ሥራን አውቆ መስራት
አንድ ሰው በቅርስ ጥበቃ ተቋም በጥበቃ አገልግሎት ተቀጥሮ እየሰራ ሳለ አንድ ቀን በቅርስ ማዕከሉ ውስጥ ሲንቀሳቀስ ብዙ ዘመናትን (1500ዓመታት) ያስቆጠረ ብርጭቆ ሰበረ።
ተቆጣጣሪው በጣም ተበሳጩ ተቆጡ ጥበቃው ምን እንደሚያበሳጫቸው ግራ በመጋባት ጠየቀ።
ኃላፊው እንዴ ብርጭቆኮ ነው የሰበርከው ብርጭቆው ደግሞ 1500 ዓመት ያስቆጠረ ትልቅ ቅርስ ነው አሉት።
ጥበቃውም ግራ ከመጋባት ውስጥ ወጥቶ ዘና በማለት እንደውም እንዲህ ያረጀ ብርጭቆ እዚህ ምን ይሰራል። እንደውም በአዲስ እተካዋለሁ አይጨነቁ በማለት ሊያረጋጋቸው ሞከረ።
ሰውየውም እጅግ ተበሳጩ። ቁጣቸው ጨመረ።
የሥራ ኃላፊውን ያስቆጣቸው ጥበቃውን ያረጋጋው ጉዳይ ምንድነው?
ጥበቃው ቅርስን ያህል ነገረ ሰብሮ እንዲህ ያረጋጋው ምን አይነት የጤና ሁኔታ ላይ ቢሆን ነው? ትሉ ይሆናል።
እስኪ ስለ እነዚህ ሁለት ሰወች በማውራት ጊዜ ከምናባክን ስለ እያንዳንዳችን እናስብ።
እኛ ምን አይነት ሰወች ነን?
ቁጡ?
ግዴለሽ?
ዝምተኛ?
እስኪ ምን ያስቆጣናል? ምንስ ዝም ያስብለናል? ግዴለሽ የሚያስደርገንስ ምንድን ነው?
ግድየለሽነት የጤናማነት ምልክት አይሆንም ሲወድቅም፣ ሲሰበርም፣ ሲጠፋም ግዴለሽ ከሆንን ጥቅሙ አልገባንም አልያም ችግር አለ።
አንዳንዶች ምናልባት ተስፋ ከመቁረጥ ግድየለሽ ሊሆኑ ይችላሉ። የፈለጉትን ከማጣት፣ በጣም የተማመኑበት ነገር ሲከዳቸው፣ ቃል ሲታጠፍባቸው፣ አምነው ሲከዱ ወዘተ ለግድየለሽነት ምንጭ ሊሆን ይችላል።
ምን ያስቆጣናል?
በተለምዶ እውነተኛ ሰው እውነቱን በምሬት ሲናገር ቁጡ ይባላል። ሌሎች ደግሞ " የሌባ አይነደረቅ መልሶ ልብ አድርቅ " እንዲሉ ጥፋታቸውን ለመደበቅ ይቆጣሉ። ጥቂቶች ደግሞ የግንባራቸው ሥጋ ቅርጽ (መሸብሸብ/ ኮስተር እንደ ማለት) ቁጡ ያስብላቸዋል።
እኔን መሰሎች ደግሞ ስራ ሲበላሽ እና ያለ አግባብ ሲሰራ በተለይ እንደ ቅርስ ጥበቃው ሰራተኛ ለደሞዝ ብቻ ገብተው በሚወጡ፤ ነገር ግን የሚሰሩት ሥራ ዓላማው ካልገባቸው ሥራቸውን በአግባቡ ካልተወጡት ያስቆጣል።
ዝምተኞችን ስንመለከት በአጭሩ ለመፈረጅ ቢያስቸግርም ሥራው ቢሰራ ባይሰራ፣ ቢበላሽ ባይበላሽ ምንም የማይመስላቸው "ያው በገሌ ነው" ብለው እንደ ድመት የሚያስቡ። ተናግሬ ሰው ከሚቀየመኝ ዝም ብዬ ተመሳስዬ አልኖርም ብለው የሚያስቡ ናቸው። እንደዚህ አይነት ለኔ ልዝብ ነው።
ለነገሩ ሁሉም ነገር ስለተናገሩት፣ ዝም ስላሉት አይፈታም አንዳንዴ ሲናገሩ የሚፈታ እንዳለ ሁሉ ዝም ሲሉት የሚፈታም አለና።
እኛ እንደ ተቋም እንደ አገር የተሰጠንን ሥራ የምንሰራው እንዴት ነው? እንደ ጥበቃው ሳይገባን ነው ወይስ እንደ ቅርስ ጥበቃ መስሪያ ቤት ኃላፊ በያገባኛል፣ በኔነት፣ ሥራው ገብቶን ነው?
ምንም አስተያየቶች የሉም:
አስተያየት ይለጥፉ