+ እግዚአብሔር እንዴት ይፈርዳል? +
(ጊዜ ወስደው ያንብቡት አያጥር ነገር ታሪክ ሆኖ ነው)
አንድ ግብፃዊ መነኩሴ ለገዳሙ መርጃ የእጃቸው ሥራ የሆኑትን ቅርጫቶች ሊሸጡ ወደ እስክንድርያ ለመጓዝ በጠዋት ተነሡ፡፡
በመንገድ ላይ ታዲያ ትልቅ የቀብር ሥነ ሥርዓት ለማድረግ የሚጓዝ ሕዝብ ገጠማቸው፡፡ ሟቹ ዝነኛ አረማዊ ገዢ ሲሆን በዘመነ ሰማዕታት በሺህ የሚቆጠሩ ክርስቲያኖችን የገደለ ሰው ነበር፡፡ አሁን ዕድሜ ጠግቦ ሞቶ ነው፡፡ ቀኑ ውብ ፀሐያማ ቀን ነበርና የሀገሩ ዜጎች በነቂስ ወጥተው ገዢያቸውን እየቀበሩ ነው፡፡
ይህንን ያዩት መነኩሴ ጉዳያቸውን ፈጽመው ወደ ገዳም ሲመለሱ አሳዛኝ ዜና ሰሙ፡፡ ለስድሳ ዓመታት በበረሃ በብሕትውና ቅጠልና የበረሃ ፍሬ ብቻ እየበላ የኖረ ባሕታዊ በዚያች ዕለት በጅብ ተበልቶ ሞቶ ነበር፡፡
መነኩሴው እጅግ ጥልቅ ኀዘን ውስጥ ሆነው እንዲህ ሲሉ አሰቡ ፦
‘በሺህ የሚቆጠሩ ክርስቲያኖችን የገደለው አረማዊ ሰው በታላቅ ክብር ታጅቦ ሲቀበር ሕይወቱን ሙሉ በጾምና በጸሎት ፈጣሪውን ያገለገለው ባሕታዊ በጅብ ተበልቶ የተዋረደ አሟሟት ሞተ፡፡ይህ እንዴት ዓይነት ፍርድ ነው? እግዚአብሔር ከመልካምነቱ ሁሉ ጋር ኢፍትሐዊ ነገሮች ሲሆኑ ዝም ብሎ ይፈቅዳል፡፡ በዚህ ምክንያት ብዙ ሰዎች የፈጣሪን መኖር ይጠራጠራሉ፡፡ እኔም ፍርዱን እንዲገልጽልኝ መጸለይ ይኖርብኛል’ አሉ፡፡
ከዚያች ቀን ጀምሮ መላልሰው ወደ ፈጣሪ ‘’ፍርድህን ግለጽልኝ’ ብለው ደጋግመው ጸለዩ፡፡ ብዙም ሳይቆይ እግዚአብሔር ፍርዱን እንዲህ ገለጠላቸው፡፡
ከሳምንታት በኋላ እንደተለመደው ወደ እስክንድርያ የሦስት ቀን ጉዞ ሊሔዱና ቅርጫታቸውን ሊሸጡ ተነሡ፡፡መንገዱን እንደጀመሩ ድንገት አንድ ወጣት መነኩሴ ወደ እርሳቸው ሲመጣ ተመለከቱ፡፡
‘’አባቴ ይባርኩኝ’
‘እግዚአብሔር ይባርክህ ልጄ’
‘አባቴ ወዴት ይሔዳሉ?’ አለ ወጣቱ መነኩሴ
‘ወደ እስክንድርያ ቅርጫቴን ልሸጥ እየሔድኩ ነው’ አሉት
‘ጥሩ አጋጣሚ ነው አባ እኔም ወደዛ እየሔድኩ ነው’ አለ በትሕትና
‘ጎሽ አብረን እንጓዛለና’ አሉ አባ፡፡ ወጣቱ መነኩሴ ከእጃቸው ሸክማቸውን ተቀበለ፡፡ ጥቂት እንደሔዱ እንዲህ አላቸው፡፡