉ የነበሩትን በሥጋት የአልጋ ቁራኛ፣ በሞትና በሽንፈት ለመቃብር እና ለስደት የዳረጓቸው፡፡
መሪዎችም እንደ አጀማመራቸው ህዝብን አገርን ሁሉንም ሳይለዩ ይመሩ የነበሩት አቅም ሲያንሳቸው ዓለማቸውን
ሲዘነጉ ቃላቸውን ሲያጥፉ ወደ የፖለቲካ መሪነት አቅም ያሽቆለቆሉት፣ አንድ ሆኖ የተነሳን ህዝብ በፖለቲካ በሃይማኖት በዘር በጎሣ
በቋንቋ በቀለም ይባስ ብሎ በፆታና በዕድሜ ወዘተ … በመከፋፈል የበተኑት የአንድነትን ወኔ ነጥቀው የአገር ስሜት ልቡን ያኮላሹበት
ሃገርን ወገንን በመተው ብዙኅንን እርግፍ አርገው ሆዳችን ከሞላ ደረታችን ከቀላ ምን አገባን ያሉት፡፡
የዱር አራዊቶቹ አቤቱታቸው እንዳይሰማ ችግራቸው መፍትሔ እንዳያገኝ ያደረጋቸው የጋራ ሃሳባቸውና አቋማቸው
አልነበረም የግል ፍላጎታቸው ራስ ወዳድነታቸውና መከፈላቸው እንጂ አፍሪካንም የጦርነት አውድማ ያደረጋት ሰላም ያሳጣት ሁሌ ተመጽዋችና
የአውሮፓውያንና የሌሎች ኃያላን ሃገራት የኢኮኖሚና የፖለቲካ እንዲሁም የባህል ቅኝ ተገዢ ያደረጋት የህዝቦቿ አንድ ያለመሆን ችግር
የመከፋፈል አባዜ የመሪዎቿ ቃላቸውን ያለመጠበቅ ዓላማቸውን መዘንጋት ለሰላምና ለነፃነት ተዋግተው ሥልጣን እንዳልያዙ፣ ስልጣን የህዝብ
ነው ብለው እንዳልዘመሩና እንዳልፎከሩ ህዝብን ማስለቀስ ማሰቃየት ሰላም መንሳትና ነፃነትን መንጠቅ የምንም ውጤት አይደለም ከጋራ
አቋም ይልቅ በግል አቋም የመታበይ፣ ከአገር ጉዳይ የራሴ ጉዳይ ይብሳል፣ ከህዝብ ይልቅ የራሴ ቤተሰብ (እኔ ብቻ ብሎ) መደንቆር
ካልሆነ በቀር፡፡
አፍሪካውያን እንኳንስ ለውስጥ ጠላት ኢትዮጵያን የመሳሰሉት ድንበር ተሻግረው
የመጡትን በጦርነት ሥልጣኔ በጣም የመጠቁትን ተዋግተው የአገርን ዳር ድንበር ያስከበሩ ወገንን ያኮሩ ታሪክን በደማቸው የፃፉ ነበሩ
ዛሬ ግን እንደ ዱር አውሬዎቹ በመሪዎቿ ችግር ባልተጠናከረ የአፈፃፀም ሥርዓትና በአንድ አንቀጽ ተከፋፍለው በመለያየት ‹‹እኛ››
ከሚለው ሃገራዊ ስሜት ይልቅ ‹‹እኔ›› ወደሚለው ግላዊነት ተሸጋግረዋል፡፡ ይህ ሁሉ የሆነው ሥልጣን ላይ ያሉት /የህዝብ ተወካዮች/
እንደ ዱር አውሬዎቹ ተወካዮች የህዝብን የብዙኅንን ድምፅ ፍላጎት እንደማሰማት የራስን ፍላጎትና ምኞት ማንፀባረቅ በጋራ ፍላጎት
እና አቋም እንደ መመራትና እንደማስተዳደር በሥሜታዊነት መነዳት መርሃቸው ከሆነ ሰነባበተ የአገራችንን ዕጣ ፈንታ እንደሌሎች አገራት
ዕድገቷን ሊያቀጭጩ፣ የጦርነት አውድማ ሊያደርጓት ዛራቸው ፈረሱን ጭኗል፡፡ visit us again!