ማክሰኞ 22 ዲሴምበር 2020

የዳሰሱትም ሁሉ ዳኑ

 "የልብሱንም ጫፍ ብቻ ሊዳስሱ ይለምኑት ነበር፤ የዳሰሱትም ሁሉ ዳኑ።" 

/ማቴ 14፣36/
ደረሰ ረታ
13/04/2013ዓ.ም
$$$$$$$$$=====
በዓለም ላይ ብዙ ሐኪሞችና ብዙ ባለ መድኃኒቶች አሉ፡፡ ሐኪሞቹ መድኃኒት ያዝዛሉ እንጂ ራሳቸው መድኃኒት አይሆኑም፡፡

ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ሐኪምም መድኃኒትም ነው፡፡
እሱ የሥጋና የነፍስ መድኃኒት ነው፡፡ ሥጋ በቊስል፣ ነፍስ በኃጢአት ሲታመሙ ገዳዩን ገድሎ የሚያድነው መድኃኒት ኢየሱስ ክርስቶስ የድንግል ማርያም ልጅ ብቻ ነው፡!!

ሕክምናው ሲያድን ሲፈውስ ጠባሳ አያስቀርም።
ሲያድን ቀስ ብለህ አይደለም የምታገግመው አልጋህን ተሸክመህ ነው የምትሄደው። አስታማሚዎችህ ለርሱ ሲነግሩት ነው አንተ እቤት ሆነህ ከበሽታህ የምትገላገለው። እመን እንጂ ሲምርህ የጠሉህ ሁሉ ናቸው ጠብ እርግፍ የሚሉልህ፣ የገፉህ ያገለሉህ ሁሉ መንገድ ይመሩሃል፣ መንገድ ይለቁልሃል፣ በወንበራቸው ያስቀምጡሃል። ጠረንህን አጥፍቶ የማይታመን መአዛ ያውድሃል።

በእጁ መዳን ከእርሱ ወዲያ አዳኝ ከእርሱ መድኃኒት እንደሌለ ካመንክ እንኳንስ ዳሰኸው ጨርቁን ነክተህ ጥላው ሲያርፍብህ ስሙን ስተጠራ ትድናለህ።

ድንቅ አይበልህ እንኳን እርሱ በእርሱ የሚያምኑ ለሥሙ የሚገዙ እርሱ የሚያደርገውን ከርሱም በላይ ያደርጉ ዘንድ ስልጣን ተሰጥቷቸዋልና። ቅዱሳኑም ያድናሉ በጨርቃቸው እራፊ/ቁራጭ እና በጥላቸው ሳይቀር።

እነርሱ ስሙን ጠርተው ''በኢየሱስ ስም'' ሲፈውሱ አጋንንትን ሲያሳድዱ እርሱ ግን በሃይሉ እና በስልጣኑ በእርሱ ፈቃድ በአባቱ በአብ ፈቃድ በመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ ይህን ያደርጋል።

በዚህ የመጽሐፍ ክፍል ጌታችን መደኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብዙዎችን እያዘነላቸው አድኗቸዋል። አንደኛው ከደቀመዛሙርቱ አንዱ የሆነውን ቅዱስ ጴጥሮስን ሲሆን ሌላኛዎቹ የጌንሴሬጥ ሰዎችን ነበረ። የመጀመሪያ ሰው ቅዱስ ጴጥሮስ የእጁን ተአምራት የቃሉ ትምህርት የተከታተለ ብዙ ልምድ የነበረው ሲሆን የጌንሴሬጥ ሰዎች ይህ እድል ከዚህ ቀደም አልነበራቸውም። ይህንንም እድል ያገኙት ከታንኳ ወርዶ ወደ መንደራቸው ገብቶ ባገኙት ጊዜ ነበረ።

እነዚህንም ከመፈወሱ አስቀድሞ ከቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ቀብር መልስ ብዙዎችን እንደፈወሰ መጽሐፍ ይናገራል።በዚሁ ምእራፍ ቁጥር 14 ላይ ''ወጥቶም ብዙ ሕዝብ አየና አዘነላቸው ድውዮቻቸውንም ፈወሰ።'' ይለናል።

እነዚህ የጌንሴሬጥ ሰወች ማን እንደሆነ ባወቁ ጊዜ በአከባቢው ባሉ በሽተኞች ዘንድ ሁሉ ሰው ላኩ የታመሙትንም ሁሉ በአንድ ሰበሰቧቸው።

ከባንኮክ፣ ከአውሮፓ፣ ከአሜሪካ፣ ከኤሸያ እውቅ የጤና ባለሙያዎች ቡድን ስለመጣ፤ አልያም የኩላሊት፣ የልብ፣ የዲስክ መንሸራተት፣ የውስጥ ደዌ እስፔሻሊስት ቡድን ስለመጣ ብለው አልነበረም የሰበሰቧቸው በደዌ ዳኛ በአልጋ ቁራኛ የተያዙትን ሁሉ እንጂ።ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በበሽታ ላይ ሳይሆን በመፈወስ ላይ ስፔሻላይዝ ያደረገ ነውና።

የተሰበሰቡት ሁሉ፦''የልብሱንም ጫፍ ብቻ ሊዳስሱ ይለምኑት ነበር፤ '' በእርሱ ዘንድ የካርድ የከፈለ የመድኃኒት መግዣ ያለው ጥሩ ዘመድ ያለው ሳይሆን የሚድነው ሁሉም ነው። ለዚህም ነው ማቴዎስ ''የዳሰሱትም ሁሉ ዳኑ'' ያለን።

በዓለማችን፣ በአህጉራችን፣ በአገራችን፣ በከተማችን፣ በመንደራችን፣ በቤታችን ሥንት ሰው አለ በደዌ የተያዘ? ሥንት ሰው አለ መዳን የሚገባው? የጌታን መምጣት ወደ እኛ መቅረብ ሰምቶ ወጥቶ አይቶ ማንነቱን ተረድቶ መፈወሰ፣ መዳን ያለበት፤ ጌታ በደጅ ቆሟል ሁላችንም ከማዳኑ እንሳተፍ።

ጥቂት የማይባሉ አዳኙን አምላክ (ሎቱ ስብሐት) ለስም አጠራሩ ክብር ይግባውና እንደ ፍጡር እያዩት አማላጅ ይሉታል።እንደ ጌንሴሬጥ መንደር ሰዎች ማንነቱን የምንለይበትን አእምሮውን ለብዎውን ፈጣሪ ያድለን።

ወደ ጌንሴሬጥ ከመግባቱ አስቀድሞ ቅዱስ ጴጥሮስንና የተቀሩትን ደቀመዛሙርት አግኝቷቸው ነበረ።

"ሕዝቡንም አሰናብቶ ይጸልይ ዘንድ ብቻውን ወደ ተራራ ወጣ። በመሸም ጊዜ ብቻውን በዚያ ነበረ።
ታንኳይቱም አሁን በባሕር መካከል ሳለች፥ ነፋስ ከወደ ፊት ነበርና በማዕበል ትጨነቅ ነበር።ከሌሊቱም በአራተኛው ክፍል ኢየሱስ በባሕር ላይ እየሄደ ወደ እነርሱ መጣ።ደቀ መዛሙርቱም በባሕር ላይ ሲሄድ ባዩት ጊዜ፡— ምትሐት ነው፡ ብለው ታወኩ፥ በፍርሃትም ጮኹ።ወዲያውም ኢየሱስ ተናገራቸውና፡አይዞአችሁ፥ እኔ ነኝ፤ አትፍሩ፡ አላቸው። ጴጥሮስም መልሶ፡— ጌታ ሆይ፥ አንተስ ከሆንህ በውኃው ላይ ወደ አንተ እንድመጣ እዘዘኝ፡ አለው። እርሱም፡— ና፡ አለው። ጴጥሮስም ከታንኳይቱ ወርዶ ወደ ኢየሱስ ሊደርስ በውኃው ላይ ሄደ።ነገር ግን የነፋሱን ኃይል አይቶ ፈራ፥ ሊሰጥምም በጀመረ ጊዜ፡— ጌታ ሆይ፥ አድነኝ፡ ብሎ ጮኸ። ወዲያውም ኢየሱስ እጁን ዘርግቶ ያዘውና፡— አንተ እምነት የጎደለህ፥ ስለምን ተጠራጠርህ? አለው።
ወደ ታንኳይቱም በወጡ ጊዜ ነፋሱ ተወ። በታንኳይቱም የነበሩት፡— በእውነት የእግዚአብሔር ልጅ ነህ፡ ብለው ሰገዱለት።ተሻግረውም ወደ ጌንሴሬጥ ምድር መጡ።"

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የለመኑት ፈቃዳቸውን እንደፈጸመላቸው ቅዱስ ጴጥሮስ ማሳያ ነው በባህሩ ላይ እንዲራመድ ፈቅዶለታልና፤ ለተራቡት በልተው ጠግበው እስኪተርፋቸው መግቧቸዋል። ማእበሉን ጸጥ አድርጓል። ከዚህ በኃላ ነው የእግዚአብሔር ልጅነቱን ሲያምኑ ማዳኑን ያሳያቸው፤ የዳሰሱትም ሁሉ የዳኑት።

እኛ የአዲስ ኪዳን ትውልድ ሁላችን በአባቶቻችን በኩል ኢየሱስ ክርስቶስን አይተነዋል፣ ዳሰነዋል፣ አብረን በልተን ጠጥተናል፣ ስንቶቻችን መዳን ተደሮጎልናል?

የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ እንዳወቁ የልብሱን ጫፍ ብቻ ሊዳስሱ ይለምኑት ነበረ፤ እግዚአብሔር ዛሬ በአካለ ሥጋ በመካከላችን ቢመላለስ/ ለጸሎት በፊቱ ስንቆም የምንለምነው ምን ይሆን?

መዳን?

ብርና ወርቅ?

ቤትና መኪና?

ስልጣን?

ረጅም እድሜ?

ወይስ ... ምን ይሆን ልንለምነው የምንከጅለው?

ጌታን የአምስት ገበያ ያህል ሰው ይከተለው ነበረ ይላል ቅዱስ መጽሐፍ ነገር ግን ከ120 ቤተሰብ ውጭ ያለው አብዛኛው ገሚሱ ውብ ነበረና ደም ግባቱን ለማየት፣ ገሚሱ ደግሞ የእጁን በረከት እና ተአምራት ለመካፈል እና ለማድነቅ፣ የተቀሩትም ከቃሉ ትምህርት ስህተት ለመቃረም ነበረ።

እኛስ፥
• ክርስቲያን የመሆናችን ዋናው ዓላማ ምንድነው ?
• ለምንድንነው የምንከተለው?
• ግባችን ምንድነው ?
• አሁን የት ነው ያለነው?
• ከክርስትና ዓላማችን አንጻር አካሄዳችን እንዴት ነው?
• እያንዳንዳችን አሁን በዚህ ሰአት በፊቱ ለፍርድ ብንጠራ ምን ይለን ይሆን? ኑ እናንት የአባቴ ብሩካን የምንባል ነን? ወይስ,... ካልሆነ እስክንጠራ ምን እያደረግን ነው? (የንስሐ ፍሬ እናፍራ)
የእግዚአብሔር ልጅ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ (እግዚአብሔር ወልድ) ማዕበሉን ጸጥ ያድርግልን፤ ከውስጥ ከውጭ የሚንጠንን የፍርሃት ማዕበል ቀጥ ያድርግልን። በደዌ ዳኛ በአልጋ ቁራኝነት የተያዙትን ይፈውስልን፤ በዘረኝነት ደዌ በጽንፈኝነት ደዌ ከመመታት እግዚአብሔር ይጠብቀን። በክርስትና ሕይወታችን መጡ ሄዱ፣ ነበሩ የሉም፣ አመኑ ካዱ ከመባል ይሰውረን። ማመናችን፣ እርሱን መከተላችን ቸርነቱ ተጨምሮበት ጽድቅ ሆኖ ይቆጠርልን። እረኛው እንደተመታበት መንጋ ከመሆን ይጠብቀን።

በእዝነ ልቡናችን አይተነዋል፣ ሰምተነዋል፣ ዳሰነዋልና መዳን ይሁንልን።
በቀረው ዘመናችን ንሰሐ ገብተን ለዘለዓለም የማያስጠማውንና የማያስርበውን ሥጋውና ደሙን ተመግበን ለርስቱ ወራሾች ለመሆን ያብቃን።
ይቆየን።
@ deressereta


እሑድ 29 ኖቬምበር 2020

ቢቻላችሁ ከሰው ሁሉ ጋር በሠላም ኑሩ

 ቢቻላችሁ ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ

#######################

ደረሰ ረታ

ክፍል አንድ


የሰው ልጅ በምድራዊ አኗኗሩ ከሰው ጋር ሲኖር አኗኗሩን የሚለካበት ሶስት ዋና ዋና ሥፍራዎች አሉት።

1. በመኖሪያ ቤት እና አካባቢው

2. በመሥሪያ ቤት

3. በቤተክርስቲያን

ከነዚህ የአኗኗር ዘይቤ የወጣ ማንነት የለንም። ምናልባት እውነተኛዎች በረኸኛ መናኒ ባህታውያን ካልሆኑ በቀር፤ የከተማ ባሕታውያንን ሳይጨምር።


ከላይ ለተጠቀሱት እንደ ሰው የምንኖርባቸው ሥፍራዎች ዋና መሰረቱ መቻቻልና መከባበር ናቸው ከዚህ የወጣ አላማ የለውም።


በጥቂቱ ለመዳሰስ ከመጽሐፍ ቅዱስ ባሻገር ሁለት መጻሕፍትን ዋቢ አድርገን ዳሰሳችንን እንቀጥላለን። "ክርስትና በማኀበራዊ ኑሮ" ኅሩይ ስሜ እና ዳዊት ደስታ ያዙጋጇቸው እንዲሁም "በኢትዮጵያ የሃይማኖት መቻቻል አለን?" በብጹዕ አባኑ ሳሙኤል የተዘጋጁ።


መልካም አኗኗር ለመልካም አስተዳደር ትልቅ ሚና ስለሚጫወት አሰናስለን እንመለከታለን።


የሰው ልጅ ከ22ቱ ሥነ ፍጥረት የሚለይበት አንዱና ዋነኛው ነገር በሕግ እና በሥርአት መኖሩ እና አንዱ የሌላኛውን መብት እና ነጻነት አክብሮ መኖሩ ነው።


ከሌላው ዓለም ኢትዮጵያውያንን ለየት የሚያደርገን ባህሪይ እና ባህል አለን። ባህላችን እንግዳ ተቀባይ ሕጋችን ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ ሰውን አክባሪ መሆናችን ነው።


ለነዚህም ተግባራችን እንደ ምሳሌ በቀዳሚነት የምንመለከተው "ኢትዮጵያውያን የሰውን ሰብአዊ መብት በመጠበቅ አንፃር በመልካም አስተዳደር ሂደት በ70 ዓ.ም በጥጦስ አማካኝነት የኢየሩሳሌም ቤተ መቅደስ ሲፈርስና ኢየሩሳሌም ስትወረር በርካታ አይሁዳውያን ፈላሻዎች ኢትዮጵያ ውስጥ መጥተው ኖረው ምንም እንኳን ኢትዮጵያ የክርስትናን ሃይማኖት ገና በ34 ዓ.ም በኢትዮጵያዊው ጃንደረባ አማካኝነት ብትቀበልም (የሐዋርያት ሥራ 8:29) አይሁድ ክርስቶስን የሰቀሉ ናቸው በማለት ማረፊያ አልተከለከሉም።" 


የሰው ልጅን አክባሪነቱ ከመጽሐፍ ቅዱስ አስተምሮ የመነጨ ነው፦ የራሱን ፈቃድ ሲፈጽም የሌላውን ወገኑንም ሆነ ባለጋራውን (ጠላቱን) ጨምሮ ህሊና ጠብቆ የሚኖር ነው። 1ኛ ቆሮንቶስ 8:11 " ሰዎች በአንተ ላይ ሊያደርጉብህ የማትፈልገውን ነገር እንዲሁ በባልንጀራህ ላይ አትፈጽም ሰዎች ሊያደርጉላችሁ የምትሹትን በሙሉ እናንተም እንዲሁ አድርጉላቸው" በሚል መርህ የሚመራ ነው።


ከሕግም አንጻር የእያንዳንዱን ግለሰብ ተፈጥሯዊ እና መሠረታዊ የሆኑትን መብቶች ያከብራል። ለማስከበርም ይጥራል። እነዚህም፦

1. ፖለቲካዊ ነጻነት

2. ማህበራዊ ነጻነት

3. ኢኮኖሚያዊ ነጻነት ናቸው።

ከሕግ አግባብ እነዚህን ሶስት ነጻነቶች በጠንካራ መሠረት ላይ ከታነጹ ሕዝብም አገርም አትናወጽምና።


ለክርስቲያኖች ቅድስት ቤተክርስቲያን ከልደተ ክርስቶስ አስቀድሞ ከሙሴ ሕግ ጀምሮ እስከ አዲስ ኪዳን ሕግ ድረስ ትምህርቷ ፍቅር፣ ሠላም፣አንድነት፣እኩልነት ነው። "ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ" በሚል አስተምሮ ታንጻለች።


ከዚህ በመነሳት የሌሎች አገራት ዜጎችና መሪዎች እምነት ተከታዮች ሳይቀር ይሰደዱባታል፤ ይጠለሉባታልም። የእስልምና እምነት ተከታይ ወገኖቻችን፣ የፖለቲካ መሪው ኒንሰን ማንዴላ፣ ማህተመ ጋንዲ፣ የተለያዩ አገራት ስደተኞች ማሳያዎች ናቸው። በግንባራችን እንጂ በጀርባችን ጥይት አይመታንም ያሉ ጀግኖች አባቶቻችን ይህችን ድንቅ አገር እስከ ሙሉ ክብሯ አስረክበውናል። እኛስ?


ዛሬ ከላይ የጠቅስናቸው ተግባራትና መገለጫችን እየቀጨጩ ይገኛሉ። እኛ ዘመን ጋር ሲደርሱ ለምን ይህ ሆነ?


ዘመኑን ካየን የዘመነ፣ የሰለጠነ፣ በእውቀት የመጠቅንበት፣ በሳይንስና ቴክኖሎጂ የታገዝንበት ሲሆን ደካሞች ነን።


• ከባቢያዊ ግጭቶች በርክተዋል

• ሽብራዊ አመጽ በተለያዩ ሥፍራ ይቀሰቀሳል

• የጦር መሣሪያ ዝውውር በርክቷል

• ዓለም አቀፍ ይዘት ያላቸው በሽታዎች/ወረርሽኞች ተበራክተዋል።

ነገር ግን ይህንን ማስቀረት አልቻልንም። ለምን?


ዲሞክራሲ የብዙሃን የበላይነት የሚረጋገጥበት የአናሳዎች መብቶች የሚከበርበት ሥርዓት ሲሆን ሥልጣንን መሰረት በማድረግ አናሳዎች የበላይነት እየወሰዱ የሚገኙበት ሁኔታ ላይ እንገኛለን። በፖለቲካ ሴራ የብሔር ግጭት፣ የሃይማኖት ግጭት፣ እየተከሰተ ይገኛል። ሲፈተሽ ችግሩ የመልካም የማኀበራዊ ኑሮ አኗኗር ችግር/ውስንነት እንደሆነ ይታመናል። ይህም ተጽዕኖ በመልካም አስተዳደር እጦት ላይ ጠባሳውን ያሳርፋል ብሎም የፍርድ መጓደልን የድሃ መበደልን ያስከትላል። ይህ ሆኖ ሲገኝ እንኳን የዲሞክራሲን መኖር ማረጋገጥ ይቅርና ወጥቶ መግባት በስጋት ይሆናል። እኩልነት ቀርቶ የጥቂቶች የበላይነት ይሰፍናል። የብሔረሰብ እኩልነት፣ የእምነት ተቋማት እኩልነት፣ የባህል እኩልነት፣ የፖለቲካ እኩልነት፣ ኢኮኖሚያዊ እኩልነት፣ ማህበራዊ እኩልነት፣ የአስተዳደር እኩልነት አይኖርም። ልማትና ሠላም አይኖርም።


ስለዚህ ቅድስት ቤተክርስቲያን እና ምእመናን በአንድነት በሃይማኖታዊ እና በማሕበራዊ ተግባራት በብቃት ልትወጣ ይገባታል። ከፖለቲካ አስተዳደር ውጭ የሆነ የራሷ አስተዳደር ሊኖራት ይገባል። ይህ ሊሆን የሚችለው ደግሞ፦

• ራሷ በክርስቶስ ሠላም ውስጥ መኖርዋን ስታረጋግጥ

• መልካም አስተዳደር በውስጧ ሲጎለብት

• የውስጥ ችግሮችዋን በራሷ መፍታት ስትችል፣መከባበር፣ መደማመጥ ሲኖር፣

• ቤተክርስቲያኒቱ ያለባትን ኃላፊነት በግልጽ በማጤን በውስጧ ተሰግስገው ሰማያዊ ሳይሆን ምድራዊ ዓላማ ይዘው የሚጓዙትን ጠርጎ ሲያስወጣ 

• ቤተክርስቲያንን የመጠበቅ ግዴታ የምእመኑም በመሆኑ በክርስትና እምነት አስተምሮ የታነጸ ሲሆንና ተሳትፎአቸውን ይበልጥ በማጎልበት የአሠራር ግልጽነትን በማስፈን ወዘተ ብቻ የሚሆን ነው።

ቤተክርስቲያን ችግሮቿን በራሷ አቅም መፍታት ስትችል መልካም አስተዳደር ይሰፍናል፤ መንፈሳዊነት ይጸናል።


"የእግዚአብሔር ጸጋ እንደ ተሰጠኝ መጠን እንደ ብልሃተኛ የአናጺ አለቃ መሠረትን መሠረትሁ፥ ሌላውም በላዩ ያንጻል። እያንዳንዱ ግን በእርሱ ላይ እንዴት እንዲያንጽ ይጠንቀቅ።" 1ኛ ቆሮንቶስ 3:10


እኛም እንደ ምእመን እንዴት በጥንቃቄ መኖር እንዳለብን እንመለከታለን።

ክፍል ሁለት ይቀጥላል


@deressereta


እኔን ለማግኘት ጽሁፎቼን ለመከታተል ከዚህ በታች የተጠቀሱት ሁሉ ወደ'ኔ ይመሩዎታል።


My Facebook page link (በፌስቡክ ገጽ እንገናኝ)


https://www.facebook.com/deresse2020/


Main facebook account (ዋናው የፌስ ቡክ ገጼ ይቀላቀሉት)


https://www.facebook.com/DeresseReta


Follow me through telegeram (በቴሌግራም ሊከታተሉኝ ከፈቀዱ) ሁሉም ምልከታዬን የማጋራባቸው ማህበራዊ ድረ ገጾች ናቸው።

ሰኞ 23 ኖቬምበር 2020

በአባቴ ቤት እንጀራ የሚተርፋቸው አገልጋዮች ስንት ናቸው?

 በአባቴ ቤት እንጀራ የሚተርፋቸው አገልጋዮች ስንት ናቸው?

ሉቃስ 15: 17

ጌታችን መድኋኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ምድር በተመላለሰበት በዘመነ ሥጋዌው ለሶስት ዓመት ከሶስት ወር አስተምሯል።

እርሱም በሚያስተምርበት ወቅት የአምስት ገበያ ያሕል ሕዝብ ይከተለው ነበር ብሎ መጽሐፍ ይነግረናል።

ከነዚህ የቃሉን ትምህርት ከሚማሩት ከእጁ በረከት ከሚሳተፉት መካከል ገሚሱ ሃጥያተኞች ስለነበሩ ሊከሱት ይከተሉት በነበሩት መካከል ተቀባይነትን አላገኘም ፤ እጅግም አስነቀፈው። እንዴት ሃጢያተኞችን ሰብስቦ ያስተምራል ብለው አሙት። ወንጀሉት።

ክብር ይግባውና ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የነርሱን ትችት ወደ ጎን በመተው ይልቅስ መድሃኒት የሚያስፈልገው ለጤነኞች ሳይሆን ለበሽተኞች እንደሆነ በመንገር ከክፋታቸው ይመለሱ ዘንድ አስተማራቸው። እኔ ሐጥአንን ልጠራ መጣሁ እንጂ ጻድቃንን ልጠራ አልመጣሁም እንዲል ከሃጢያተኞች ጋር ዋለ። እነርሱም አጉረመረሙ። በማጉረምረማቸው ምክንያት ሶስት ምክንያታዊ የሆነ ትምህርት በምሳሌ አስተማረ።

፩ኛ. አንድ ሰው መቶ በጎች ነበሩት ቀኑን ሙሉ በለመለመ መስክ እያሰማራ ከምንጭ ውሃ እያጠጣ ዋለ ሲመሽም ወደ በረታቸው ያጉራቸው ዘንድ ወደ ቤቱ ተመለሰ። ከመሸ ከደከመውም በኋላ አንደኛው በግ እንደጠፋበትም ተረዳ ዘጠና ዘጠኙን በበረት ቆልፎባቸው በጨለማ አንዱን በግ ፍለጋ ወጣ። ያንን በግ እሲኪያገኝ ድረስ በከባድ ድካም ውስጥ ሆኖ ፈለገው። አገኘውም። እጅግም ደስ አለው። ጎረቤቶቹንም ጠርቶ አንዱ በጌ ጠፍቶ ነበር ተገኝቷል ከኔ ጋርም ደስ ይበላችሁ አላቸው።

፪ኛ. አንዲት ሴት አሥር ሳንቲሞች (ድሪም) ነበሯት ከአሥሩ ሳንቲሞች አንዱ ጠፋባት መብራት አብርታ ፈለገችው፣ የቤቱንም ቆሻሻ ጠርጋ ወደ አንድ ጥግ ሰበሰበች ፈለገችው አገኘችውም እርሷም እንደ ባለ በጉ ጎረቤቶቿን ጠርታ አንድ ድሪም ጠፍቶብኝ ነበር አገኘሁት ከኔ ጋር ደስ ይበላችሁ አለቻቸው።

፫ኛ. አንድ ባለጸጋ ሰው ሁለት ወንድ ልጆች ነበሩት ይህ ሰው የሃብቱ ወራሾች እነዚህ ልጆች ብቻ ነበሩ፤ ይሁን እንጂ ሐብት የሚወረሰው አባትየው ሲሞት ነው። ትንሹ ልጅ ከአባቱ የሚደርሰውን ሐብት ንብረት ተመኘ አባቱንም ቢያይ ቢያይ አይሞትም እጅግም ቸኮለ። ስለዚህ ወደ አባቱ በመሄድ የሚደርሰውን አንድ ሶስተኛውን ይሰጠው ዘንድ ጠየቀ አባቱም ኩፍሎ ሰጠው። ሐብቱንም ይዞ ወደ አንድ እሩቅ አገር ሄደ። በልቶ ጠጥቶበት ከጋለሞታዎችም ጋር አባክኖት በአጭር ጊዜ ጨረሰው።

ገንዘቡ ሲያልቅ ጓደኞቹም ከአጠገቡ አንድ በአንድ እየሸሹት ብቻውን ቀረ። ሀብቱም አልቆ ባዶ እጁን ቀረ፣ ተራበ፣ ተጠማ፤ መጠለያም አጣ። ወቅቱም በአገሩ ድርቅ ተከስቶ ነበርና ረሐብ ሆነ። ያስጠጋው ዘንድ ወደ አንድ ሰው ዘንድ ሄደ። እርሱም አስጠጋው ሰውየው ላስጠጋበት ዋጋ ይሆነው ዘንድ አሳማዎቹን እንዲጠብቅለት አደረገው።

አሳማ እጅግ አስጠሊታ ከመሆኑ የተነሳ እስራኤላውያን አሳማ መጠበቅ አይወዱም። የነካው ይረክሳል፣ ሥጋውንም አይበሉትም። ይህ የባለጸጋ ሰው ወጣት ልጅ ውሎና አዳሩ እጅግ በሚገማ የአሳማ በረት ውስጥ ሆነ። ወቅቱ ድርቅ እና ረሐብ የነበረበት ወቅት ስለሆነ እጅግ ከመራቡ የተነሳ አሳማው ከሚበላው ይመገብ ዘንድ ይመኝ ነበር።
ርሐብና እና ጽም እጅግ ጸናበት። ችግርም ጸናበት።
በስተ መጨረሻ ወደ ልቡም ተመለሰ። እንዲህም አለ፦ በአባቴ ቤት እንጀራ የሚተርፋቸው አገልጋዮች ስንት ናቸው? ተነስቼ ወደ አባቴ ቤት እሄዳለሁ አባቴ ሆይ የሚገባኝን ሁሉ ወስጄ ሄጃለሁ ከእንግዲህ ልጅህ ልባል አይገባኝም ከአገልጋዮችህ እንደ አንዱ አድርገኝ እለዋለሁ። ብሎ ወደ አባቱ ዘንድ ሄደ። አባቱም በርቀት ተመለከተው እጅግም አዘነለት ወደ እርሱም ሮጦ አቀፈና ሳመው።
ልጁም አባቴ ሆይ ልጅህ ልባል አይገባኝም አለው።
አባትም ከሁሉ የሚበልጠውን ልብስ አምጡና አልብሱት፣ ለእግሩ ጫማ ስጡት፣ የሰባውን ፊሪዳ አምጡና እረዱለት እንብላ እንጠጣ ደስም ይበለን። ልጄ ሙቶ ነበር ሕያው ሆኗል፣ ጠፍቶ ነበር ተገኝቷል፤ አለ።
እቤት የነበረው፣ ከአባቱ ሐብት ንብረት ያልተካፈለው ትልቅ ልጅ እርሻ ዉሎ ወደ ቤት ሲመጣ ከቤታቸው ቅጽር ድምጽ ሰማ፣ ያልተለመደ ድምጽ ነው የዘፈን ድምጽ፣ የደስታ ድምጽ የምስራች የያዘ ድምጽ፣ እኛ ቤት ምን ተፈጠረ? ምንስ ክስተት ተከሰት? እኔ ከቤት ከወጣሁ እኔ የማላውቀው ነገር ምንስ ተፈጠረ ብሎ ጠየቀ፤ ከጎረቤትም ልጅ መጣና ወንድምህ ነው አለው።

ወንድሜ ምን ሆነ?
ወንድሜስ ከዚህ የት አለ? ብሎ ጠየቀ።

የጠፋው ወንድምህ ተገኝቷል፤ አባትህም ተደስቷል። ለወንድምህ መምጣት በቤታችሁ ትልቅ ደስታ ሆኗል። አባትህም ትልቁን ፊሪዳ ለወንድምህ አርዶለታል። አዲስ ልብስም አልብሶታል። ለጣቱም ቀለበት አጥልቆለታል ብሎ ወሬውን አደረሰው።

ወንድሙም እጅግ አዘነ፣ እኔ በዚህ ቤት ስኖር ሥጥር ሥግር አንዳች ቀን ትልቅ እና የሰባ ፊሪዳ አይደለም ግለግል እንኳን ታርዶልኝ አያውቅም፣ አዲስ ልብስ እና የጣት ቀለበት አልተገዛልኝም። ሐብት ንብረቱን ተካፍሎ ቤቱን ጥሎ የሄደን ልጅ ተመልሶ መቀበሉ ስለምን ነው በማለት አኮረፈ ወደ ቤትም አልገባም አለ።

አባቱም ስለ ትልቁ ልጅ ተጨነቀ ሊያግባባውም ሞከረ። ስለ ጠፋው ልጁ/ወንድሙ መገኘት ሊነግረው ሞከረ።

ትልቅ ልጅ፦ ልጅህ ሲመጣ የሰባውን ፍሪዳ አረድክለት፣ ለጣቱም ቀለበት አጠለክለት፣ አዲስ ልብስም እንዳለበስከው ሰማሁ ... እኔ እስከ ዛሬ እንደ ባሪያ ሳገለግልህ ነበር አንድም ቀን ለእኔ እና ጓደኞቼ አንዲት ጠቦት አላደረክም ገንዘቡን ከጋለሞታዎች ጋር ሲበትን ለኖረው ልጅህ እንዴት እንደዚህ ታደርግ ዘንድ ልብህ ፈቀደ አለው።

አባትም ልጄ አንተ እስከ ዛሬ ከኔ ጋር ነበርክ የእኔ የሆነው ሁሉ ያንተ ነበር፤ ነገር ግን ይህ ወንድምህ ( ትልቅ ልጅ ወንድሙን ስለ ተናደደበት አባቱን ልጅ አለው አባት ግን ወንድም በማለት አስታወሰው) ሞቶ ነበር ሕያው ስለሆነ ጠፍቶ ነበር ስለተገኘ ደስ ሊለን ሐሴትም ልናደርግ ይገባል አለው።

ከላይ በተጠቀሱት ምሳሌዎች የጠፉ ሶስት ነገሮችን ተመልክተናል።
1. በመጀመሪያ በግ ጠፋ
2. በመቀጠል ድሪም (ሳንቲም) ጠፋ
3. በስተ መጨረሻ ሰው ነው የጠፋው
እግዚአብሔር በሉቃስ ወንጌል ምእራፍ 15 በመጽሐፍ ቅዱስ የሚገኙትን ሁሉን ጠቅልሎ ሊይዝ በሚችል መልኩ ያስተማረበት የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ነው። እዚህ የተጠቀሱት ምሳሌዎች ሳይቀር በጣም ወርቃማ ምሳሌዎች ናቸው።

ይህ የትምህርት ክፍል ከመደነቁ ባሻገር በሕይወታችን ውስጥ የሚያሳየን ትልቅ ምሥጢር አለ። ይኸውም አንድ ክርስቲያን ከቤተክርስቲያን እንዴት አድርጎ እንደሚጠፋ፣ ሕይወቱ እንዴት እንደሚቅበዘበዝ፣ እግዚአብሔር እንዴት እንደሚፈልገን፣ እንዴትስ ወደ እግዚአብሔር ቤት እንደምንመለስ ቁልጭ አድርጎ ያሳየናል። (ጽሑፉ ረዘመ እኔ ረጅም ጽሑም አልወድም የምትል ከሆነ ከዚህ ምሥጢር አትሳተፍም)

በምሳሌው በመጀመሪያ የጠፋው እንስሳ ነው፣ በመቀጠል የጠፋው እቃ ሲሆን በመጨረሻም የጠፋው ሰው ነው።

• ሰወች ስንጠፋ ሰው ሆኖ የማይበድል እንጨት ሆኖ የማይጨስ የለም እያልን እንጠፋለን።
• አንዳንዴ ከሰውነት ክብር ዝቅ ብለን የእንስሳ ተግባር ስንከውን እንገኛለን። (አውሬያዊ ጭካኔ ይታይብናል።)
• አንዳንዴ ከእንስሳት ዝቅ ብለን እቃ የምንሆንበት አጋጣሚ አለ። እንስሳት በዘር አይጣሉም እኛ ግን ከነርሱ አንሰን በዘር እንጣላለን። አንበሳ ምን ቢከፋ ምን ቢርበው አንበሳን አይበላም እኛ ግን እርስ በርስ እንበላላለን። የማንጠቅም ርካሽ የምንሆንበት ጊዜ አለ።
እግዚአብሔር በነዚህ ምሳሌ እንደምንመለከተው ሊያስተምረን የፈለገው እንደ እንስሳም ብትጠፉ እፈልጋችኋለሁ፣ እንደ እቃም ብትጠፉ እፈልጋችኋለሁ፣ እንደ ሰውም ብትጠፉ እፈልጋችኋለሁ ሲል ነው። አንዳንዴ ከሰውነት ክብር ወርደን እንደ እንስሳ የምንሆንበት ጊዜ አለና። " ሰው ክቡር ሆና ሳለ እንስሳትን መሰለ" እንዲል። ከእንስሳም ዝቅ ብለን በእቃ ልክ ስንገኝ እንደሚፈልገን ያጠይቃል።

በጠፉት ሶስት ምሳሌዎች በመጀመሪው ላይ ፈላጊው እረኛ ነው፣ ሁለተኛ ላይ እናት ነው፣ በሶስተኛው ላይ አባት ነው።

የሁላችን አባትም እናትም የሆነ እግዚአብሔር አምላካችን ነው። "አባታችን ሆይ " በሉ ብሎ እንዳስተማረን። ሊቃውንቱም እግዚአብሔር እናት እና አባት ብቻ ሳይሆን አያታችንም ነው ይሉናል።

ለዚህም ምሳሌ ሲጠቅሱ እንዲህ ይላሉ፦

እግዚአብሔር ራሱን በብዙ ምሳሌ እንዲመስል (በዶሮ በወፍ እየመሰለ እንዲያስተምር) ዶሮ ጫጩቶቿን ከእቅፎቿ በታች እንድትሰበስብ እንዲሁ የአለሙ መድህን እግዚአብሔር እኛን ይሰበስበናል።

ዶሮ ለጫጩት እናትም አያትም እንደሆነች እርሱ እናታችንም አያታችንም ነው። ምድራዊ እናት እና አባት በዋልንበት አይዉሉም በአደርንበት አያድሩም። እግዚአብሔር ግን በዋልንበት የሚውል ባደርንበት የሚያድር መልካም አባታችን/እረኛችን ነው። " እግዚአብሔር እረኛዬ ነው የሚያሳጣኝ የለም በለመለመ መስክ ያሳድረኛል በእረፍት ዉሃ ዘንድ ይመራኛል" እንዲል

እረኛ በጎቹን ቀን ከጠበቀ ሌሊት ይተኛል፣ እግዚአብሔር ግን እኛን ሲጠብቅ አይተኛም። "ሕዝቤን የሚጠብቅ አያንቀላፋም" ይላልና።

እረኛ በጉን ጠብቆ ካሳደገ በኋላ አርዶ ይበላዋል አልያም አርደው ለሚበሉት አሳልፎ ይሸጠዋል። እረኛችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ስለ መልካም እረኝነቱ በሰላሳ ብር ስለ በደላችን ተሸጠ። ተላልፎ ተሰጠ። ኢየሱስ ክርስቶስ በጎቹ የሸጡት እረኛ ነው።

እረኛው በጎቹን አርዶ ሲበላ የእኛን እረኛ ግን እኛ ተሰልፈን በቤተክርስቲያን ምሥጢር አርደን እንበላዋለን። የእረኛ ፍቅር እስከ ማረድ ነው። የእኛ እረኛ ግን ነፍሱን ስለ በጎቹ አሳልፎ እስከ መስጠት ነው።

ነገር በምሳሌ እንዲሉ ምሳሌው እንዲህ ነው፥

እረኛው እግዚአብሔር ነው
መቶ በጎች የተባሉት ሰውና መላእክት ናቸው።
አንድ በግ ጠፋ የተባለው ሰው ነው ዘጠና ዘጠኙ ነገደ መላእክት ናቸው።

ይሕ ምሳሌ የማዳኑን ሥራ ነው የሚያሳየን።

እኛ ሰዎች እንዴት ከቤተክርስቲያን እንጠፋለን ካልን፥

1ኛ. እንደ በግ ነው፦ በግ የሚጠፋው አውቆ አይደለም። የሚበላው ሣር የሚጠጣው ውሃ ፈልጎ የፊት የፊቱን ብቻ እያየ ሳያስበው ነው። እኛም ከቤተክርስቲያን ርቀን የሄድነው፣ ጠፍተን የሰነበትነው እንዲሁ እንደ በጉ ነው ሳናውቅ እንደምንጠፋ ሳናውቅ/ የጸናን ስለሚመስለን/የቆምን ስለሚመስለን ነው።

በጉ ስለሚበላ ስለሚጠጣ ሲል እንደ ጠፋው እኛም በእንጀራ ጉዳይ ከቤተክርስቲያን የጠፋን አለን። (ቢዚ ነኝ፣ ሥራ ይበዛብኛል፣ አይመቸኝም፣ እቤት ስገባ ይመሻል፣ ጠዋት ከቤት የምወጣው በሌሊት ነው፣ ቅዳሜና እሁድ ይደክመኛል፣ ማህበራዊ ጉዳይ አለብኝ፣ ቤተሰብ አስተዳዳሪ ነኝ፣ ልጅ አሳድጋለሁ ወዘተ እያልን በሰበብ ጠፍተናል። ከአንዱ ሥራ ሌላ ሥራ፣ ከአንዱ ትምህርት ሌላ ትምህርት እያልን ላንመለስ ሄደናል።)

የዚህ በግ ሳር መብላት ውሃ መጠጣት ክፋት የለውም ዋናው ችግር ከበረቱ መራቁ እንጂ። የኛም ችግር ሥራ መሥራታችን፣ ትምህርት መማራችን፣ ቢዚ መሆናችን አይደለም። ከቤተክርስቲያን መራቃችን እንጂ። በጉ ከበረት እየራቀ ሲሄድ ተኩላ ይበላዋል ወይም ሌባ ይሰርቀዋል የእኛም ከቤተክርስቲያን ያርቀናል ወይም በመናፍቃን ያስነጥቀናል/ያስክደናል፤ አልያም በዲያቢሎስ እንጠቀጥቃለን።

በጉ ሲጠፋበት እስኪያገኘው ድረስ ፈለገው፤ ሲያገኘውም እጅግ ደስ አለው አንስቶም በትከሻው ተሸከመው ይላል እግዚአብሔር አንድ አዳም ቢበድል ቢጠፋ እስኪያገኘው ድረስ እጅግ አሰልቺ በሆነ ትእግስት በሚጨርስ ፍለጋ ውስጥ አገኘው። ከቤቱ የጠፋን እኛንም እግዚአብሔር እስኪደክመው ሳይሆን እስኪያገኘን ድረስ ይፈልገናል። ለዚህም ነው በቃሉ ብርሃንነት ሊፈልገን በአደባባዩ አልገኝ ስንለው በማህበራዊ ሚድያ ሳይቀር ቃሉ እንዲነገረን ያደረገው። ለዚህኮ ነው ወደ እርሱ መሄድ ሲገባን ወደኛ የመጣው። እምቢ አሻፈረኝ ስንለው በመሰልቸት ሳይተው ወደ በረቱ እስክንመለስ ድረስ እየፈለገን ያለው።

አስቀድመን እንዳየነው የጠፋው በግ ሲገኝ በቤቱ ደስታ ሆነ በትከሻውም ተሸክሞ ወደ ቤቱ ወሰደው ሳያውቅ ነውና የጠፋውና። እኛንም የአለም መድሃኒት ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቤቱ ስንመለስ በዘጠና ዘጠኙ ነገደ መላእክት ዘንድ ደስታ ይሆናል ሳናውቅ ነውና የጠፋነው።

አውቆ ከመጥፋት ይሰውረን።

አሁን በዚህ ሰአት ይህን ቃል እንድናነብ ያደረገን፣ በቤቱ የሰበሰበን፣ በቤቱ እንድንኖር ያደረገን እኛ ፈቅደን መጥተን አይደለም እርሱ በፍቅር በትከሻው ተሸክሞን አምጥቶን እንጂ። ይኸን ጊዜ ከጽሁፍ ርዝመት ያልጨረሱት አሉ። አንተ እየጨረስክ ያለኸው በፍቅር በደስታ በትከሻው ተሸክሞህ ስለመጣ ነው እንጂ አንተ ከቃሉ ፍቅር ስላለህ አንተ ስለምትሻል አይደለም። እኛማ አለም እንዴት ሰነበተች?፣ የፖለቲካው ጡዘት የት ደረሰ?፣ ዋንጫውን ማን በላ?፣ ወዘተ የሚለው ሚድያ ላይ ነበርን። አሁን እዚህ የተገኘነው መርጠን አይደለም ተመርጠን እንጂ። ፈቅደን አይደለም ተፈቅዶልን እንጂ።
እኔኮ እፈልጋለሁ ለመምጣት ግን አይመራኝም እንላለን ዛሬ መርቶ ያመጣን እግዚአብሔር ነው የኛ ብርታት አይደለም። " በምህረትህ ብዛት ወደ ቤትህ እገባለሁ" እንዲል። እየፈለጉ ያልመጡትን እግዚአብሔር ያምጣልን። የመጣነውን በቤቱ ያለነውን አያርቀን።ያጽናን።

ክፍል ሁሉት ይቆየን።

ሐሙስ 29 ኦክቶበር 2020

ሁለት ምርጫ አለን

 ሁለት ምርጫ አለን

ደረሰ ረታ
19/2/2013

ሕጻናት ንጽሕ ናቸው፤ ለዚህም ነው ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋእለ ሥጋዌው ስለ መንግሥተ ሰማያት ሲያስተምር " እንደ ሕጻናት ካልሆናችሁ የእግዚአብሔርን መንግሥት አትወርሱም" ሲል ያስተማረው።

ሕጻናት:-
ከእናት እና ከአባታችሁ ማንን ትወዳላችሁ?
ከከረሜላ እና ከቸኮሌት የቱን ትመርጣላችሁ?
ከእናት ከአባት ከእህት ወንድማችሁ ማንን የበለጠ ትወዳላችሁ?
ወዘተረፈ
ተብለው ለምርጫ ሲጠየቁ
እናቴንም አባቴንም፣
ከረሜላም ቸኮሌትም፣
እናቴንም አባቴንም እህት ወንድሜንም ይሏችኋል።
ደግማችሁ ከሁለቱ አንዱን ምረጡ ብላችሁ ስታስገድዷቸው ሁሉቱንም/ሁሉንም ብለው ድርቅ ይላሉ። ሕጻናት ንጽህ ናቸውና። እምቢ ብትሏቸው እንኳን እምቢ ተጣልቼሃለው/ሻለሁ ብለው ጥለዋችሁ ይሄዳሉ አንዱን ብቻ አይመርጡም። ሌላኛውን ማጣት አይፈልጉምና።

እኛስ?

ከገንዘብና ከሰው፣
ከእምነትህ እና ከፖለቲካ፣
ከአገርህ እና ከጥቅምህ፣
ከወንድምና ከእህትህ፣
ከሥራህ እና ከሃላፊነትህ፣
ወዘተረፈ
ተብለን ስንጠየቅ ምላሻችን ብለን የምንሰጠው ይበልጣል ብለን ያሰብነውን አንዱ ነው እንጂ ምንም አይነት ማስረጃ አግኝተን አይደለም።ተልቀናል/አድገናል ብለን ስለምናስብ ስሌት ( calculation) ውስጥ እንገባለን።

አለማወቃችን ግን ከልጆች የዋህነት እና የልብ ንጽሕና ስለማይበልጥ ምርጫችን ስሕተት ይኖርበታል። በምሳሌ ስንመለከት ጥያቄው ከእናት እና ከአባት ለመምረጥ ምን መስፈርት ተቀምጦልን ነው አንደኛቸውን የመረጥነው? ከገንዘብ እና ከሰው እንዴት ልንመርጥ ቻልን? ሁለቱን አንድ የሚያደርጋቸው ምን መለኪያ ተገኝቶ ነው? እነዚህም እስኪ ይቅሩና ማን ነው አንዱን ብቻ ምረጡ ያለን? እንዲሁ ከሁለት ነገሮች መካከል አንዱን መምረጥ በምርጫ ሕግ ሥለምናውቅ እንጂ።

ሕጻናት ግን በቅንነት እና በፍቅር ሁለቱንም ይመርጣሉ።

አንዳንዶች ሰውን ከገንዘብ፣ ገንዘብን ከሰው ጋር ያነጻጽሩልንና አንዱን ከፍ አንዱን ዝቅ አድርገው በግድ አንዱን ምረጥ ይሉናል። ሁለቱም አስፈላጊነታቸውና መለኪያቸው ለየቅል ነውና።

ስለዚህ እንደ ሕጻናት ስንሆን ሁሉም የኛ ይሆናል። በ"እውቀት" ውስጥ ያጣነውን በየዋህነት እና በቅንነት ውስጥ ሁለቱንም እናገኘዋለን።

ሕይወትን በስሌት መኖር ሐጥያት ባይሆንም ቅሉ በየዋሕነት ሁለቱንም መምረጥ ግን ብልሕነት ነው ሁለቱንም ያስገኘናል እንጂ አያሳጣንም።

ገንዘብንም ሰውንም ይዞ መኖር ይቻላልና።

ከገንዘብ እና ከጤና ምረጡ ለሚሏችሁ ገንዘብንም ጤናንም እንደምትመርጡ ንገሯቸው።

አገርና እምነትን ለሚያስመርጧችሁ ሁለቱንም እንደምትመርጡ ንገሯቸው።

ከፖለቲካ እና ከመንፈሳዊነት ሲያስመርጧችሁ ሁለቱም ምርጫችሁ እንደሆኑ አረጋግጡላቸው።

የሰውን ልጅ ትክክል የሚያደርገው ከሁለት አንዱን መምረጡ ሳይሆን የመረጠውን እንዴት ይጠቅምበታል የሚለው ነውና። አንዳንዶች ገንዘብ ሃጢያት እንደሆነ ያወሩናል ድሕነት ጽድቅ ነው ወይ? ብዬ እጠይቃቸዋለሁ።

እንደዛ ቢሆን ኖሮ ድሆች ሁሉ ጻድቅ ሐብታም ሁሉ ሐጥአን በሆኑ ነበር። ነገር ግን እውነታው ሐብትን በአግባብ መጠቀም አለመቻል ነው ጽድቁም ሐጥያቱም።

ስለዚህ ሁላችንም ሁለት ምርጫ አለን። አንድም ሁለቱን አንድም ሁሉንም መምረጥ።

#######$$#######$$$#######

እኔን ለማግኘት ጽሁፎቼን ለመከታተል ከዚህ በታች የተጠቀሱት ሁሉ ወደ'ኔ ይመሩዎታል።

My Facebook page link (በፌስቡክ ገጽ እንገናኝ)

https://www.facebook.com/deresse2020/

Main facebook account (ዋናው የፌስ ቡክ ገጼ ይቀላቀሉት)

https://www.facebook.com/DeresseReta

Follow me through telegeram (በቴሌግራም ሊከታተሉኝ ከፈቀዱ) ሁሉም ምልከታዬን የማጋራባቸው ማህበራዊ ድረ ገጾች ናቸው።

https://t.me/deressereta

ከአሥር አመት በላይ ከ50ሺ በላይ አንባቢዎች ያሉት መጦመሪያም አለ።

www.deressereta.blogspot.com 

ረቡዕ 28 ኦክቶበር 2020

ባለሁበት አከባቢ መኖሬ እንዲታወቅ እፈልጋለሁ።

 ባለሁበት አከባቢ መኖሬ እንዲታወቅ እፈልጋለሁ።


ደረሰ ረታ
18/2/2013

ፍቅር ቃላት ብቻ ሳትሆን መስዋእትነትን፣ ክርስትና ምኞት ሳትሆን ሕይወት ናትና መኖርን፣ ማድረግን፣ ትሻለች። የአገር እና የቤተ እምነቶች ጥቃት፣ የክርስቲያኖችን እና የሙስሊሞች ስደትና ሞት፣ የአንድነታችን መላላት እየተመለከትን እንዲህ ቢሆን ኖሮ፣ እንዲህ ባይደረግ ኖሮ፣ እያልን ከመመኘት ባለፈ በተግባር የተፈተሸ፣በአርአያነት የተሞላ ማንነት፣ ፍቅርና ሕይወት ይፈልጋል።

ስለዚህ ባለን አጋጣሚ ሁሉ በተሰጠን እድሜና ጤና በየአጥቢያችን፣ በተለያዩ መንፈሳዊ ማህበራት፣ ተሰባስበን በያለንበት የተለያዩ ሕብረቶች በመሳተፍ መንፈሳዊነታችንን መገንባት፣ አገልግሎትን ማበርከት፣ አብያተ እምነትን እና ምእመናንን መርዳት፣ ወዘተ ይጠበቅብናል።ከአንድ ሁለት ይሻላልና።

አንዳንዶቻችን ከንፈር ስንመጥ እና ነገሮች አቅጣጫቸውን እንዲስቱ የተነሱበትን አላማ ይበልጥ እንዲያሳኩ ከማራገብ የዘለለ ፋይዳ የለንም።

አንዳንዶች ደግሞ አይተው፣ ሰምተው፣ ስሜቱን ተገንዝበው ዝምምምም የሚሉ አሉ። አይጠቅሙ አይጎዱ።

ነገር ግን ይህቺን አገር ወደፊት ለማስቀጠልም ሆነ ከጉዞዋ አደናቅፈው ወደኋላ ከሚያስቀሯት ይልቅ አፋቸውን ለጉመው ዝምታን በሚመርጡት ነው። ከአጥፊዎች ይልቅ የ"ገላጋዮች" ቁጥር እጅጉን ይልቃልና።

በልማትም ይሁን በጥፋቱ የሚሳተፉ፣ በማሳደድም ይሁን በማፈናቀል፣ በመግደልም ይሁን አካል በማጉደል፣ በመቀማትም ይሁን ባለማገላገል ከሚሳተፉት እንደ አገርም ሆነ እንደ መንደር ቁጥራቸው የሚበዛው አያገባንም ብለው ዝም ብለው የተቀመጡት ናቸው።

አገርም ሆነ ሕዝቡ አብዝቶ የሚጎዳውም ይሁን የሚጠቀመው ባጥፊዎች ወይም ባልሚዎች ሳይሆን በብዙ ዝምተኞች ምክንያት ነው።

አብዛኛው ሰው በመኖሪያ ቤቱ፣ በመኖሪያ ሰፈሩ፣ በመሥሪያ ቤቱ፣ በእድር በማህበሩ፣ በእቁብ በስብሰባው፣ መኖሩ አይታወቅም፤ እርሱም ብቻ አይደለም ምንም አስተዋጽኦ አያደርግም።ስለዚህ ሰዎች መኖሩን አያውቁትም። በክፉም በደግም ሥሙ አይነሳም።

እኔ ግን ባለሁበት አካባቢ፣ ባለሁበት ማህበረሰብ፣ ባለሁበት መሥሪያ ቤት፣ ባለሁበት እቁብና እድር ትልቅ ተጽዕኖ ፈጣሪ መሆን ቢያቅተኝ መኖሬ እንዲታወቅ እፈልጋለሁ። ኖሬ ከሌሎች በተሻለ ባልጠቅምም የለም በሚባል ግን በሥሜ ችግር እንዲፈጸም፣ በዝምታዬ ብዙዎች እንዳይጎዱ ስለምፈልግ።

እስኪ በየስብሰባው በዝምተኞች ችግር በጥቂት ተናጋሪዎች ስንት ውሳኔ እንዳለፈ፣ ስንት ጥፋት እንደተፈጸም፣ ስንት ሐብት እንደተመዘበረ፣ ስንት ሕይወት እንደተቀጠፈ፣ ስንት ትዳር እንደፈረሰ፣ ስንት ቤተሰብ እንደተበተነ፣ ስንትና ስንት ውድቀት አገሪቱ ላይ እንደ ደረሰ።

ከእድር ስብሰባ እስከ ፓርላማ ስብሰባ ስንት ዝምተኞች ስንት መኖራቸው እንኳን የማይታወቁ ሰዎች ዋጋ እንዳስከፈሉን የደረሰብን እናውቃለን።

ባላችሁበት ስፍራ፣ የሃላፊነት ቦታ፣ የተወከሉበት መድረክ፣ በተሰጠዎት አደራ፣ ... ብናገር ባልናገር ባደርግ ባላደርግ በማለትዎትና ዝም በማለትዎ ስንቶች ዋጋ ከፍለዋል? አገር ዋጋ ከፍላለች?

ትልቅ ቦታ አይሁን ተቀጥረውም ይሁን ተመርጠው፣ ተወክለውም ይሁን በበጎ ፈቃደኝነት በሚያገለግሉበት ቦታ የርስዎ ድርሻ ትልቅ እንደሆነ ያምናሉ? ሚሊዮኖች ከጀርባዎ እንዳሉ ይገነዘባሉ? የርስዎ ዝምታ፣ የርስዎ ዝንጋታ፣ የርስዎ አይቶ ማለፍና ሰምቶ መቻል ዋጋ እንደሚያስከፍል ምን ያህል ይሰማዎታል?

ባሉበት ቦታ የርስዎ እንዳሉ/መኖርዎ መታወቅ ማድረግ፣ ተጽእኖ መፍጠር፣ ድርሻዎትን በአግባቡ መወጣት፣ ... የምርጫ ጉዳይ አይደለም። የግዴታ ጉዳይ እንጂ።

ብዙዎች እያሉ እንደሌሉ ተቆጥረዋል፣ ብዙዎች ድምጸ ተአቅቦ አድርገዋል፣ ብዙዎች እስከ መፈጠራቸው ተዘንግተዋል፣ ... በነዚህ ምክንያት አገርና ሕዝቡ ዋጋ እየከፈሉ ነው።

እኔ ባለሁበት አከባቢ መኖሬ እንዲታወቅ እፈልጋለሁ። እርስዎስ?

#$$$#####@@@@####$$$$$&&&&$$#

እኔን ለማግኘት ጽሁፎቼን ለመከታተል ከዚህ በታች የተጠቀሱት ሁሉ ወደ'ኔ ይመሩዎታል።

My Facebook page link (በፌስቡክ ገጽ እንገናኝ)

https://www.facebook.com/deresse2020/

Main facebook account (ዋናው የፌስ ቡክ ገጼ ይቀላቀሉት)

https://www.facebook.com/DeresseReta

Follow me through telegeram (በቴሌግራም ሊከታተሉኝ ከፈቀዱ) ሁሉም ምልከታዬን የማጋራባቸው ማህበራዊ ድረ ገጾች ናቸው።

https://t.me/deressereta

ከአሥር አመት በላይ ከ50ሺ በላይ አንባቢዎች ያሉት መጦመሪያም አለ።

www.deressereta.blogspot.com 

ማክሰኞ 27 ኦክቶበር 2020

ከ"ሚሰበር ይሰንጠር"

 ከሚሰበር ይሰንጠር

ደረሰ ረታ
17/2/2013

አንዳንዶች ከትህትናም ይሁን ከስንፍና በተለይ መንፈሳዊ ነገሮችን ላለማድረግ እኔ ይቅርብኝ፣ እኔ ለዚህ ነገር ብቁ አይደለሁም፣ ከኔ የተሻሉ ሌሎች አሉ፤ በማለት ወደኋላ ሲያፈገፍጉ ይታያሉ።

ይሕ ተግባር ንሰሐ ለመግባት፣ ትዳራቸውን በመንፈሳዊ መንገድ ለመጀመር፣ በአገልግሎት ለመሳተፍ፣ ከዚህም አልፈው ስለአገራዊ ጉዳይ እነርሱን እንደማይመለከት ይሰማቸዋል። አገር የምትመራው በፖለቲከኞች ብቻ ይመስላቸዋል፤ ቢሆንም ቅሉ ፖለቲካን ይፈሩታል ይሸሹታልም።

ነገር ግን የእምነት ተቋምም ይሁን አገር ባላዋቂዎች ባህር ላይ እንዳለች ታንኳ ስትናጥ እነርሱም በዚህ ጉዳይ ጤናቸውን ያጣሉ። ደስታቸውም ሆነ ሰላማቸው ከሁለቱ ጋር በጥብቅ የተቆራኘ ነውና።

ስለዚህ:-

ጸሎት ከሚቀር በዝንጉእ ልቡናም ቢሆን ይጸለይ፣
ጾም ከሚቀር ንሰሐ ባንገባም ምጽዋት ባንሰጥም እንጹም፣ በጥቂቱ ስንታመን በብዙ የሚሾም ፈጣሪ ያበረታናልና።

ሥራችን ውጤት አልባ፣ ፍሬ ቢስ ቢሆንም፣ ምንም እንኳን እኛ ብንደክምም፣ ጥቅም ባናገኝበትም እንሥራ፣ ጋን በጠጠር እንዲደገፍ አገርም የኔ ድጋፍ ያስፈልጋታልና።

ውሃ ቢወቅጡት እንቦጭ የሆነ ማንነት ቢኖረንም ቅሉ ተመልሶ ጭቃ ብንሆንም ንስሐ እንግባ፤ እንጹም፣ እንጸልይ፣ ሥጋውን ደሙን እንቀበል፣ እናገልግል፣ ከስንፍና በራቀ ትህትና ውስጥ ሆነን ማገልገል ይጠበቅብናል መንፈሳዊነትም ይገባናል እንበል።

ሰይጣን እና ውሻ አንድ ናቸው፤ ውሻ የእውሩን በትር እንቅስቃሴ አይቶ እንዲሸሽ አይነስውርነቱ ውሻን በበትሩ መከላከል እንዳያግደው ሁሉ እንዲሁ ሰይጣንም በኛ ጸሎት እንደዛው ነው የምንጠራው ሥመ አምላክ ሃይል አለውና። ምንም የልብ ንጽሕና ባይኖረንም የአፋችንን እንቅስቃሴ ተመልክቶ ይሸሻልና እንጸልይ። ጸሎት ካለመጸለይ ይሻላልና። አገርን ማገልገል ካለማገልገልና በሙስና አገርን ከማቆርቆዝ ይሻላልና። ሁሉም ባለበት መስክ ታማኝ ሆኖ ካገለገለ አገር ትበለጽጋለችና።

እያንዳንዱ ሰው በየቤቱ በሕይወቱ ውስጥ እምነቱ የሚያስገድደውን ተግባር በትንሹም ቢሆን ቢያከናውን ካለማድረግ ይሻላል። ከ"ሚሰበር ይሰንጠር" ይላሉና አበው፤ የአገር ጉዳይ የአብያተ እምነት ጉዳይ ተሰብሮ ከሚጣል ተሰንጥሮም ቢሆን ቢቀጥል ይሻላልና። ነገ ስንጥሩ መደፈኑ አይቀርምና።

ስለዚህ ከአገር እና ከየእምነት ሥፍራችን ጋር ያለን ቁርኝት ተሰብሮ ከሚቀር ተሰንጥሮም ቢሆን ይቀጥል ነገ ሌላ ቀን ነውና።

በሌሎች አስተማሪ ጽሑፎች እንድንገናኝ ከታች ያሉትን ሊንኮች ይጠቀሙ።

My Facebook page link (በፌስቡክ ገጽ እንገናኝ)

https://www.facebook.com/deresse2020/

Main facebook account (ዋናው የፌስ ቡክ ገጼ ይቀላቀሉት)

https://www.facebook.com/DeresseReta

Follow me through telegeram (በቴሌግራም ሊከታተሉኝ ከፈቀዱ) ሁሉም ምልከታዬን የማጋራባቸው ማህበራዊ ድረ ገጾች ናቸው።

https://t.me/deressereta

ከአሥር አመት በላይ ከ50ሺ በላይ አንባቢዎች ያሉት መጦመሪያም አለ።

www.deressereta.blogspot.com 

እሑድ 11 ኦክቶበር 2020

በኛ ይብቃ ...

 በኛ ይብቃ ...

ደረሰ ረታ
1/2/2013

አደጋዎች በሽ ናቸው።

የትራፊክ አደጋ፣ በህክምና ስህተት የሚደርስ አደጋ፣ በብሔር ግጭት የሚደርስ አደጋ፣ በሃይማኖት ጥላቻ የሚደርስ አደጋ፣ በፖለቲካዊ አስተሳሰብ የሚደርስ አደጋ፣ በተፈጥሮ ክስተት የሚደርስ አደጋ፣ በሰው ሰራሽ በእቅድ የሚደርስ አደጋ፣ ወዘተረፈ በእነዚህና በሌሎች አደጋዎች የብዙዎች ንብረት ወድሟል፣ አካል ጎድሏል፣ ለስደት ተዳርገዋል፣ ለሞት ተዳርገዋል።

የተረፉት፣ የተጎጂዎች ቤተሰብ፣ የቅርብ ሰዎች በየሚድያው ይቀርቡና "በኛ ይብቃ ... ከኛ ተማሩ" ሲሉ ይደመጣል።

ከመች ወዲህ ነው ጥቃት መማሪያ የሚሆነው?

ከመች ወዲህ ነው ጥቃት መማሪያ የሆነው?

በምን መልኩ ነው መገደል መማሪያ ሊሆን የሚችለው?

እነማንስ ተምረው ድርጊታቸውን አቆሙ?

ከዚህ ልምድ የሚቀስሙት ገዳዮች ወይስ ሟች ነው ትምህርት የሚወስደው?

እኔ በበኩሌ ከዚህ አልማርም፤ በገዳዮች ስሕተት መሞት በቃኝ። በአጥፊዎች ተገፍቼ መኖር በቃኝ። በአሳዳጆች መፈናቀል በቃኝ።

እመራሃለሁ የሚለኝ መንግሥት ከስጋት ነጻ ሊያደርገኝ ይገባል፣ በዚህ ላይ ለተሰማሩት ፍርዲ ሊሰጥልኝ ይገባል፣ ሁሉንም እኔ እየሆንኩ በኔ ይብቅ እያልኩ መኖር በቃኝ።

በብሔር ግጭት የምሰደድ የምሞት እኔ፣ በፖለቲካ ሽኩቻ ንብረቴ የሚዘረፍ እና የሚወድም እኔ፣ በሐይማኖት ግጭት የምገፋ የማምለክ ነጻነቴን የማጣ እኔ፣ ... በቃኝ።

በኛ ይብቃ እያልኩ አልኖርም፤ ፍትህ ይገባኛል።

በሕክምና ስሕተት ህይወት የሚቀጥፉ፣ በፖለቲካ ቁማር ጫወታ ሕዝብ የሚያሰቃዩ አገር የሚያተራምሱ፣ በተረኝነት መንፈስ በሕዝብ ገንዘብ የሚጫወቱ፣ በግዴለሽነት በትራንስፖርት በመኪና አደጋ አካል የሚያጎድሉ ንብረት የሚያወድሙ ሕይወት የሚቀጥፉ የሚቀጡበት ሕግ ይሻሻልልን። ደማችን ፈሶ፣ ንብረታችን ተዘርፎ፣ ተስፋችን ሰልሎ፣ ሕይወታችን አልፎ አይቅር።

"በኛ ይብቃ" ይብቃን። በእነርሱም ተመጣጣኝ ቅጣት ይጣል።

#በወሊድ_ምክንያት_በሕክምና_ስሕተት_መሞት_በቃን
#በመኪና_አደጋ_መሞት_በቃን፣
#በሐይማኖት_ተለይቶ_መሞት_በቃን፣
#በእርስ_በርስ_ግጭት_መሞት_በቃን፣
#በተረኝነት_መገፋፋት_በቃን።

@deressereta

ከወደዱት ያስተምራል ብለው ካሰቡ like እና share ያድርጉ።
My Facebook page link (በፌስቡክ ገጽ እንገናኝ)

https://www.facebook.com/deresse2020/

Main facebook account (ዋናው የፌስ ቡክ ገጼ ይቀላቀሉት)

https://www.facebook.com/DeresseReta

Follow me through telegeram (በቴሌግራም ሊከታተሉኝ ከፈቀዱ) ሁሉም ምልከታዬን የማጋራባቸው ማህበራዊ ድረ ገጾች ናቸው።

https://t.me/deressereta

ከአሥር አመት በላይ ከ50ሺ በላይ አንባቢዎች ያሉት መጦመሪያም አለ።

www.deressereta.blogspot.com 

ረቡዕ 30 ሴፕቴምበር 2020

አርአያነት

 "አርአያነት"


ከምትሰሩት ይልቅ ስለምታጠፉት ነገር ተጠንቀቁ።

ደረሰ ረታ


ሰው የዘራውን ያንኑ ያጭዳልና እያንዳንዳችን ከምንሰራው ይልቅ ስለምናጠፋው ነገር ልንጠነቀቅ ይገባናል።


የአለማችን ትላልቅ ሰዎች ይጠቅማል ያሉት እና እውቀታቸውን ተጠቅመው የሰሯቸው የአእምሯቸው ውጤት ጥፋት ያስከተለባቸው ብዙዎች ናቸው።


የኖቬል ሥራዎች


ጠቢባን እውቀት አይነጥፍባቸውምና ባለቸው እውቅና እና እውቀት ተጠቅመው ጥፋትን አምክነዋል፣ እድሉን ያላገኙት ደግሞ በሌሎች ጠቢባን ጥፋታቸው እንዲመክን ተደርገዋል።


ዛሬ አለማችን በብዙ አቅጣጫ በብዙዎች ስህተት እና ክፋት ጥንስስ እየታመሰች ትገኛለች። አገራችንም ኢትዮጵያ በ"ምሁሮቻችን" ያልተገባ ንትርክ እና ትርክት፣ በልሂቃን ዝምታ፣ በሆድ አደሮች ጫጫታ፣ በፖለቲከኞቻችን ጽንፈኝነት፣ እየታመሰች ነው።


አንዳንዶች ሊነጋ ሲል ይጨልማል ሲሉ ገሚሶች ደግሞ ከድጡ ወደማጡ እያሉ የዳቦ ሥም ያወጡለታል። ግራም ነፈሰ ቀኝ ዋጋ እያስከፈለን ይገኛል።


ታድያ እኛ ከየትኛው ነን?


እያወቁ ከሚያጠፉት ወይንስ እየሰሩ ከሚጠፋባቸው ወገን ነን?


እንደ አብይ ያነሳነው የመዳሰሻ ርእሳችን "ከምትሰሩት ይልቅ ስለምታጠፉት ነገር ተጠንቀቁ" የተሰኘው ቃላችን ብዙዎቻችን አንድን ተግባር ስንከውን የሚታየን ፊትለፊት ያለው በጎ ነገር እንጂ ከበስተጀርባው ያለውን አሉታዊ ተጽዕኖ ልብ አንለውም። ችግሩ ከተከሰተ በኋላ ጥፋተኝነቱንም ለመቀበል እንቸገራለን።


ለዚህም ነው ችግሩ ከመከሰቱ አስቀድሞ ጥንቃቄ እንድናደርግ ለማሳሰብ የተገደድኩት። ወድጄም አይደለም ጥፋቱ በራሴው ስለተከሰተ ላስተምርበትም ብዬ እንጂ።


ነገሩ እንዲህ ነው፦ ትንሽ ልጅ አለችኝ ሁለት አመት ከመንፈቅ ሆኗታል። እንደ አብዛኛው ቤተሰብ ልጅ ሞባይል ትወዳለች።ሞባይል እጇ እንደገባ "ዩቲዩብ" ውስጥ ገብታ የልጆች መዝሙር እና ጨወታ ትከፍታለች። የሚገርመው ደግሞ አገርኛ አትወድም የውጭውን ካልሆነ በቀር። ይህ ድርጊቷ እንደ አገር በልጆች ፍላጎት ላይ ብዙ መሥራት ያለብን ነገር እንዳለ ይሰማኛል። ይሁን እንጂ "የኢትዮጵያ ልጆች ቴሌቪዥን" ሳላመሰግን አላልፍም።


ወደጉዳዬ ስመለስ ሞባይል መውደዷ እንዳለ ሆኖ ዛሬ ያስተዋልኩባት ነገር ትንሽ ሳይሆን በደንብ ትኩረቴን ስቧል። መሉ በሙሉ ጥፋቱ የኔ ነው። አሁን የጻፍኩላችሁንም ጨምሮ የምጽፈው ሞባይሌን ተጠቅሜ ነው። ታክሲ ውስጥም ሆነ የትኛውም ቦታ ላይ ሆኜ እጽፋለሁ። ርእሴ ማህበረሰቡ ስለሆነ የትም ሆኜ ይጎነትለኛልና።


ይህ የአጻጻፍ ክስተት እቤት ድረስም ይዘልቃል። ከዚህ ጋር ተያይዞ ታድያ የመጻፍ ትእዛዝ ከውስጤ ሲደርሰኝ፣ መጽሐፍ የማንበብ ዛር ሲመጣብኝ፣ ድካሜን ለማራገፍ ስሻ መኝታ ቤት የመግባት ልምድ አለኝ። ልጄ ሶልያናም የኔ ነገር መጣባት መሰል ወደ መኝታ ቤት ትገባለች። እኔ እንደማደርገው በጀርባዋ ተኝታ፣ እግሯን አነባብራ፣ ሲያሻት በሆዷ ተኝታ ሞባይሏን ትመለከታለች።


እዚህ ጋር ነው ስብራቱ። 


ልጄ ሶልያና ለሁላችንም በኔ በኩል ተናገረች፤


ልጄ ሶልያና ለኔም ለናንተም የሚሆን መልእክት አስተላለፈች መሰል አጋራኋችሁ።


በድርጊቶቻችን መካከል ሁሌም ልብ ልንለው የሚገባ ነገር እንዳለ ይሰማኛል፣ እንቅስቃሴያችን ድርጊታችንን ከመከወን ባሻገር አርአያነት ያለውና ከመሰናክልነት እስከሚችለው አቅም ድረስ የጸዳ መሆን አለበት።


ሁላችንም እንዲህ ነን ሥንሰራ እንስታለን፣ ሥንሰራ እናጠፋለን፣ ሥንሰራ ያልጠበቅናቸው ብዙ ነገሮች ይከናወናሉ፣ ሥለዚህ ስለምንሰራው ብቻ ሳይሆን ከበስተጀርባው ስላለው ስህተት እንድናስብ መልእክቴን ማስተላለፍ እፈልጋለሁ።


እኔ ለልጄ አርአያነት የጎደለው ተግባር በማሳየቴ አልያም ለስለስ ስናደርገው የምሰራውን ነገር ብቻ ስመለከት ያላየሁት ነገር ልጄ ላይ ተጽእኖ አሳድሯል። ስለምጽፈው ነገር፣ ስለማነበው ጉዳይ፣ ስለምሰራው ሥራ ብቻ ሲሆን በተዘዋዋሪ ግን ስህተት እየሰራሁ እንደሆነ ልብ አላልኩም።


ልክ እንደዚሁ ሁላችንም ለምናደርጋቸው ነገሮች ጥንቃቄ እናድርግ እላለሁ። በመቀጠልም ከፍ ስንል እንደ አገር እንደ ተቋም ትዝብቴን ልሰንዝር።


የተቋማት ሰው ሃይሎች ስለሚቀጥሩት እንጂ ስለሚያባርሩት የቀድሞ ሰራተኛቸው ጥንቃቄ ይጎድላቸዋል። (በአንድ ወቅት በምሰራበት ተቋም አዲስ ተቀጣሪ ሰራተኞች ሥራ ጀምረው ወራት አልያም አመት ይሰሩና ይለቃሉ፣ አልያም በዚያው ይቀራሉ፣ የቅርብ አለቆችም ማስታወቅያ ያወጣሉ በራሱ የለቀቀውን ሰራተኛ ያሰናብታሉ፣ ይሕን ነገር በተደጋጋሚ ማየቴ ሰላም አልሰጥ ሲለኝ ዋና የሥራ ሃላፊውን ገብቼ አነጋገርኩት "ሰራተኞች ከዚህ ክፍል ለምን በብዛት ይለቃሉ? የሚለው ቢጠና ሃላፊነቱ የሰው ሃይል ቢሆንም exit interview እየተጠሩ/መልቀቂያ ለሚወስዱት ቢደረግ" ብዬ ላቀረብኩት ሐሳብ የሚያሳዝን ምላሽ ነበር ያገኘሁት። " ከዚህ የተሻለ ክፍያ የሚያገኙ ከሆነ ይሂዱ እኛም ሌላ እንቀጥራለን" ነበር ያለኝ። እዚህ ጋር ነው ችግሩ ስለምንቀጥረው እንጂ ስለምንለቀው ሰራተኛ አንጨነቅም።


ሐሳቤና ሐሳቡ ተቃርኖ ነበረው እኔ ከስህተታችን እንድንማርበት ስፈልግ እርሱ ስለሚተካው ሰራተኛ ነበር፤ የለቀቅናቸውን ሰራተኛ ክብርና ጥንቃቄ ከሌለን በእጃችን ስላሉት ያለን ጥንቃቄ ምን ዋስትና አለው።


የሥራ ሃላፊዎች ስለሚያሰሩት ሥራ እንጂ ሥለሚሰራው ሰው ጥንቃቄ ይግግድላቸዋል።


የጦር መሪዎች ነጻ ስለሚያወጡት አገር እንጂ በጦርነቱ ስለሚገደሉት፣ ጥቃት ስለሚፈጸምባቸው፣ ስለሚወድመው ንብረት፣ ተልእኮ አሰጣጥ ላይ ጥንቃቄ ጉድለት ይታያል።


ቴሌ፣ መብራት ሃይል፣ ውሃና ፍሳሽ፣ መንገዶች ባለስልጣን ሥራዎቻቸውን ሲያከነውኑ የሚሰሩትን ብቻ ሳይሆን ስለሚጠፋው ነገር የተጠያቂነት ሥሜት ሊሰማቸው ይገባል።


መንገድ ሲቆረጥ እና መስመር ሲዘረጋ የሕብረተሰቡ መሰረተ ልማት እንዳይደረግ ከፍተኛ ጥንቃቄ ሊደረግበት ይገባል።


ግለሰቦች አጥራቸውንም ሲጠግኑም ይሁን ሕንጻዎችን ሲገነቡ የነዋሪዎችን እንቅስቃሳ በማያደናቅፍ እና ሕይወታቸውን በማያናጋ መልኩ እንዲሆን ይጠበቃል።


ሁሌም አንድ ወደልቤ የሚመጣ ጉዳይ ላንሳና ላጠናቅ።


አገሪቱ ላይ የተለያዩ ችግሮች ሲከሰቱ፣ የነዳጅ ዋጋ ሲጨምር፣ ኢኮኖሚው መረጋጋት ሲሳነው፣ ባለሃብትና ነጋዴዎች ለመንግሥት ቅሬታቸውን/አቤቱታቸውን ሲያቀርቡ ሁሉም መንግሥትን ጨምሮ መፍትሔ ሲሰጡ ጫናው የሚያርፈው ድምጽ በሌለው ሰፊው ሕዝብ ላይ ነው።


በቅርቡ የኮቪድ19 የኮረና አለም አቀፍ ወረርሽኝ ወቅት ኑሮ በሁሉም ላይ በትሩን ሲያሳርፍ፣ ኢኮኖሚው አለምን ባሽመደመደበት ዘመን የጤና ተቋማት እና የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ አካል የሆነው የትራንስፖርት አጠቃቀም ውሳኔ የትራንስፖርት ወጪውን እንዲሸፍን የተደረገው ድሃው ሕዝብ ነው።


ስለዚህ ውሳኔዎቻችን አንዱ ጋር መፍትሔ ሰጪ ሲሆኑ ሌላ ሥፍራ ችግር ፈጣሪ እንዳይሆኑ ልንጠነቀቅ ይገባል እላለሁ። ይህ የግሌ እይታ ነው።


እኛ ምርጥ የሚባሉ ሥራዎችና ሐሳቦች ይኖሩን ይሆናል፤ አሉንም። ታድያ እንዚህን እንደ ልጃችን እንደምንሰስትለት ሁሉ ሌላኛውን ያላየናቸውንም እንድናያቸው መልእክቴን አስተላልፋለሁ። ሥራዎቻችን ሃላፊነት እና አርአያነት የጎደለው እንዳይሆን ጥንቃቄ እናድርግ። ከምንሰራው እኩል ስለሚጠፋብን ነገር ትኩረት እንስጥ።


Follow me through 

@deressereta

እሑድ 27 ሴፕቴምበር 2020

ኦርቶዶክሳዊ የአለም እይታችን

 ኦርቶዶክሳዊ የዓለም እይታችን

( Orthodoxy Interpretive frame work )

የዓለም እይታችን በዓለማችን ውስጥ ነገሮች እንዴት እንደሚከናወኑ ለመረዳት እንዲያስችለን በማወቅም ይሁን ባለማወቅ በአእምሮአችን የምንይዛቸው የግምቶች (assumptions) ስብስብ ነው። በእለት ተዕለት ከተፈጥሮ ጋር በምናደርገው ግንኙነት ከእውነታው የራቀ ምኞታችንን የሚወስኑ እነዚህ ግምቶች ናቸው ፡፡

እነዚህ ግምቶች ወደ አዕምሯችን የምንወስዳቸውን ነገሮች የሚተረጉሙበት ለአዕምሯችን እኛን ለመምራት በሚያስችል መልኩ አንድ አምሳያ(model) ይሰጡናል ፡፡

የአስተሳሰባችን እና የሕይወታችን አንድነት አንዲሠምር መሰረት ስለሚያደርግ ይህ የዓለም እይታ ለእኛ በጣም አስፈላጊያችን ነው። ጥሩ ሕይወት ምን ማለት እንደሆነ እና ትርጉም ያለው ምን እንደሆነ ሕይወት እንድንረዳ ያስችለናል ፡፡ ከአካባቢያችን የሚፈጥሩት ተጽእኖዎችን በምንጋፈጥበት ጊዜ ወዲያውኑ ሀሳባችንን እና ድርጊቶቻችንን እንድንመርጥ ይረዳናል ፡፡

የዓለም እይታ ከሌለ በእያንዳንዱ ቅጽበት የሚኖሩ ሁሉንም የስሜት ህዋሳት ግብዓቶችን መረዳት አንችልም ነበር። እኛ ሁላችንም የዓለም እይታ አለን ፡፡ ጥያቄው የእኛ የዓለም እይታ በምን ዓይነት ግምቶች ላይ የተመሠረተ እንደሆነ እናውቃለን? ወይ ነው

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለቆላስይስ ሰዎች በጻፈው ደብዳቤ ላይ በጣም ግልፅ በሆነ ሁኔታ ለክርስቲያኖች በሰጠው ማስጠንቀቅያ- " እንደ ክርስቶስ ትምህርት ሳይሆን ፣ እንደ ሰው ወግና እንደ ዓለማዊ እንደ መጀመሪያ ትምህርት ባለ በፍልስፍና እና በከንቱም መታለል ማንም እንዳይማርካችሁ ተጠበቁ ። " ቆላ 2:8 ብሏቸዋል፡፡

የሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስን ማስጠንቀቂያ በማዳመጥ ከክርስቶስ ይልቅ በዓለም እና በዓለም ባህላዊ ባህሎች በኩል የሚሰጡን ፍልስፍና ማታለያዎች (philosophical deceptions) ምንድናቸው?

ጥቂቶችን እነሆ :-

1. ምክንያታዊነት (Rationalism)

ምክንያታዊነት ለሚደርስባቸው መደምደሚያዎች በአመክኖአዊ አዕምሮአችን ላይ ሙሉ እምነትን ይሰጣል ፡፡ የእውነት ምንነት የሚረጋገጥው እና የሚወሰነው በአእምሮ የማስተዋል አቅምና በሥነ አመክንዮታዊ አስተሳሰብ ላይ ስንደገፍ ብቻ ነው የሚል አመለካከት ነው ፡፡ “I think, therefore I am” የሚለው የፈረንሳያዊ ሬኔ ዴካርት የተለመደው ጥቅስ አስተሳሰባችን ማን እንደሆን እና እኛ የሃሳባችን ድምር እንደሆንን የሚገልጽ አመለካከት ነው።
በሃሳባችን ወይም በምክንያቶቻችን ላይ ሙሉ በሙሉ እምነት ሊኖረን እና እንደ ሥጋችን እና ደማችን እንደሆን አድርገን እንድንጠብቀው ይገፋፋናል።
ይህ አመለካከት የእኛን ፈቃድ በማስቀደም የእግዚአብሔርን ፈቃድ እንደ ሁለተኛ ስለሚቆጥር ከኦርቶዶክሳዊው የዓለም እይታ ጋር ይጋጫል ፡፡ ይህ ደግሞ አስተሳሰባችንን በእጅጉ ወደ ሚቆጣጠሩት ወደ ሌሎች ብዙ ጎራዎች ይመራናል ፡፡

2. ተሞክሮነት / ተዳሳሽነት (Empiricism)

ይህ አመለካከት የእውቀት መሠረት ከስሜታችን አንጻር ሲታይ ተሞክሮአችን እንደሆነ ይገምታል። ይህ የሳይንሳዊ ዘዴ መሠረት ነው። የዚህ አይነት የዓለም እይታ ፍፁም እውነት የሚገኘው ስሜቶቻችን ከሚሰጡን እና እኛ የምናውቀውን በስርዓት ባለው መልኩ በተደረገ ጥናት አማካይነት ብቻ መሆኑን ያረጋግጣል ፡፡ በቅዱስ መጽሐፍ ውስጥ የተመዘገበውን የመለኮታዊ መገለጥን እውነት ውድቅ ያደርገዋል።

3. ሰብአዊነት / ግለሰባዊነት

ሰብአዊነት እና ግለሰባዊነት የተመሰረተው እውነት እና ሥነ-ምግባራዊ በሆነ መንገድ በሚፈለጉት ግምት ነው። ይኸውም የግለሰቦችን ራስን በራስ ማስተዳደር እና እያንዳንዱ ግለሰብ የራሱን ወይም የራሷን እውነት መፈለግ አለበት የሚለውን ሀሳብ ይወስዳል። ይህ በእምነት እና መለኮታዊ በሆነ መንገድ በተገለጡት በእግዚአብሔር ሕግጋት ላይ የተመሠረተ ጥገኛነትን ስለማይቀበል ከኦርቶዶክሳዊው የዓለም እይታ ጋር ይጋጫል ፡፡ ከቤተክርስቲያኒቱ ስልጣን ይልቅ ለእያንዳንዱን ግለሰብ አመለካከት እና ውሳኔ ከፍተኛ ቦታ ይሰጣል ፡፡ ይህ ደግሞ ከመንፈሳዊ እሴቶቻችን ሁሉ አርቆ ፍጹም ወደሆነው አለማዊነት (secularism) ይወስደናል፡፡

4. አንጻራዊነት(Relativism )

አንጻራዊነት መነሻው የሁሉም የፍርድ መሠረቱ አንጻራዊ ነው በማለት ሲሆን ፣ ይህም እንደ ሁኔታውና እንደግለሰቡ ወይም ድርጊቱን ግለሰቡ እንደሚያይበት ሁኔታ ይለያያል ማለት ነው፡፡ የግለሰቡ ወይም የሰዎች ስብስብ እምነቶች እና ሃይማኖት ለእነሱ “እውነት” ነው ብሎ ያስባል ፣ ግን ለሌሎች ግን የግድ እውነት አይሆንም ፡፡ በዚህ ግምቶች ስብስብ በዓለም አቀፍም ሆነ ሙሉ በሙሉ እውነት የሆነ ሃይማኖት የለም ፡፡ እንደዚሁም ሥነ ምግባራዊ ፍፁምነት የሉም ፣ ትክክለኛ ወይም የተሳሳቱ የሥነምግባር አቋሞች የሉም ፡፡ ሁሉም የሞራል እሴቶች ለአንዳንዶች እውነት ናቸው ግን ለሌሎች ግን አይደሉም ፡፡ ይህ ከኦርቶዶክስ ዓለም እይታ ጋር ይጋጫል ክርስትና ፍጹም እውነት ነው ፡፡ ፡ በአንጻራዊነት አመለካከት ምክንያት የራሳችንን እውነት አንዳንድ ጊዜ እንክዳለን ፡፡ ዘመናዊነት ሁሉንም ባህሎች እና ትውፊቶች አይቀበልም ፡፡ የቀደመውን እና የቀደመውን ዘመን “የጨለማ ዘመን” ነው ብሎ ይገምታል። ይህ አመለካከት በመፅሃፍ ቅዱስ ውስጥ ያልተካተቱትን የቤተክርስቲያን አባቶች እና የቤተክርስቲያኒቷን ሁሉንም ትውፊት በእጅጉ ዋጋ ያሳጣችዋል ፡፡

እነዚህን ሁሉ አንድ ላይ ስናመጣቸው ወደ እግዚአብሔር መኖሩ አይታወቅም ( agnosticism) ወደማለት እና ፈጽሞ እስከመካድ (atheism) ያደርሳል ፡፡ በእነዚህ ሁሉ ጎራዎች እና በውስጣቸውም በያዙት ድብቅ ግምቶች (assumptions) በእኛ ላይ ተጽዕኖ እያሳደሩብን መሆኑን እና በኦርቶዶክሳዊው የሕይወት መንገዳችን ላይ በተቃራኒው እንደቆሙ መገንዘብ አለብን ፡፡ የክርስቶስን እና የቤተክርስቲያኒቷን ትምህርት ሙሉ በሙሉ ለመቀበል እንችል ዘንድ የራሳችንን የዓለም እይታዎችን መመርመር ፣ የተደበቁ ግምታችንን ማሻሻል ፣ መመርመር እና አስፈላጊ ከሆነ እንዲለወጡ መፍቀድ አለብን።

አምላካችን በቅዱሳኑ አድሮ እና በሥጋዌው የተገለጠውን እውነት ሁሉ ተቀብለን ቤተክርስቲያናችንን የነፍሳችን መዳኛ እና የደስታችን ቦታ ማድረግ ይኖረብናል። የራሳችንን የአዕምሯዊ ግንባታ በመተው ፣ “ጌታ ሆይ የማይገባኝ አገልጋይህን እዝነኝ ፥ ባለማወቄና እርዳኝና በእውነትህ ውስጥ ምራኝ ”እንበለው ።

ታሪካችንን አስታውሰን ፣ ኦርቶዶክሳዊነት ያለመለወጥ በሐዋርያት በኩል የጌታችን እና የአዳኛችን ትምህርቶች መሆኑን ተረድተን እንደ የማይለዋወጥ የእውነት ምንጭ መቀበል ይገባናል።

የኦርቶዶክስ የዓለም እይታ ምንድነው?

እኛ ክርስቲያኖች እንደመሆናችን መጠን በአዕምሮአችን የማሰብ ችሎታ ብቻ ለመረዳት ከሚያስችለን በላይ የሆነ እምነት አለን ፡፡ እግዚአብሔር ከሁሉም ምክንያታዊ እውቀት በላይ መሆኑን እናውቃለን ፡፡ በምክንያታዊ ሂደት ወይም በሳይንሳዊ ዘዴ ሊብራሩ የማይችሏቸውን ተዓምራቶች ለመቀበል ምንም ችግር የለንም። ሃይማኖታችን ፍጹም በተገለጠው እውነት ላይ የተመሠረተ በመሆኑ ምስጢራዊ እና የማይታየውን እንቀበላለን ፡፡ሁሉን ቻይ እና ፍጥረቱን አፍቃሪ በሆነ አምላክ እናምናለን እንዲሁም ሙሉ በሙሉ እንታመናለን። ከዚህ ሥጋዊ ዓለም ባሻገር በሚመጣው ዓለም ውስጥ የዘላለም ሕይወት ለማግኘት ድህነትን እና ከእርሱ ጋር ህብረት እንዲኖረን እንፈልጋለን ፡፡ ኑሯችን በቁሳዊ ደህንነታችን እና ደስታን በመፈለግ ላይ የተመሠረተ የሕይወት መንገድ አይደለም። የቤተክርስቲያኗን ትውፊት እንቀበላለን እናም መጽሐፍ ቅዱስን እንደ ቤተክርስቲያን ስጦታ አድርገን እንቆጥረዋለን። እኛ በቤተክርስቲያን እና በትውፊታዊ አውድ መሠረት እንተረጉማለን ፡፡ የቤተክርስቲያናችን አባቶች ያቆዩልንን ጥበብ በቀላሉ መጣል አንችልም። በቅዱሳት መጻሕፍት ትርጓሜያችን ውስጥ ልንመለከተው ይገባል ፡፡

እንደ ቤተክርስቲያኗ አባልነታችን የክርስቶስ ምስጢራዊ አካል አባላት ነን። ዘመናዊው ማኅበረሰባችን ያስተዋወቀንን የሐሰት እውነቶችን እና ወጎችን በመከተል ወጥመድ ውስጥ እንዳንወደቅ እና መዳንን እና ዘላለማዊ ህይወትን ከእኛ በማራቅ ከእግዚአብሔር ህብረት እንዳይለዩን ከሐሰት ግምቶች መራቅ አለብን። ይህ ቀላል ጉዳይ አይደለም ፡፡ የቤተክርስቲያኗን እውነቶች እና ልምዶች ለመከተል በመወሰናችንም ምናልባትም ከብዙኅኑ ጋር ማለት በሚያስችል ሁኔታ ተቀባይነትን ልናጣ እንችላለን ፡፡
አሁን ያለንበት እውነታ በአእምሯችን ውስጥ የተገነባው በዘመናዊ የአኗኗር ዘይቤያችን ፣ በኦርቶዶክስ ባልሆኑ ክርስትያኖች በሚሰጡ ትምህርቶች እና የዘመናዊው ትምህርት ስርዓቶቻችንን በሚመሠርቱ ጎራዎች ላይ በመመስረት የተደበቁ ግምቶች ናቸው ፡፡ እነዚህ መሠረተ ቢስ ግምቶች እምነታችንን ያዳክማሉ። እነሱን መመርመር እና ከእምነታችን ጋር የማይሄዱትን በደንብ መለወጥ አስፈላጊ ነው ፡፡ የኦርቶዶክስ የሕይወት መንገድ የኃጢያተኛ አኗኗራችንን እንድንከፍት ፣ የተሳሳቱ አመለካከቶችን እንድንገለጥ እና ባህርያችንን እንድንለውጥ ይመራናል።

እነዚህን የተደበቁ ግምቶች በውስጣችን መኖራቸውን መመርመር የመጀመርያው ሂደት ነው ፡፡ ከኦርቶዶክሳዊው የሕይወት መንገዳችን ጋር የሚጋጩ በገሃዱ ዓለም ያሉ አንዳንድ ነገሮችን ለመለየት የተወሰነ ጊዜ ውሰዱ ፡፡ ከዚያ እራስዎን ይጠይቁ ፣ ቤተክርስቲያኒቷ በእነዚህ ሁሉ ተቃርኖዎች በቅዱሳት መጻህፍቶችዋ እና በትውፊቷዋ እንዴት ልትረዳኝ ትችላለች? ብለው ይማጸኗት

እንጂ

• ብሔረተኛ ሆኖ ኦርቶዶክስ መሆን አይቻልም ! ! !
• እየተሳደቡ ኦርቶዶክስ መሆን አይቻልም ! ! !
• በሰዎች ላይ እየተደገፉ ኦርቶዶክስ መሆን አይቻልም ! ! !
• ቤተክርስትያን ያወገዘችውን እየተከተሉ ኦርቶዶክስ መሆን አይቻልም ! ! !

መልካም ቀን
ዲ. ኤልያስ ደፋልኝ 

በምን መታወቅ ይፈልጋሉ?

 በምን መታወቅ ይፈልጋሉ?

(ምን ሰርተው ታወቁ?)


ከስብ ሥም ይሸታል ይላሉ አባቶቻችን ሲተርቱ። ልጅ እያለሁ ለበአል የቤታችን ግድግዳ ከሚዋብባቸው ጋዜጦች ላይ ከማነባቸው አምዶች መካከል "ምን ሰርተው ታወቁ?" የሚሰኘው ቀልቤን ይገዛዋል።

ኢትዮጵያ የጀግኖች አገር እና ሉአላዊት አገር ለመሆኗ ማረጋገጫው "የአድዋው ጦርነት" ድል የግንባር ላይ ምልክት ያህል ይሁን እንጂ ያኔም ሆነ በዚሁ በዘመናችን ብዙ በሥም ጠቅሰን የማንጨርሳቸው የጦር ሜዳ ጀግኖች አሉን።

ዘመን ተሻጋሪ የአትሌቲክስ ጀግኖች ለመዘርዘር ከመነሳት አለመጀመሩ ሳይሻል አይቀርም። ሰማይና ምድር እንዳይቆጡን በሁለት ወገን የተሳለ ስይፍ የመሰለውን እንቋችንን አትሌት ሻለቃ ኃይሌ ገብረስላሴን አለማንሳት ነውር ነው እንደ ምሳሌ እንጥቀሰው።

መጽሐፍ "እንቁዎቻችሁን በእርያዎች ፊት አታስቀምጡ" የሚለውን ዘንግተን በእርያ ፊት በግብር ስንኩላን ከሆኑት ፊት ሃይሌን በማስቀመጣችን በእጅ የያዙት ወርቅ እንደ መዳብ ይቆጠራል እንዲሉ ሆነብን።

እርሱ ግን ጽናቱ እና ጀግንነቱ በድቡሽት መሬት ላይ ሳይሆን በአለት ላይ የተመሰረተ ነውና ወይ ፍንክች ያባ ቢላዋ ልጅ ሆኖ አግኝተነዋል። ለማንኛውም ኃይሌ በሁሉም መስክ ጀግናችን ነው።

እስኪ ወደራሳችን እንመለስ።

ምን ሰርተን መታወቅ እንሻለን?

ምንስ እየሰራን ነው ያለነው?

በአንድ ወቅት ካነበብኩት ነገር የማስታውሰው "በሕይወት ዘመንዎ ፍጻሜ በእርስዎ የቀብር ሥነሥርዓት ላይ የሕይወት ታሪክዎ ምን ተብሎ እንዲነበብልዎ ይፈልጋሉ?" የሚል ነበር።

እያንዳንዳችን የሕይወት ታሪካችንን በተግባር እየጻፉ/እየተገበሩ ማለፍ ግድ ቢሆን ሥምዎ በምን እንዲጠራ ይፈልጋሉ?

በሕይወት ዘመንዎ በምን መታወቅ ይፈልጋሉ?

ተማሪ ከሆኑ መምሕሮችዎ ምን አይነት ተማሪ ነበር ብለው እንዲያስታውስዎ ይፈልጋሉ? የትምህርት ቤት ጓደኞችዎሰ?

የመንግሥት ሠራተኛ ከሆኑስ ቀጣሪዎችዎ አልያም የቅርብ አለቃዎ በምን እንዲያውቁዎ/ ምን አይነት ሰው ነው ብለው እንዲጠሩዎ ይፈልጋሉ? የሥራ ሃላፊስ ከሆኑ ምን አይነት አለቃ መባል ይፈልጋሉ?

አገር ቢመሩ?
በንግዱ አለም ቢሆኑ?
የቤተሰብ አስተዳዳሪ (ባል/ሚስት) ሆነውስ?
ልጅ እያሉስ ቢሆን?
የሰፈር ሰው እና ጎረቤትስ?

ሥም ከስብ ይሸታልና እንዲህ ተባልኩ፣ ሰው አይወጣልኝም፣ ደመ መራራ ነኝ፣ እድሌ ጠማማ ነው፣ ወዘተረፈ ከማለት የነገ ሥምዎት ላይ ዛሬ አቅደውና አውቀው ቢሰሩ ይሻላል።

ሥምን ለመገንባት የሚፈጀውን ያህል ሥም ለመጥፋት ጊዜ አይፈጅበትምና በጥንቃቄ እንንቀሳቀስ።

አገሬ ምንም አላደረገችልኝም ከማለት ለአገሬ ምን አደረኩላት የሚለውን አስተሳሰብ እናበልጽግ።

አገር የምታድገውና የምትበለጽገው ተባብረን ሥንቦጠቡጣት ሳይሆን ተባብረን ሥንሰራላት ነውና።

ወጣቶች፣ አረጋውያን፣ ምሁራን፣ የእምነት ተቋማት መምህራን፣ የተቋማቱ መሪዎች፣ የቢሮ ሃላፊዎች፣ ሰራተኞች፣ ነጋዴዎች፣ የፖለቲካ ፓርቲ አመራርና አባላት፣አገር መሪዎች ወዘተረፈ ሁላችንም ከወዲሁ እናስብ፤ ምን ሰርተን መታወቅ? ምን ሰርተን አገራችንን ማስጠራት እንፈልጋለን?

ልብ በሉ ምን ሰርተው እንጂ ምን ሰርቀው አላልኩም።

ሁላችንም እድል ተሰጥቶናል የአዲስ አመት የመጀመሪያው ወር የመጀመሪያው ሳምንት ላይ ስለሆንን እቅዳችንን እናስተካክል፣ ያላቀድን እናቅድ፣ ያቀድን እንኑረው።

ልጆቻችንም ወላጆቻቸው ምን ሰርተን እንዳለፍን የሚመረምሩት ታሪክ ይኑራቸው፣ ያልፈጸምነው እነርሱ የሚጨርሱትን በጎ ነገር እንተውላቸው።

ቸር ይግጠመን።
ደረሰ ረታ
8/1/2013
@deressereta

የመስቀሉ ነገር

 


የመስቀሉ ነገር
ደረሰ ረታ
16/1/2013
(ደመራ)

በንግሥት እሌኒ ትእዛዝ መሰረት መስቀሉን ለዘመናት ከተቀበረበት የቆሻሻ ክምር/ተራራ ሥር ጎልጎታ ከኢየሩሳሌም በብዙ መከራ እና ፍለጋ አግኝታ እስክታስወጣው (ከመስከረም አሥራ ሰባት እስከ መጋቢት አሥር) ቀን ድረስ የመስቀሉ ሃይል አይታወቅም ነበር።

መስቀሉ አስቀድሞ ከባድ ጥፋት/ወንጀል የፈጸሙ ሰወች ምድርን እንዳያረክሱ ከምድር ከፍ ከሰማይ ዝቅ ብለው በሞት የሚቀጡበት የተመሳቀለ ከእንጨት የሚሰራ ነበር።

ኢየሱስ ክርስቶስም ክብር ይግባውና ከወንጀለኞቹ እንደ አንዱ ተቆጥሮ ተሰቀለበት። በእለተ አርብ መጋቢት ሃያ ሰባት ቀን በስድስት ሰአት በከበረ እጸ መስቀል ላይ ሰቀሉት። ሳዶር፣ አላዶር፣ ዳናት፣ አዴራ፣ሮዳስ በሚባሉ ችንካሮች ቸነከሩት። እንደ ወንበዴ ሊቆጥሩት ንጹሁን በወንበዴዎች መካከል ተሰቀለ።

የክብር ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስ አዳምን ያድነው ዘንድ በእንጨት መስቀል ተሰቀለ። መከራን በሥጋው ተቀበለ።

የወንበዴዎች መቅጫ መስቀል በመለኮት ደም ከበረ።
ብዙ ተአምራትን ሰራ፤ አይሁድንም አሳፈረ። ፈርተው ደነገጡ።

ከዚህ በኋላ የመስቀሉ ነገር የአደባባይ ምሥጢር ሆነ።

አይሁድ በቅናት አይናቸው ስለቀላ የማዳኑን ሃይል ለመደበቅ በደላቸውንም ለመሸሸግ ያንን የወንበዴ መቅጫ የተመሳቀለ እንጨት/መስቀል በመለኮት ደም ከብሯልና ክብሩን ለመሸሸግ ወስደው ከምድር በታች ጥልቅ ጉድጓድ ቆፍረው ቀበሩት። የወንበዴዎቹንም መስቀል ከላይ አደረጉበት። እስከ አራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ድረስ (327አ.ም) ድረስ በኢየሩሳሌም ከተማ ቆሻሻ ተከምሮበት ለብዙ ዘመናት ለረጅም ወራት ተደብቆ ኖሯል።

አውቀውም ይሁን ሳያውቁ ቆሻሻ ደፉበት፣ የቆሻሻውም ብዛት ተራራ ሰራበት።

በመስቀሉ ልቧ የተነካ ንግሥት (ንግሥት እሌኒ) ደመራ አስደምራ መስከረም አስራ ስድስት በእጣን ጢስ እየተመራች የተቀበረውን መሥቀል ከተቀበረበት ከምድር ልብ አወጣች።

በአጼ ዳዊት ዘመነ ንግሥና ታስቦ እርሳቸው አረፍተ ዘመን ሲገታቸው በአጼ ዘርኣያቆብ ዘመን ኢትዮጵያ የግማደ መስቀሉ ባለቤት ሆነች።

የትናንቷ ኢትዮጵያ፣ የትናንት ኢትዮጵያውያን፣ የትናንት እናቶች(ሴቶች)፣ የትናንት መሪዎች ይህን ተግባር ሲፈጽሙ የዛሬዎቹ ግን ከቤተክህነት እስከ ቤተመንግሥት ለዚህ ዘመን ለዚያውም ለዚህ አገር እና ትውልድ የማይመጥን ተግባር ይፈጽማሉ።

ሆሳእና "አሁን አድን" የሚል ስያሜን ይዛ አሁን ለክርስቲያኑ ፍትህ ነፍጋለች፣ ከተማዋ ከካህን ስያሜዋን ያገኘች ብትሆንም ካህን ገፊ ሆናለች፣ ከተማዋ ለምህረት ይሁን ለመአት እሳት ይዘንብባት እንደነበር የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው። ሆሳእና የጌታ መገለጥ የታየበት በአል ቢሆንም ኢትዮጵያዊቷ ሆሳእና ግን ከክቡሩ የሰው ልጅ የጥምቀት እና የመስቀል ደመራን ማክበሪያ ሥፍራ ለከብት ማቆሚያ ተሰጥቷል።
የእንስሳት ክብር ከሰው/ከክርስቲያን ክብር ልቋል።
ናዝሬት (አዳማ)፣ ደብረዘይት (ቢሾፉቱ)፣ ሞጆ፣ስልጤ፣ እና ሌሎች ክልልም እንዲሁ እየቀጠሉበት ነው። የቤተክርስቲያንን ጥላቻ የመንግሥትን ሥልጣን ተገን አድርጎ ግለሰቦች ጫና ሆነዋል። ይህ ጥላቻ ጅማ፣ ጅግጅጋ፣ ሻሸመኔ፣ ዝዋይ፣ አሩሲ፣ አሰላ፣ መተከል ወዘተ ላይ አብያተክርስቲያናት ተቃጥለዋል ክርስቲያኖች ተሰውተዋል፤ ሐብት ንብረቶች ወድመዋል። የመንግሥት ተሿሚዎች እንደገና መልሰው ክርስቲያኑን በመግለጫ አስፈራርተዋል። የጸጥታ አካላት ቆመው ባለበት ሥፍራ የተደራጁ ጽንፈኞች አካላዊ እና ስነልቡናዊ ጥቃት ሲፈጸሙ እያየን ነው። መንግሥት ጥቃቱን ከመከላከል ይልቅ ለአጥቂዎች ሽፋን እየሆነ ያለበት ሁኔታ ነው ያለው።

በአስሩም ክልሎች በሁለቱም የፌደራል ከተሞች በሁሉም ወረዳና ቀበሌ፣ በሁሉም የግልና የመንግሥት ተቋማት ብልሹ አሰራር እና አመራር፣ በግልና በመንግሥት የከፍተኛ የትምህርት ተቋማት፣ መስቀሉ ተቀብሯል። የመስቀሉ አዳኝነት፣ የመስቀሉ ሃይል፣ ተደብቋል። ቆሻሻው (ምንዝር፣ ሙስና፣ ጥላቻ፣ ዘረኝነት፣ አስገድዶ መድፈር፣ ግብረ ሰዶም፣ የበላነት መንፈስ፣ የተተኪነት መንፈስ፣) ተከምሮበታል። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን እነርሱም (በሽንገላም ቢሆን) እንደሚሉት እኛም እንደምናምነው ሁሉን አቻችላ እና እኩል አድርጋ ከማእዷ የምታጋራ አገርም እናትም ጭምር ናት።

ይህች ሥንዱ እመቤት ቤተክርስቲያን ጠላቶቿ ገነው፣ ገፊዎቿ በዝተው፣ አቅሟ ተዳክሞ፣ ሰፊ እጇ ሰልሎ (ዝሎ) ታይታለች። ቢሆንም የሲኦል ደጆች እንኳን አይችሏትም። ትናንትንም እንዲህ እያለፈች እዚህ ደርሳለች። እንደሌሎች በእርዳታ እና በበጀት ሌሎችን ለመጫን እና ለማጥቃት የበላይ ለመሆን ሌላ ተልእኮ ይዛ የምትንቀሳቀስ ተቋም አይደለችም።

ትናንት የኢየሱስ ክርስቶስን መስቀል በደመራ በእጣን ጢስ ከተቀበረበት ከቆሻሻው ሥር እንዳላገኘችና እንዳላወጣችው ዛሬ ኢትዮጵያን የተጫናትን መከራ፣ መገፋፋት፣ መከፋፈል፣ መገዳደል፣ ለማስወገድ ደመራውን ደምሮ ጢሱን አጢሶ መስቀሉን ለማክበር ከፍ ከፍ ለማድረግ የመንግሥት ባለሥልጣናት ብልሹ አሰራር እና ቆሻሻ ተግባር ለጊዜውም ቢሆን የመስቀልን በአል የአገራችን የደቡብ እና የኦሮሚያ ክልሎች እንቅፋት ሆነዋል።

በሁሉም አቅጣጫ ኦርቶዶክሳዊ የሆነ እንባውን የሚያነባበት፣ ዋይታና እሮሮ የሚያሰማበት፣ በአላቶቹን በአደባባይ ሳይሆን እንደ ዘመነ ሰማእታት ከምድር በታች እንዲያከብር የሚጠበቅበት እየሆነ መጥቷል።

የመስቀል በአል ያነጋግረን እንጂ የጥምቀተ ባህር ነገርም ከተነሳ እጅን በአፍ ላይ አስጭኖ የሚያስቆዝም ነው።

ለመፍትሔው ብዙ የወጣት ማህበራት፣ ማህበረ ካህናት፣ ቤተክህነት፣ ሲኖዶስ ይንቀሳቀሳል። ነገር ግን ችግሩን ሊቀርፉት አልቻሉም። በቤተክርስቲያን ላይ በሚደርሱ ጥቃቶች ሳቢያ ብዙ የሚደራጁ በአካልና በየሚድያው (ፌስቡክ፣ ቴሌግራም፣ ዩቲዩብ) የሚደራጁ ምእመናን ሞልተዋል፤ ይሁን እንጂ ከተሰባሰቡበት አላማ ውጭ የአክቲቭስቶችና የዩቲዩበሮች እንጀራ ከመሆን አልዘለሉም። ይህም የውስጥ ችግራችን የመስቀሉን ሃይል በማወቅም ይሁን ባለማወቅ የሚጣሉ የቆሻሻ አይነቶች ናቸው።

የመስቀሉን ክብር የሚገልጥ መሪ ኢትዮጵያ ያስፈልጋታል። መስቀሉ የአማንያን ብቻ ሳይሆን ላላመኑትም ይጠቅማል። ከመስቀሉ ጋር የተቀበረ ፍትሕ ለኦርቶዶክሳዊያን ብቻ ሳይሆን ለሌሎች በእምነት ለማይመስሉን ጩኸታቸው ለታፈነ የእምነት ተቋማትና ምእመናን ሁሉ ፍትህ ያሰጣል። ሽቅብ ወደላይ የሚሸኑትን ግፈኞች አደብ ያስገዛል ለመንግሥት እና የጸጥታ አካላት ሳይቀር የራስ ምታት የሆኑትን ሥርአት ያስይዛል።

በመሥቀል በአል ሥም አገሪቱ ላይ የሚፈጸሙ ሥርአት አልበኝነት የኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን ብቻ መስሎን እንደ ጠላት ተመልክተው ደስታም ተሰምቶዎት ከሆነ ተሳስተዋል።

ይህ የጽንፈኝነት አካሄድ ኢትዮጵያዊ መስሊሙን፣ ፕሮቴስታንቱን፣ ካቶሊኩን፣ የይሖዋ ምሥክሩን፣ ወንጌላውያንን፣ ዋቄፈታውን፣ ባሕሉን፣ ወጉን፣ ታሪክን ሁሉ አንድ በአንድ መንካቱ አይቀሬ ነው። ስለዚህ አብሮ መንቃት አብሮ ቆሻሻውን ቆፍሮ ተራራውን ንዶ መስቀሉን አውጥቶ፣ ክብሩን ገልጦ፣ በአሉን በጋራ ማክበር የተሻለ መፍትሔ ነው።

ሰፊዋን ኦርቶዶክስ ከናቁና ከነቀነቁ ወደሌላው የማይመጡበት ምንም ምክንያት የለም። እነዚህን ሰወች ሃይማኖተኛ አድርጎ ብቻ ማየት፣ የእምነቱ ጥላቻ ብቻ አድርጎ ማየት ትልቅ ስህተት ነው፤ የትኛውም ሃይማኖተኛ በምንም መለኪያ ይህንን የማድረግ ሞራል የለውምና። ይህ ተግባር አገርን የማፍረስ ተልእኮ እንጂ።

መንግሥትም ሆነ ሕዝብ ይህንን ችግር የአንድ ቤተክርስቲያን ጉዳይ ብቻ አድርጎ ማየት የለበትም። ምንአልባት ዛሬ ኦርቶዶክስ እና ሙስሊም በእምነቱ ምክንያት ተገድሏል ያልን እንደሆነ የትናንቱን የሌሎች ቤተእምነቶች መቃጠል እና የምእመናን ሞት አንዘንጋ። ነገም የተደገሰልን እልቂትና ውድመት ሊኖር ስለሚችል በአንድነት በመቆም አገርንና ሕዝብን ልንጠብቅ ይገባል።

ችግሩ ዘላቂ ባይሆንም መስቀሉ ከተቀበረበት እስኪወጣ ክልከላዎች እስኪነሱ ቆሻሻውን ከመድፋት ይልቅ ማንሳት ላይ እስካልተረባረብን ድረስ ይቀጥላል።

ስለዚህ አገርንና ቤተክርስቲያንን ለመታደግ መሰባሰባችንን አንተው። ቆሻሻ (ብልሹ አሰራርን፣ ሙስናን፣ ስልጣንን አላግባብ መጠቀምን፣ ዘረኝነትን፣ ተረኝነትን፣ የግል ጥቅም ማስቀደምን) መስቀሉ የተቀበረበት ቦታ መጣልን እናቁም እንዲህ እያደረግን የምንቀጥል ከሆነ የቤተክርስቲያንን እና የአገርን ትንሳኤ ቀን እናረዝመዋለንና።

ንግሥት እሌኒ መስቀሉን ከተቀበረበት ለማውጣት ወራት የፈጀባት ሕዝቡ የጣለው የቆሻሻ ክምር ብዛት ነው። እንዲሁ ለኢትዮጵያ ትንሳኤ መቅረብም ሆነ መራቅ ምክንያቱ እኛ በምናጠራቅመው አይነት እና የቆሻሻ ብዛት ስለሚወሰን ጥንቃቄ እናድርግ።

መስቀሉ የሚወጣበት የመዳን ቀን የሚቀርብበት የሰወች እኩልነት የሚረጋገጥበት ቀን እንዲቃረብ ተራራውን ለመናድ፣ መስቀሉን ለማክበር ቁፋሮውን እንቀላቀል።

በየሙያ መስካችን በየተሰማራንበት ተራራውን እንናድ፤ (ጥላቻ፣ መከፋፈል፣ መጠቃቀም፣ ወዘተ) ይወገድ። ያኔ የመስቀሉም የሆነ የኢትዮጵያ ክብር ይገለጣል። ብዙዎች ይፈወሳሉ። ይድናሉ። ጎባጣው አሰራር ይቀናል፣ ለምጻሙ ይነጻል፣ የሞተ ተስፋችን ይለመልማል፣ እውሩ አመራራችን ይስተካከላል። እንባችን ይታበሳል።

ሕዝብና መንግሥትም በሰላም እጅ ለእጅ ተያይዞ ለልማትና ለሰላም ይሰለፋል። ኢትዮጵያ አገራችን ቁጥር አንድ ታላላቅ አገሮች አንዷ ትሆናለች። ኢትዮጵያውያን የስደት መከራቸው ማብቂያ ያገኛል። አማንያን በሰላም አምልኮአቸውን ያከናውናሉ። ነጋዴ ነግዶ አርሶ አደር አርሶ አርብቶ አደር አርብቶ ሰርቶ አዳሪ ሰርቶ ያልፍለታል። አውርቶ አደር እና አባልቶ/አዋግቶ አደሮች ቦታ ያጣሉ። በነው ከስመው ይጠፋሉ።

መስቀል መከራ ቢሆንም ቅሉ እኒህን ሁሉ የማሸነፍ ሃይል ስላለው ሁሉን ድል አድርጎ በአሉን በሰላም የምናከብርበትን ዘመን ቅርብ ያድርግልን።

በፍጹም መንፈሳዊ ቅናት ፍትሕን እንፈልግ፣ በፍጹም ትሕትና መፍትሔ ለማግኘት እንምከር። ከንግሥት እሌኒ የምንማረው በትህትና ወደ አባቶች ለምክር መቅረብን፣ በመንፈሳዊ ቅናት ለአግልግሎት መሯሯጥን፣ ለአገር ከፍታ ከክብር ዝቅ ማለትን ነውና። ዝቅ ብለን አገርን ከፍ እናድርጋት።

ከአጥብያ ቤተክርስቲያን እስከ ቅዱስ ሲኖዶስ የሚጠበቅበትን ያድርግ እያደረገም ይገኛልና እኛም የበኩላችንን እንወጣ።

በጾም፣ በጸሎት፣ በምሕላ፣ በሱባኤ፣ በንሰሐ፣ እግዚአብሔርን ምላሽ ልንጠይቅ መንግሥትንም በመደራጀት በሥርአት እና ሕጉን ተከትሎ በመንፈሳዊ ሥነምግባር መብታችንን ልንጠይቅ ይገባል።

የጌታዬ የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል ሆይ የጥፋት ጭለማ ውጦናልና ወዴት አለህ? በሚያጠፉን ጠላቶቻችን ተከበናልና ወዴት አለህ? ገጸ ምሕረትህ ወደኛ ትመለስ።

መስቀል ለእኛ ለምናምን ሃይላችን ነው፣ መድኋኒታችን ነው፣ የክብራችን መገለጫ ነው።

እውነት እንዳይደበቅ አጋሩት።
ይቆየን።

በቴሌግሬም ገጽ ለመከታተል

@deressereta

ቅዳሜ 22 ኦገስት 2020

+ እግዚአብሔር እንዴት ይፈርዳል? +



+ እግዚአብሔር እንዴት ይፈርዳል? + 
(ጊዜ ወስደው ያንብቡት አያጥር ነገር ታሪክ ሆኖ ነው)
አንድ ግብፃዊ መነኩሴ ለገዳሙ መርጃ የእጃቸው ሥራ የሆኑትን ቅርጫቶች ሊሸጡ ወደ እስክንድርያ ለመጓዝ በጠዋት ተነሡ፡፡
በመንገድ ላይ ታዲያ ትልቅ የቀብር ሥነ ሥርዓት ለማድረግ የሚጓዝ ሕዝብ ገጠማቸው፡፡ ሟቹ ዝነኛ አረማዊ ገዢ ሲሆን በዘመነ ሰማዕታት በሺህ የሚቆጠሩ ክርስቲያኖችን የገደለ ሰው ነበር፡፡ አሁን ዕድሜ ጠግቦ ሞቶ ነው፡፡ ቀኑ ውብ ፀሐያማ ቀን ነበርና የሀገሩ ዜጎች በነቂስ ወጥተው ገዢያቸውን እየቀበሩ ነው፡፡
ይህንን ያዩት መነኩሴ ጉዳያቸውን ፈጽመው ወደ ገዳም ሲመለሱ አሳዛኝ ዜና ሰሙ፡፡ ለስድሳ ዓመታት በበረሃ በብሕትውና ቅጠልና የበረሃ ፍሬ ብቻ እየበላ የኖረ ባሕታዊ በዚያች ዕለት በጅብ ተበልቶ ሞቶ ነበር፡፡
መነኩሴው እጅግ ጥልቅ ኀዘን ውስጥ ሆነው እንዲህ ሲሉ አሰቡ ፦
‘በሺህ የሚቆጠሩ ክርስቲያኖችን የገደለው አረማዊ ሰው በታላቅ ክብር ታጅቦ ሲቀበር ሕይወቱን ሙሉ በጾምና በጸሎት ፈጣሪውን ያገለገለው ባሕታዊ በጅብ ተበልቶ የተዋረደ አሟሟት ሞተ፡፡ይህ እንዴት ዓይነት ፍርድ ነው? እግዚአብሔር ከመልካምነቱ ሁሉ ጋር ኢፍትሐዊ ነገሮች ሲሆኑ ዝም ብሎ ይፈቅዳል፡፡ በዚህ ምክንያት ብዙ ሰዎች የፈጣሪን መኖር ይጠራጠራሉ፡፡ እኔም ፍርዱን እንዲገልጽልኝ መጸለይ ይኖርብኛል’ አሉ፡፡
ከዚያች ቀን ጀምሮ መላልሰው ወደ ፈጣሪ ‘’ፍርድህን ግለጽልኝ’ ብለው ደጋግመው ጸለዩ፡፡ ብዙም ሳይቆይ እግዚአብሔር ፍርዱን እንዲህ ገለጠላቸው፡፡
ከሳምንታት በኋላ እንደተለመደው ወደ እስክንድርያ የሦስት ቀን ጉዞ ሊሔዱና ቅርጫታቸውን ሊሸጡ ተነሡ፡፡መንገዱን እንደጀመሩ ድንገት አንድ ወጣት መነኩሴ ወደ እርሳቸው ሲመጣ ተመለከቱ፡፡
‘’አባቴ ይባርኩኝ’
‘እግዚአብሔር ይባርክህ ልጄ’
‘አባቴ ወዴት ይሔዳሉ?’ አለ ወጣቱ መነኩሴ
‘ወደ እስክንድርያ ቅርጫቴን ልሸጥ እየሔድኩ ነው’ አሉት
‘ጥሩ አጋጣሚ ነው አባ እኔም ወደዛ እየሔድኩ ነው’ አለ በትሕትና
‘ጎሽ አብረን እንጓዛለና’ አሉ አባ፡፡ ወጣቱ መነኩሴ ከእጃቸው ሸክማቸውን ተቀበለ፡፡ ጥቂት እንደሔዱ እንዲህ አላቸው፡፡

የአዳል በግ

 

አንዱ ደወለልኝና የአገራችን ደቡባዊት ከተማ ስም ጠራልኝና እዛ ከተማ ውስጥ እና ዙርያዋ የሚገኙ ወጣቶች የአዳል በጎች ናቸው እንዴ? አለኝ።
እኔ እስከማውቀው የአዳል በግ ባለቤት/ባለበጉ ያልሆነ ከግልገልነት እስከ ሙክትነት እድሜው ዘወር ብሎ ያላየው ገዝቶ እየነዳ ወስዶ የሚያተርፍበት፣ የገዛ አርዶ አወራርዶ ነግዶ የሚያተርፍበት፣ ሌላው የደላው ደግሞ በልቶ ከርሱን የሚሞላበት ነው።
ሻጭም በርሱ ስሜት እየለካ በጉን ብሔርና ክልል ይሰጠዋል፤ ከበግነት ማንነት የአዳል በግነት መለያ ያላብሰዋል።የበጉን ሥጋና ቆዳ አዋዶ ይሸጠዋል።
ይሕንን የዋህ ሲጠሩት አቤት፣ ሲሸጡት ገዢን ተከትሎ የሚሄድ፣ ሲያርዱት ለምን ብሎ በማይጠይቅ በግ ለሰው የተመሰለው፤ ለዚያውም በክፉ ሰው ከሰውነት ልክ በወረደ ክብርን ጠርቶ ውርደትን በመረጠ ሰው አለማቀፋዊ ማንነቱን በውስን ሥፍራ በጠባብ መንደር በብሔር የተሸበበ ሰውን ይወክል ዘንድ የተገደደ በግ ነው። የአዳል በግ።
እነዚህ ሰወች ደግሞ ከሰውም ይልቅ ለአውሬነት የሚቀርቡ፣ አውሬያዊ ጸባይ ያላቸው። ሰውን ቁልቁል ዘቅዝቀው የሚሰቅሉ፣ ብሔርን መሰረት አድርገው ለይተው ገድለው አስክሬንን የሚያክል ነገር ያለ ባህላችንና እምነታችን መሬት ለመሬት የሚጎትቱ፣ እንደ አገር ድሃ እና ለማኝ አገር፣ እንደ ሕዝብ ለሰው ልጅ የሚገባውን የተመጣጠነ ምግብ መመገብ አይደለም በአግባቡ በልተን የማናድር፣ እንዲሁ ብሔርና ሐይማኖትን መሠረት በማድረግ ሐብት ንብረትን ለማውደም እንደ መንጋ የሚነዱ፣ መንግሥትን ያህል ተቋም በጥቅም በመገዛት ለዚያውም ለጠላት አገር መንግሥት ለመገልበጥ ላይ ታች የሚሉ የሰው እንክርዳዶች።
እነዚህ ናቸው በየዋሁ በግ የተመሰሉት፤ በአንድ በኩል እውነትም ሲታዩ በጎች ናቸው ለሚያርዳቸው የሚታዘዙ፣ ገድሎና ዘልዝሎ ሊበላቸው ከቋመጠ ጋር የሚውሉ። በሬ ካራጁ እንዲሉ። ክፋታቸው እንዳለ ሆኖ ያሳዝናሉ።
እንደ በግ ግር የሚሉ፣ የማያስቡ የማያስተውሉ፣ የሚጠቅማቸውን ለይተው የማያውቁ። ከትናንት ውድቀትና ስህተት የማይማሩ። አልፎ ተርፎ ከራሳቸውም ሥህተት ጭምር የማይማሩ።
ይህ ጓደኛዬ ስለነዚህ ወጣቶች ሲያወራልኝ በስሜት ነበር በውስጡ የሚንተከተከው ደም የቆዳውን ከለር እስኪቀይር ነበር ደሙ ፈልቶ በስሜት እያወራኝ ያለው።
እውነት ግን ምን ሆነናል?
ምንስ እየሆንን ነው?
ምንድን ነው የነካን?
እስከማውቀው ኢትዮጵያዊነት እንዲህ አልነበረም፤ እርግጥ ነው ጥንትም አንዳንድ አገርና ሕዝብን ለጥቅም ሲሉ አሳልፈው የሚሸጡ አሉ። ነበሩም በመጠን እና በይዘታቸው ግን ይሕን እንደማያክሉ የታሪክ ድርሳናት ይመሰክራሉ። "የአበሻ ጀብዱ" የሚለው መጽሐፍ ቋሚ ምሥክር ነውና።
ይህ ተግባር ጓደኛዬ በጠቀሳት አንዲት ከተማ የተወሰነ የተወገዘ ተግባር ብቻ አይደለም። ዋና ከተማችንን ጨምሮ እንጂ።
የወደሙ ሐብት ንብረቶች፣ የሞቱ ሰወች፣ የጎደለ አካል ከአንድ የጦርሜዳ ውሎ በላይ ነው። እንደ አገርም እንደ ሕዝብም በአለም መድረክ የተዋረድንበት። ገዳይም ሟችም እኛው ራሳችን ... የሆንበት አሳፋሪ ተግባር።
የሚላስ የሚቀመስ የሌለው መናጢ ድሃ ወጣት ንብረት ሲያወድም የሥራ ገበታው ሥራ አጥ ወገኖቹ ሰርተው ደመወዝ አግኝተው ቤተሰብ የሚያስተዳድሩበትን ሥፍራ ቋሚ እና ተንቀሳቃሽ ንብረት የሚያቃጥል።
በደጉም በክፉም ጊዜ ጸጥታ በማስፈን፣ ሰላማችን እንዳይደፈርስ ዘብ የሚቆሙ የጸጥታ አካላትን መግደል፣ አካል ማጉደል ያጎረሰ እጅ ነካሽነት ነው።
ለነዚህ አረመኔዎች የአዳል በግነት ምግባራቸውን የሚገልጥ የነውረኝነታቸው መገለጫ ሥም ሳይሆን የክብር ሥም ነው የሚሆነው። ለአዳል በጎች ደግሞ እንዲህ ጭካኔ በተሞላ ተግባር በሚሰማሩ ከሰውነት ክብር በወረዱ በመንጋ በሚያስቡ በመንደር በተወሰኑ ወጣቶች መመሰል ስድብ ነው።
ቀጣይ ትውልድ የማፍራት ተግባር ላይ ቤተሰብ ትልቅ ድርሻ እንዳለው እሙን ነው በመቀጠል የአካባቢው ማህበረሰብ የሐይማኖት አባቶች የአገር ሽማግሌዎች የትምህርት ቤት መምህራን ወዘተ እያለ ይቀጥላል። እስከ ማስታውሰው እነዚህ አካላት በኔ ማንነት ውስጥ ድርሻቸውን ስለምገነዘብ ለነዚህ አካላት ትልቅ ክብር ነበረኝ። እነርሱ በውስጤ ባሰረጿት የአንዲት ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያዊነት ውስጤ በፍቅር ብርሃን ይንቦገቦጋል የመንደርተኝነት ጨለማ አልዋጠኝም። "ኑ ቡና ጠጡ" የምትል የመልእክት ድምጽ ከወላጆቼ እንደሰማሁ በቀጫጭን እግሮቼ ብን ብዬ በርሬ ዘር፣ ቀለም፣ ሐይማኖት፣ ብሔር ሳልለይ ቡና ጠጡ ብዬ ከመጥራት ወዲያ መከፋፈልን ባላየሁበት ማህበረሰብ ውስጥ እንዴት ዛሬ በሐይማኖት፣ በብሔር ተከፋፍሎ ጸብ ግድያ ማፈናቀል ንብረት ማውደም ከየት መጣ?????
ማንስ በመካከላችን የሐሳብ እንክርዳድ ዘር ዘራ?
የሐይማኖት መምህራን በምሣሌ ሲያስተምሩ አንድ ገበሬ መሬቱን አርሶ አለስልሶ ስንዴ ዘራበት ሰብሉ ከቡቃያነት አልፎ ከፍ ማለት ሲጀምር እርሻውን ቢመለከት አረም ወርሮታል እንደልማዱ ቤተሰቡን ሰብስቦ የአከባቢውን ሰው ደቦ ጠርቶ የበቀለውን አረም አረመው። በመቀጠልም የዘራው ዘር አብቦ ካፈራ በኋላ ተመልሶ ቢመለከተው ንጹሕ የስንዴ እርሻ በእንክርዳድ ተወርሯል። የእምነት መምህራን ይህንን የስንዴ እርሻ በእንክርዳድ መወረር አመስጥረው ሲያስተምሩ "እንክርዳዱን" የዘራው ጠላት ሰይጣን እንደሆነ ያስተምራሉ።
በዚህ ትውልድ መካከልም የሰው ልጅ እንደ ሰው ሲፈጠር እንዲህ በመከፋፈል ሳይሆን ከአንድ አዳም እንደተገኘን አሁንም የእምነት ተቋማት የሥነ ፍጥረት ትምህርት አስተምህሮ ያስረዳናል። እንዲህ በመከፋፈል እንድንባላ እንድንጋጭ አንዱ ሌላኛውን እንዲያሳድድ ንብረት እንዲያወድም አገር እስከ ማፍረስ የሚያደርስ ግጭት እንዲፈጠር የሚያደርጉ ተግባራት ይከናወናሉ። ይህን እንዲሆን ማን አደረገ? ካልን ሁላችንም የምንገነዘበው የሰይጣንን ተግባር የሚተገብሩ በትውልድ መካከል የእንክርዳድ ዘርን የሚዘሩ አክቲቪስቶች፣ ፖለቲከኞች፣ "ከእውቀት ነጻ " ምሁራን ተብዬዎች፣ ሚዲያዎች ወዘተ ናቸው።
ችግሩን ማወቅ የመፍትሔው አጋማሽ ነው እንዲሉ ምሁራን ትውልዱ ራሱን እንዲህ በውስጣችን እንክርዳድ የሚዘሩትን ምን ማድረግ ይጠበቅበታል? መንግሥት? የእምነት አባቶች፣ የአገር ሽማግሌዎች፣ ወዘተ ምን ያድርጉ?
አስቀድመን እንደተናገርን በስንዴ እርሻ ውስጥ የበቀለውን የእንክርዳድ ዘር ገበሬው በመኸር ወቅት ስንዴውን ከእንክርዳዱ በጥበብ እንዲለይ በየደረጃው ያለን ስለ ሕዝባችን ሃላፊነት የሚሰማን ግለሰብ እና በተለያየ የመንግሥት ሃላፊነት በመውሰድ ሠላም የማስፈን፣ ጸጥታ የማስከበር፣ ሕግን የማስከበር ተግባር ላይ የተሰማሩ አካላት በጥበብና በማስተዋል እራሳችንንና ወገናችንን ከጠላት ዲያቢሎሳዉያን ልንጠብቅ እና ልንከላከል ይገባል።
ወደ መሬት ስናወርደው ሕብረተሰቡ የሚደርሰውን መረጃ ከማህበራዊ ሚዲያ፣ ከኤሌክትሮኒክ ሚዲያ፣ ከህትመት ሚዲያ፣ ወዘተ የምናገኛቸውን መረጃዎች ብስል ከጥሬ መለየት የሚጠቅመውን ከማይጠቅመው፣ እውነተኛውን ከሐሰተኛው መለየት ይጠበቅበታል።
ሕዝብን ከጥፋት አገርን ከመበታተን ሐብትና ንብረትን ከውድመት የሚታደጉ የጸጥታና የደህንነት አካላት አገርንና ሕዝብን ለመታደግ ያገኙትን ሳይንሳዊ ጥበብ ፖለቲከኞችን እና መሪዎችን ከመጠበቅ፣ ተፎካካሪዎችን መረጃ ከመጥለፍ እና ከማገት ተጠብቀው አገርን እና ሕዝብን ከጥፋት ለመታደግ የእለት ተለት አገር ውስጥ የሚሰራጩ መረጃዎችን በማሰስ በመተንተን ጥፋት ከመፈጠሩ ንብረት ከመውደሙ የሰው ህይወት ከማለፉ አስቀድሞ ሊያከሽፍ ጥፋተኛውንም በቁጥጥር ሥር ማዋልና ለሕግ ማቅረብ ይኖርበታል።
የሕግ አስፈጻሚ አካላት እና በተለያዩ ተግባራት ላይ የተሰማራው ባለስልጣን ህግን ከለላ በማድረግ ጥፋት ላይ የተሰማሩትን ፈቃድ ከመስጠት በዘለለ የየእለት ተግባራትን ትክክለኛነት መመዘን፣ እርምትና እርምጃ መውሰድ ይጠበቅባቸዋል። ይህንን ካልከወንን ጥፋቱ ቀላል አይሆንምና። እንደ ምሳሌ ብናነሳ በማህበረሰብ መካከል የመከፋፈል ቅስቀሳ የሚያደርጉ ሚዲያዎች አስቀድመው ሕጋዊ ከለላ ለማግኘት በሕጋዊ መልኩ ፈቃድ ወስደው ሥራ ጀምረዋል። ግብር ይከፍላሉ። ሕግ ባለበት አገር ውስጥ ሕጋዊ መስለው ይንቀሳቀሳሉ። ይህ ብቻ በቂ አይደለም። ብሮድካስት ባለስልጣን በየወቅቱ ሥራቸውን መፈተሽ፣ እርምት መውሰድ፣ እርምጃ መውሰድ፣ ወዘተ ይኖርበታል። ይህ ሳይሆን ሲቀር ግን የሚደረገው ሩጫ "ጅብ ከሄደ ውሻ ጮኸ" ይሆንብናል። እነርሱ የተቋቋሙበትን አላማ ካሳኩ በኋላ ማስጠንቀቅያ መሥጠት፣ ለመዝጋት መሯሯጥ በሕዝብ ላይ መዘባበት ይሆናል። ሌሎችም እንዲሁ ተጠቅሰው ተዘርዝረው የማያልቁ አስቀድመን አስበን በመከወን ከጥፋት ልንታደግ የሚገቡ ተግባራት አሉን።
ብዙውን ጊዜ እንደታዘብኩት ከሆነ አንድ ነገር ከሆነ በኋላ ህጉን ስንተች ስለ አገሪቱ ሕግ መላላት ስናወራ ይደመጣል። እንደ ኢትዮጵያ ከ98% በላይ ሐይማኖተኛ በሆነ ማህበረሰብ መካከል ስለ ምድራዊ ሕግ መጨቃጨቅ ለኔ ውሃ የማያነሳ ሀሳብ ነው ምክንያቱም እንደ ሐይማኖተኛነታችን እምነትን እንደተቀበለ እና እንደመንፈሳዊ ሰው ምድራዊ ሕግ ለሰው ልጅ ኢምንት ነውና። ምድራዊ ሕግ ስለ መደፈር ፍትሕ ከመስጠቱ በፊት መረጃና ማስረጃ ይሻል። መንፈሳዊ ሕግ ግን ስለ ዝሙት "ያየ የተመኘ አመነዘረ" ይላል። በእምነት ጥላ ሥር ላደገ ማህበረሰብ ሴትን ልጅ ለመድፈር አይነሳሳም። ሕጉ ላልቷል ሥጋት አይሆንበትም። ሕጉን ሳይሆን የሚያወግዘው ዝሙትን ነውና። ስለዚህ የእምነት ተቋማት እና የእምነት ተቋማት መምሕራን ትውልድን በመቅረጽ ላይ ድርሻና ግዴታ አለባቸው። እንዲህ ስንል ግን በእምነት ስም የሚነግዱትን ስመ አምላክ ነጋድያንን ልብ ልንል ይገባል። እነርሱም የትውልዱ ነቀርሳዎች ስለሆኑ።
እንግዲህ እንደ በግ እንዳንነዳ ምን እናድርግ?
በግ ላለመሆን ያለን ብቸኛ አማራጭ ሰው መሆን ነው።
ሰው ስንሆን:-
እንደ ሰው እናስባለን
እንደ ሰው እንኖራለን
ሰዋዊ እሳቤ ይኖረናል
እንተሳሰባለን
እንከባበራለን
በሐሳብ የበላይነት እናምናለን
የሰውን ክቡርነት እናምናለን
ለሕግ እንገዛለን
በጥቅም አንገዛም
አገርና ሕዝብን አንሸጥም
ሕዝብን ለፖለቲካ ፍጆታ አናባላም
ንብረት አናወድምም
አካል አናጎድልም
ሕይወት አንቀጥፍም።
ሰው ክቡር ሆኖ ሳለ አያስተውልም እንስሳትን መሰለ እንዲል እኛም ወደ ማስተዋል ተመልሰን እንደ ሰው እንኑር።
ደረሰ ረታ
ሐምሌ 7/2012

እንደ ሰው ልንኖር

 

የከሰል ጭስን አደገኝነት አውቆ ከሰልን የሚፈራ እና የሚጠላ ከመሸ በኋላ ከሰል አቀጣጥሎ ቤቱ አስገብቶ የሚቆልፍ ሰውና በዘር/ብሔር /በሃይማኖት ግጭት የሚመጣን እልቂት የሚጠላ ነገር ግን ጸቡን የሚያቀጣጥል ሰው ይመሳሰሉብኛል።
መቸስ ግጭት አንዴ ከተቀጣጠለ በኋላ አደጋ እንዳያደርስ የሚያደርግ ብልሃት እንደሌለው አገር ያወቀው ጸሃይ የሞቀው ነው።
አሳን መብላት በብልሃት እንዲሉ ማንኛውም ግጭት ዋስትና የለውምና ሁላችንም ከብሔራችን ሰውን አስቀድመን እንተዛዘን እንከባበር።
እዚህ ቤት ያለ እሳት እዛም ልብ እያልን ቢሆን መልካም ነው።
ዛሬን ለመኖር ትናንትን ምክንያት በማድረግ ከነገ መጨናገፍ ኋላቀርነት ነው።
ትናንት ጡት ተቆረጠ በሚል ትርክት ዛሬ እየቆረጡ ነገን ማበላሸት የትናንት ትርክት እውነት እንኳን ቢሆን በዚህ ዘመን እንዲህ አይነት ተግባር መከወን ከትናንቶቹ እጅግ አንሶ መገኘት ነው።
ትናንት በባሪያ ንግድ ዘመን አባቶቻችን ይህን ኋላቀርነት ለማስቀረት ብዙ ዋጋ እንዳልከፈሉ ዛሬ አለም በዘመነበት ሰአት እንዲህ እንደ ግመል ሽንት ወደ ኋላ መሄድ ነው። ድርጊታችንም ሰወች እንዲህ አድርጉ እያሉን እንደ ሮቦት ሳያገናዝቡ መነዳት ዘመናዊ ባርነት ነው።
እምቢኝ ብለን ወደ ኋላ ዘመን የሚያስጉዙንን ልናወግዛቸው የተልእኳቸው አስፈጻሚ ከመሆን በመቆጠብ አገራችንን በልማት እና በሰላም ማስከበሩ ጎን ልንቆም እንደ ፍጥረታችን እንደ ሰው ልንኖር ይገባል።
ደረሰ ረታ
ሐምሌ 29/2012

ለራሳችን ያለን አመለካከት- SELF IMAGE

 ለራሳችን ያለን አመለካከት-

 SELF IMAGE 

****************************************************************

ከምንም በላይ አንዳችንን ከሌላኛችን የሚለየን ነገር ቢኖር ለራሳችን ያለን አመለካከት ወይም ምስል በእንግሊዘኛው ደግሞ Self Image ነው። የስነ ልቦና ባለሙያዎች ስለዚህ የስነ ልቦና ጥበብ መጀመሪያ ባጠኑበት ወቅት፤ ታላቁ የስነልቦና ግኝት ብለውት ነበር። ሁላችንም በዚህ አለም ላይ ስንኖር የኑሮዋችን መጠንና ልኩ የሚወሰነው ለራሳችን ባለን አመለካከት ወይም በአይምሮዋችን ውስጥ ስለራሳችን በምንቀርጸው ምስል ነው። ባህሪያቶቻችን፤ ውሳኔዎቻችን፤ አጋጣሚዎቻችንና በህይወታችን የምንስባቸው ሰዎች በሙሉ ለራሳችን ባለን አመለካከት ተጽዕኖ ስር ይወድቃሉ።
ለራስ የሚሰጥ አመለካከት (self Image) በህይወታችን እጅግ ወሳኝ ነገር ነው። አንድ ሰው ስኬታማና ደስተኛ ሊሆን የሚችለው ለራሱ የተስተካከለና አወንታዊ አመለካከት ሲኖረው ብቻ ነው። ችግሩ ይህንን እውነታ ማንም ሰው ከልጅነታችን ጀምሮ ስለማያስተምረን አብዛኛዎቻችን ለራሳችን የተሳሳተ አመለካከት በመያዝ እናድጋለን። አቅምና ችሎታችንን የሚገድቡ እምነቶች ( Self Limiting beliefs) ሳናውቀው በአይምሮዋችን ውስጥ ስር ይሰዳሉ። እኒህ አመለካከቶቻችን ናቸው የምንፈልገውን ኑሮ እንዳንኖር እንቅፋት የሚሆኑብን።
“እርሱ እችላለሁ የሚለውም፤ አልችም የሚለውም ሁለቱም ትክክል ናቸው”- ኮንፊሺየስ
ህይወታችንን ሊቀይሩ የሚችሉ እውነታዎች በሙሉ ቀላልና ያልተወሳሰቡ ሀሳቦች ናቸው። ምናልባት ለዛም ይሆናል በቁም ነገር ወስደን የማንተገብራቸው። እኛ ሰዎች በተፈጥሮዋችን የተወሳሰበና ከባድ ነገር ይበልጥ ተዓማኒነት ያለው ይመስለናል። ለችግሮቻችን መፍትሄ ስንፈልግ እንኳን ቀለል ያለ ሃሳብ አንቀበልም። እቃ ስንገዛ የተወደደው እቃ ሁሌም ከረከሰው የተሻለ ይመስለናል፤ በወረፋ ካልተሰለፍን በቀር የምናገኘው አገልግሎት ጥራት ያለው አይመስለንም። ተሻምተን ካላገኘናቸው በቀር ነጻ ለምናገኛቸው ነገሮች ዋጋ አንሰጥም። እራሳችንን ለመለወጥ ስናስብም እንደዛው፤ በቀላሉ አስተሳሰባችንን በመቀየር ህይወታችንን መቀየር እንደምንችል አምነን መቀበሉ ይከብደናል። ሰው አስተሳሰቡን በመቀየር ኑሮውን መቀየር እንደሚችል ለብዙ መቶ አመታት ሲንገር የነበረ ቢሆንም፤ ግልጽና ቀልላ ሀሳብ ስለሆነ ነው መሰል እምነት አንጥልበትም።
እያንዳንድችን ስለራሳችን በአይምሮዋችን የምንቀርጸው ምስል አለ። ይህ ምስል መልካም ምስል ካልሆነ በኑሮዋችን ላይ የሚጸባረቁት እውነታዎችም ከዚህ ምስል የተለዩ አይሆኑም። በተቃራኒው ስለራሳችን ያለን አመለካከት ወይም በውስጣችን የምንስለው ምስል መልካም፤ጠንካራና አወንታዊ ከሆነ፤ በኑሮዋችን ላይ የሚንጸባረቁት እውነታዎች በሙሉ የአወንታዊው አመለካከታችን ነጸብራቆች ይሆናሉ። ይህ ለራሳችን የምንሰጠው አመለካከትና ግምት ነው፤ በራሳችን ላይ የሚኖረንን እምነት የሚወስነው። በራስ መተማመናችን የሚበቅለው ለራሳችንን ባለን አመለካከት አፈር ላይ።
በትምህርትም ሆነ በስራ፤ በፍቅርም ሆነ በግል ህይወታችን ውስጥ የምናገኛቸው ውጤቶች ለራሳችን ካለን አመለካከት የሚመነጩ ናቸው። ምናልባት እዚህኛው ጽሁፌ ላይ ትንሽ ስለራሴ መናገር ያለብኝ ይመስለኛል። ከአመታት በፊት ስለራሴ የነበረኝ አመለካከትና አሁን ስለራሴ ያለኝ አመለካከት እጅግ የተራራቁ ናቸው። ለራሴ አነስተኛ አመለካከት በነበረኝ ወቅት ብዙ ነገሮችን “በአልችልም” ስሜት ሸሽቻለሁ። አቅሜን ባለማወቄ ከሚገባኝ በታች የሆኑ ነገሮችን አሜን ብዬ ተቀብዬ ነበር። የተሻለ ህይወት ለሌሎች እንጂ ለእኔ የሚገባኝና የሚቻል ስላልመሰለኝ እራሴን ወደኋላ ጎትቼዋለሁ። ሆኖም ግን እራሴ ላይ መስራት ከጀመርኩኝ ጀምሮ ( After I embarked on the journey of personal development) ኑሮዬ የሚወሰነው ለራሴ ባለኝ አመለካከት መሆኑን ለመረዳት ግዜ አልፈጀብኝም። ደስታና ስኬት፤ ፍቅርና ክብር፤ መውደድና መወደድ ለሁላችንም የቀረቡ ገጸ በረከቶች ናቸው። ለራሳችን አወንታዊ አመለካከት ሲኖረን ብቻ ነው እኛም እንደማንኛውም ሰው ከኒህ ገጸ በረከቶች የፈለግነውን ያህል መቋደስ እንደምንችል የምናምነው።
ለራሳችንን ያለንን አመለካከት መለወጥ እረጅም መንገድ ነው (It’s a Never Ending Process)። ምክንያቱም ስለራሳችን በውስጣችን የምንስለው ምስል የተሳለው በእኛ ብሩሽ ብቻ አይደለም። ቤተሰብ፤ ማህበረሰብ፤ ጓደኛ፤ አስተማሪ እንዲሁም ሌሎች አጋጣሚዎች የየራሳቸውን አሻራ አኑረውበታል ወደፊትም ከተጽዕኖ ሙሉ በሙሉ ማምለጥ አንችልም። ሆኖም ግን አመለካከታችንን የመለወጥ ሙሉው ሃላፊነት የማንም ሰው ሳይሆን የራሳችን ብቻ መሆኑን ማመን መቻል አለብን። ይህ እምነት የመጀመሪያው እርምጃ ስለሆነ።
ስለራሳችን ስናስብ የሚመጣብን ምስል አወንታዊ ካልሆነ በእርግጠኝነት አመለካከታችን ለማስተካከል እራሳችን ላይ መስራት አለብን ማለት ነው። በአይምሮዋችን ውስጥ የምንፈልገውን ኑሮ መኖር እንደማንችል የሚነገርን ድምጽ ካለ፤ በፍርሃትና በአልችልም ስሜት የሚያስፈራራን ምስል በውስጣችን ካለ፤ ለራሳችን ያለንን አመለካከት የተሳሳተ እንደሆነ የሚያረጋገጡልን ምልክቶች ናቸው። ለራሳችን የምንሰጠው አመለካከት የኑሮዋችን ካርታ ነው። አወንታዊና ገንቢ አመለካከት ሲኖረን አቅጣጫችን ወደ ተሻለ ህይወት ነው። በተቃራኒው ለራሳችን ያለን አመለካከት ዝቅተኛ ከሆነና ስለራሳችን ስናስብ አሉታዊ ምስል የሚቀረጽብን ከሆነ እየተጓዝን ያለነው ወደማይጠቅመን ጎዳና ነው። ደስተኛ ለመሆን የተስተካከለ አመለካከት ወሳኝ ነው፤ ስኬታማ ለመሆን ስለራሳችን አወንታዊ ምስል በውስጣች ሊኖር ግድ ይለናል። ይህ ሀሳብ እጅግ ሰፊ ነው፤ ጽሁፌን ግን ማንዴላ በእስር ሳለ ብርታት ይሰጠው ከነበረው ድንቅ ግጥም ውስጥ በተወሰደች ስንኝ ልቋጭ።
“እኔ ነኝ የእድሌ ወሳኝ፤ የእጣ ፋንታዬ መሪ
የነፍሴ ጀልባ ቀዛፊ፤ የኑሮዬ ሹፌር ዘዋሪ”
“It matters not how strait the gate,
How charged with punishments the scroll.
I am the master of my fate:
I am the captain of my soul.”- Invictus poem by William Ernest Henley.
@mindsetethiopia

እራስን ተጠያቂ ማድረግ መለማመድ (ክፍል ስድስት)

 

ይህቺ ምድር መሽቶ እስኪ ነጋ ነግቶ እስኪመሽ ጉድ ነው የሚሰራባት አስቀድሜ እንደነገርኳቸው ትንንሾች ትልቅ የሆኑ የሚመስላቸው ትልቁን ሲያጠፉ፣ አንገት ሲያስደፉ፣ አገር ሲያጠፉ፣ ትውልድ ሲያመክኑ ነው።
አንዳቸውም ጠቋሚ ጣታቸውን ወደራሳቸው አያዞሯትም፤ ወደሰው ከመቀሰር ውጪ። ራስን ለማየት አልታደሉም።
በአንድ ወቅት ነው አሉ ሰውየው ሚስቱን አየሻቸው እያለ ወደ ጎረቤትየው ቤት ያመለክታታል ሚስትም ወዳሳያት ትመለከታለች። ታጥቦ የተሰጣው ልብስ በደንብ እንዳልታጠበ የጎረቤታቸው ሴትዮ ልብስ እንኳን ማጠብ እንደማትችል ይነግራታል። ሌላ ቀንም እንዲሁ ያየውን ያሳያታል ሚስትም አይታ መልስ ሳትሰጠው ትሄዳለች። እንደለመደው በሶስተኛው ቀን ወደ መስኮቱ ይመለከታል ጎረቤቱን ለመተቸት ያየውን ነገር ማመን ይከብደዋል። ሚስቱን ጠራት ያየውን ነገር በመደነቅ ያወራላታል፤ ይህን የማይታመን ነገር አየሽ? ሴትዮዋ ሰራተኛ ቀጥራ ነው ወይስ እንዴት እንዲህ ባለሙያ ብትሆን ነው ያጠበችው የጠራላት? ሚስትም መለሰችለት።
እስከዛሬም ጎረቤታችን ባለሙያ ነበረች ሁሌም ልብስ የምታጥበው ጥርት አድርጋ ነው በዚህ ምንም እንከን አይወጣላትም። ችግሩ ያለው ያየህበት ሁኔታ ያየህበት መንገድ ነበር ችግር የነበረበት።
እቤት ተቀምጠህ በመስኮት ነበር የምትመለከተው የመስኮታችን መስታወት ደግሞ አጽድቼው ስለማላውቅ ቆሽሿል። ከዚህ የተነሳ የጎረቤታችንን ንጹሕ የተሰጣ ልብስ በቆሻሻ መስታወት ውስጥ ስታየው ቆሻሻ መሰለህ። ችግሩ ከልብሱ አልያም ከአጣቢዋ ሳይሆን ካየህበት ከኛው መሥታወት መቆሸሽ ነው ብላ ከስህተቱ አረመችው።
ስንቱ ተመልካች ይሆን የራሱን ቆሻሻ እይታ የሌላኛውን ንጽሕና ያጎደፈው?
ስንቱ ይሆን በራሱ ሸውራራ እይታ ቀጥ ያለውን ነገር ያጎበጠው?
ስንቱስ ይሆን በእንደዚህ አይነት ተመልካቾች ውሳኔው የተዛባው? ፍርድ የተጓደለው? ድሃ የተበደለው?
ስንትትቻችውስ ይሆኑ የራሳችው ቆሻሻ እይታቸውን የጋረደባቸው?
በምድር ዛፍ ሆነን ባሳለፍንባቸው ዘመናት አብያተ እምነቶች፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ተቋማት፣ መሪዎች፣ ሕዝቡ፣ ወዘተ ራሳቸውን እንደማየት ጊዜያቸውን ሌሎችን በማየት የሚያባክኑ።
ሁሉም በጉያቸው ትልቅ ችግር ተሸክመው ጠላታችን እገሌ ነው በማለት ጣታቸውን ይቀስራሉ፤ ለዚህ ነው ለችግራቸው መፍትሔ ያላገኙት።
እስኪ በአገራችን የእምነት ተቋማትን ተመልከቱ በውስጥ ችግር ላይ አተኩሮ ከመጠናከር፣ በአንድነት እምነታቸውን ከማጠንከር፣ እርስ በርስ ላይ የተመሰረተ ህብረት ላይ እይታቸውን ከማድረግ ይልቅ እይታቸውን ሌላ ነገር ያተኩራሉ። ሁሉም ከራሳቸው የላቀ ጠላት የላቸውም።
ሁሉም በጉያቸው ብዙ ቁጥር ያለው መናፍቅ፣ ባንዳ፣ ሌባ፣ ተሸክመው ከጥቂቶች ጠላቶች ራሳቸውን ለመከላከል ይጥራሉ። ውጤቱን ገምቱት
እኛም ዛፎች ይህ ችግር ይታይብናል።
ይህ ችግራችን ነው ዛሬ ተሰባስበን ጊዜያችንን እያባከንን የምንገኘው፤ የችግሩን ምንነት ሳንለይ ለመፍትሔ የተሰበሰብነው።
በሰው ዘንድም ብዙ በጀት ተመድቦ፣ ጊዜ ወስደው፣ ጥናት አስጠንተው፣ በስብሰባ እድሜያቸውን ያለ መፍትሔ የፈጁት ከችግር ጋር ተወልደው ያረጁት ምክንያቱ ችግሩን ሳይለዩ ለመፍትሔ ስለሚቀመጡ ነው።
እኛ ጠላት ብለን የተቀመጥነው መሉ በሙሉ የፈረጅነው የሰው ልጅ ነው፤ ነገር ግን በጥልቀት ስንመረምረው የራሳችን ጥመት ተጣሞና ተንጋዶ ማደግ ለመጥረቢያ መመቸት ነው።
ሰውም እንዲሁ ለጥቃት መመቻቸት፣ ተጋልጦ መሰጠት ነው የጎዳቸው እንጂ ሌላ ስራ ፈትቶ እነሱን ለማጥቃት የሚደክም የለም። እስከነ ተረቱም አህያቸውን ውጪ እያሳደሩ ጅብን ነገረኛ ያደርጋሉ እንደሚባለው ነው።
በሉ እንግዲህ ከምንም በፊት እራሳችንን እንመርምር፣ ሌላው ላይ ከመፍረዳችን በፊት ከችግሩ ንጹሕ መሆናችንን እናጥራ፣ የችግሮች ሁሉ መፍትሔ ሩቅ አይደለም ሌላ ቦታ ሳይሆን እኛው ጋር ነው።
ሌሎችን ተጠያቂ ከማድረግ ይልቅ ራሳችንን ተጠያቂ ማድረግ እንለማመድ።
በጎቹን ተኩላ የነጠቀው/የበላቸው እረኛው ችግር ስላለበት ነው፤
ርስታችን የተወረሰው ርስታችንን ምንም ስላልሰራንበት ነው፤
ሌሎች መጥተው የደፈሩን እኛ ስላልተከባበርን ነው፤
የገደሉን ፍቅር ስላልተሰጣጠን ነው፤
ቤታችንን የበረበሩት አጥራችንን ስላላጠበቅን ነው፤
ጠላታችን እኛ ራሳችን ስለሆንን ራሳችንን ማሸነፍ፣ ተጠያቂ ማድረግ እንልመድ፣ እኛ ቀዳዳችንን መድፈን ስንለምድ ጠላትን እንዴት መከላከል እንዳለብን ይገባናል።
ጆሮ ያለው መስማትን ይስማ።
ተፈጸመ።
የዘመንን ወለምታ፣ የትርክትን ስብራት፣ ሸውራራ እይታን፣ በቀና አስተምህሮ እንጠግናለን።
ይከታተሉን።
ሐሳብ አስተያየትዎን ከመስጠት አይቆጠቡ።
መልካም ቀን ይሁንልዎ።
ደረሰ ረታ
ነሐሴ 13/2012 አ.ም

እራስን ተጠያቂ ማድረግ መለማመድ (ክፍል አምስት)

 

ሰው ማለት በ21ኛው ክፍለ ዘመን የሚድያ ሕግ የሚወጣለት፣ የራሱ ጉዳይ ስንት እያለ በየሚድያው ስለራሱ ሳያወራ አንድ ማስታወቂያ ሰምተን እንመለሳለን እያለ ስለቁሳቁስ ትልቅነት ይደሰኩራል፣ አንድም ቀን ስለ ሰው ልጅ ትልቅነት ስለ ዛፎች አስፈላጊነት ጊዜ ተሰጥቶ አይወራም፣ ይኸው አንድ መሪ ከወደ ኢትዮጵያ ቢገኝ እና ዛፍ እንትከል ቢላቸው የሰው ዘር ከምድረ ገጽ እንንቀል ያላቸው ይመስል ጠምደው ይዘውታል። እነ ሥመ አይጠሬ ሰው እናፈናቅል ሲሏቸው አይደለም ቀን ሌሊት ይወጣሉ።
ምድራችን ዛሬም ስለ አስገድዶ መደፈር ሕግ ላይ ይጨቃጨቃል፣ ክቡር የሰው ልጅ መሰረታዊ አስፈላጊ ነገር አልተሟላለትም፣ ረሐብ፣ በሽታ፣ ጦርነት፣ የተፈጥሮ አደጋ፣ ሰው ሰራሽ አደጋ፣ የራስ ምታት ሆኖበታል።
ሰው ምድር ላይ ክቡር ፍጡርነቱ ተዘንግቶ ገራሚ የፊልም ስክሪፕት ሆኗል።
አስቂኝ፤ መሳለቂያ።
ትውልዱ በሰለጠነ ዘመን ቁልቁል ሄዷል፤ ለምን የሚል ከተገኘ መፍትሄው ቅርብ ነው።
እኔ በዘመኔ ገና ችግኝ ሳለሁ አባቶቻችን ትላልቅ ዛፎችና ዋርካዎች በየደብሩ፣ በየገዳማቱ፣ በየመስኪዱ፣ እና በየቄዬው ቁምነገር መገበያያ ነበሩ።
የተጣላ የሚታረቅበት፣ መንገደኛ የሚያርፍበት፣ እረኛ ጸሐይ የሚያበርድበት፣ ታሪክ የሚነገርበት፣ እድር እቁብ የሚጠጣበት፣ እውቀት የሚገበይበት ነበር።
የሰው ልጅ አስተሳሰቡ የተቃኘው ዛፍ ስር ነው፤
እውቀት የገበየው ዛፍ ሥር ነው፤
ሥንትና ሥንት አገራዊ ጉዳዮች ውሳኔ ያገኙት ዛፍ ሥር ነው፤ ጥቅማችን የትዬለሌ ነው። ለዚህ አለም ከመጥፋታችን መኖራችን ነበር የሚጠቅመው። ዛሬ ግን ለራሱ ክብር የነሳው የሰው ልጅ ጥቅማችንን ዘነጋው።
እኛ ዛፎች በጥንት ሰወች እንደሚነገረው ከሰው መርጦ ለሹመት ከእንጨት መርጦ ለታቦት ተብሎ የተነገረልን ነን። የሰው ልጅ ሥለ ራሱ ምን እንደሚያስብ ማወቅ ቢከብድም አሁንም ቢሆን እኛ ዛፎች ትልቅ ነን ስለትልቅነታችን፣ ስለ አስፈላጊነታችን ነው የማምነው። እኛ ከሌለን ፍጥረት መኖር ይከብደዋል። እኛ የምንመኘው ለኛ ሕልውና ሲባል ሰወች እንዲኖሩ ጸሎታችን ነው። የእነርሱን ስለኛ ያላቸውን አመለካከት ባናውቀውም።
ታናናሾቼ ዛፎች ቅድም ወዳነሳሁት ታሪክ ልመልሳችሁና አብዛኛው የእምነት አባቶች ውሎና አዳራቸው ዛፍ ሥር ነበር። ገና ከጨቅላ እድሜያቸው አንስቶ ፊደል የቆጠሩት፣ ምንባብ እና ዜማ የቀጸሉት እኛ ዛፍ ሥር ነው፤ ሥነምግባር እና ብዙ እውቀት የገበዩት እዚሁ ነው።
ታሪክ ያልኳችሁ ዛሬ ይኽ የለም ብዙ የእውቀት መገብያ ወንበሮች ታጥፈዋል፣ የቆሎ ተማሪው ሊቁ ከተማ ገብቶ ሎተሪ አዟሪና ተሸካሚ ሆኗል፣ አድባራትና ገዳማት ሊቃውንት ተራቁተዋል፣ ካድሬ ተሰግስጎባቸው ክብራቸውን አጥተዋል፣ሥለ ፍርድ መጓደል ሥለ ድሃ መበደል የሚሟገት ጠፍቷል፣ እውቀትን እውነትን የሚያስተምር የላቸውም፣ መሥጊዶች ውበታቸው፣ ግዝፈታቸውና ይዞታቸው እንጂ ኡስታዞች ሼኮች ኡለማዎች ሰሚ አጥተዋል።
አደባባዮች የጲላጦስ አደባባይ ሆነዋል ንጹሕ የሚሰቀልባቸው ቆሻሻውና ነውረኛው የሚነግስበት።
ትምህርት ቤቶች ትውልዱ መክኖ የሚወጣበት ከሆነ ከረመ፣ ሥነምግባር አይነገርበት፣ ሥለ አገር ፍቅር አይሰበክበትም፣ ታሪክ ይንጋደድበታል፣ ጥላቻ ይሰበክበታል፣ ጭንቅላት ይንጋደድበታል፣ አክቲቪስት/አፈ ክፍት/ ፣ ፖለቲከኛ ይፈለፈልበታል።
ሰውና አለሙ እንዲህ ነው፤
ሥንጠቀልለው ችግራችን ራሳችን ነን ራስን ተጠያቂ ማድረግ እንልመድ። የጠፋነው ራስችን ጠማማ፣ ቆልማማ ሆነን ነው ለአጥፊዎቻችን የተመቸነው።
በፍጹም ቀጥ ብለን እስካላደግን ስለመጥፋታችን በሌሎች ላይ ጣታችንን አንቀስር፣ አንድ እንሁን አንለያይ፣ እኔ በሚል ትብታብ አንተብተብ፣ እኛ በሉ፣ ለመወፈር ሌላውን አናቀጭጨው፣ ትልቅ ለመምሰል ሲሉ ሌላውን ማቅለል ማሳነስ የክፉ ሰው ተግባር ነው፤ ዛፎች ይህ የለብንም የሚታይብን ይኸንን በአስቸኳይ እናስወግድ።
እንደምትመለከቷቸው ሰወች ናቸው ትልቅ መስለው ለመታየት ትልቅ ሰው የሚሳደቡት፣ የሚያንቋሽሹት፣ የሚዘረጥጡት፣ ... አንዳንድ ሰወች ከአስተሳሰባቸው ማነስ የተነሳ ብሔርን ሳይቀር፣ ቋንቋን ሳይቀር፣ እምነትን፣ ባሕልን፣ ... ሳይቀር የነርሱ ካልሆነ አሳንሰው ያያሉ። ይህ ትልቅ ስህተት ነው አያኗኑርም ያጋጫል። ግጭቱ እንዲህ በቀላሉ የሚቋጭ እንኳን አይደለም ከትውልድ ወደ ትውልድ ይሸጋገራል።
በዚህ ዘመን ትልቅ ሰው አይከበርም፣
ሐሳብ ያለው አይወደድም፣
ለምን? ብሎ የሚጠይቅ ሰው እርኩስ ነው፣
አድር ባይ ሲሊኩት ሄዶ ሰፈር እንደ ችቦ የሚለኩስ፣ መንገድ እንደ ደጃፍ የሚዘጋ ይፈራል ይከበራል ይሾማል ይሸለማል፣
ችግር የሚባል አይደርስበትም፣
ንጹሕ ሰው ተሳቆ ይኖራል፣
ሽማግሌ የሐይማኖት አባት አይሰማም አይከበርም፣ ሥነ ምግባር፣
ግብረ ገብነት አይነገርም፣
ቀጥ ያለ አይወደድም፣
ወደ ፊት መጓዝ ሳይሆን እንደ ሎጥ ሚስት ወደ ኋላ መመልከት የአገሪቱ/የትውልዱ ማነቆ ነው።
ይቆየን።
ክፍል ስድስትን ያገናኘን።
የዘመንን ወለምታ የትርክትን ስብራት በቀና አስተምህሮ እንጠግናለን።
ይከታተሉን።
ሐሳብ አስተያየትዎን ከመስጠት አይቆጠቡ።
መልካም ቀን ይሁንልዎ።
ደረሰ ረታ
ነሐሴ 13/2012 አ.ም
እንኳን ለደብረ ታቦር (ቡሄ) በአል አደረሳችሁ።

እራስን ተጠያቂ ማድረግ መለማመድ (ክፍል አራት)

 

12/12/12
ጎበዝ መጨረሻችን የመጥረብያ እጀታ አይሁን፣
ቅርንጫፎቻችንን አንመልከት ቅርንጫፎቻችንን ከተመለከትን ብዙ የተራራቅን ይመስለናል፤ ሥሮቻችንን ተመልከቱ እንዲህ አምሮብን ዘመናትን ያስቆጠርነው የሥሮቻችን ተጋምደው መኖር ነው ምሥጢሩ።
እንደ ሰው ልጅ ፍላጎት ቢሆን ገና ድሮ አልቀናል፤
ምድር ተራቁታ ድርቅ ምድረ አዳምን ከምድረ ገጽ ባጠፋ ነበር።
ጨከን ብለን ለራሳችንም ሆነ ለሰው ልጅ ሥንል እንኑር።
እኛኮ ከአንድ ለም አፈር የበላን ከአንድ ምንጭ የጠጣን የአንድ ምድር ውጤቶች ነን። ቅርንጫፎቻችንን አንይ ሥራችን አንድ ነው። ቅርንጫፎቻችንን ላየ በቀላሉ ሊለየን ይችላል ሥራችንን ዘልቆ የተመለከት ማንም አይለየንም።
የሰው ልጅም እንዲህ የሚባላው ቅርንጫፉን እየተመለከተ ነው፣ ቀለሙን ፣ ሐይማኖቱን፣ ጎሳውን፣ ቋንቋውን፣ አከባቢውን፣ ... ነገር ግን የትመጣውን ቢመረምር ከአንድ አፈር ነው። ይህ ጠፍቶት ነው የሚባላው።
እድሜዬ ጠና እንደማለቱ ብዙ የሰው ልጅ ጠባይ አውቃለሁ። መኖር ደጉ ይኸውላችሁ ... ብለው አንገታቸውን አቀረቀሩ በሐሳብ እሩሩሩሩሩቅ ሄዱ፤ ጸጥታው ሰፈነ ... አልተመለሱም።
በምርኩዛቸው ምድርን ቆረቆሩ፣ እንባቸው በአራቱም ማእዘን ወረደ። ጭንቅላታቸውን ነቀነቁ። ይህቺ ምድር ትፍረዳ ብለው አንገታቸውን ቀና አደረጉ።
ይህቺ ምድር እና እኔ ስንቱን አየን ምድር ሥንቱን ደጋግ አባቶች ከጉያዋ ሸሸገች? ጓደኞቼ ለሥንቱ መቀበሪያ ሣጥን ሆኑ?
ሥንት ጀግና ሥንት አገር ወዳድ ሥንት ለሰው ሟች በቀለባት ይህቺ ምድር? ዛሬ አቃፊ ነን ባይ እንጂ እንግዳ እንኳን በቅጡ የሚያስተናግድ የለባትም ምድራችን፣ እሾክና አሜኬላ አበቀለች ምድር፣ ያለ ማዳበሪያ ፍሬ አልሰጥ ካለች ሰነበተች፤
ለምን? ብሎ የሚጠይቅ ትውልድ የለም።
ተገዶ ሳይሆን ወዶ ትውልዱ እንደ እኛ ለሚጨርሱት እጀታ ሆኗል እንደ እኛ።
እጀታ ሆኖ እርስ በርስ ከተጨራረሰ በኋላ ጨረሱን ይላል መለስ ብሎ ... ለምን? እንዴት? አይልም።
ግርርርርር ከማለት ምን ይገኛል?
ያለ ጎረቤት ብቻውን ምን ሊሆን ነው?
ጓዶች ያለ ሰውኮ ይህቺ ምድር ጨው እንደሌለው ወጥ ነው፤ ቀምሼ ባላውቀውም አሉ ታላቁ ዛፍ/ ዋርካው። ዛፎች ፈገግ አሉ በትልቁ ዋርካ አነግስገር።
ተመልከቱ አሉ እጃቸውን ወደ ማዶ እየጠቆሙ ያ የምትመለከቱት ቤት ባለቤት ወላጆቻቸውን ወደ ኋላ ተመልሶ የሚያጠና ቢገኝ የነርሱ ቤተሰብ የኋላ አመሰራረት እና የዛሬ ልጆቻቸው ታሪክ ለየቅል ነው።
ወላጆቻቸው መንገደኛ እንግዳ ተቀባይ፣ የተራበ የሚያበሉ፣ የተጠማ የሚያጠጡ፣ የታረዘ የሚያለብሱ፣ የታመመ የሚጠይቁ፣ ... ነበሩ። የዚህ ቤት ታሪክ "ነበር" ላይ ተገትሮ ቆሟል፤ ቶሎ የሚደርስለት ትውልድ ካልተገኘ አደጋ ላይ ነው።
ዛሬ ቤቱን ብትመለከቱ ብዙ ክፍሎች ተዘገተው ተቀምጠዋል። እንኳን እንግዳ ሊቀበሉ ልጆቻቸው መጻተኛ ሆነው በየአለማቱ ተበትነው እንግዳ ሆነው ይኑራሉ። ይህ ቤተሰብ የሁሉም ቤተሰብ ምሣሌ ነው። የአገር ምሣሌ ነው። ቤትና አገር አንድ ነው ብዙ የሚያመሣሥላቸው ነገር አለ ሁላችንም እንዳየነው ቤት ተሰርቶ ሰው ገብቶ ካልኖረበት ይፈርሳል። አገርም አያድርግባቸውና እንደዛው ነው። ክልሎች ከኛ ሰው ውጭ አይኑርበት ብለው የሚያፈናቅሉት ጥቅማቸውን ነው እየነኩ ያሉት የሰው ልጅን ጥቅም ሥላልተረዱት።
ቢገባቸው ኖሮ እንኳን ሊያሳድዱ፣ ሊያፈናቅሉ፣ ሊገድሉ፣ ሐብትና ንብረታቸውን ሊያወድሙ ይቅርና ሙሉ ወጪያቸውን ችለው ባኖሯቸው ነበር። የሰው ልጅ መኖሩ ዘርፈ ብዙ ጥቅም አለው። ምድር ተራቁታ በረሃነት ባልሰፋ ፣ ምድር ለምነቷን ባላጣች፣ እኛ ተጨፍጭፈን ብቻ ባላለቅን፣ ሰው በተፈናቀለ ቁጥር ቤት ሊሰራ ባልመነጠረን ነበር፤ ወገኖቼ ታሪኩ ብዙ ነው ስንቱ ተዘርዝሮ ያልቃል።
በአጭሩ እንኳን ሰው እና ሰው እኛና ሰው ተለያይተን መኖር አንችልም። ወደ ዋና ጉዳዬ ስመጣ እኛና ሰወች ጠላቶች አይደለንም ተመጋጋቢዎች ነን። አንዳንችን ለአንድኛችን አስፈላጊ ነን። የምንጠፋፋ አይደለንም። እኛ ያለነሱ እነርሱ ያለኛ አንኖርም። እነርሱ ራሳቸው ሰወች እንዳጠኑት በሳይንሳቸው ከነርሱ በሚወጣ የተቃጠለ አየር እኛ ስንኖር እነርሱ ከኛ በሚወጣ አየር ይኖራሉ።
እናንት ወገኖቼ አስቀድማችው እንደ ጠቀሳችሁት ሰወች ጨረሱን፣ ጨፈጨፉን፣ ወዘተ ያላችሁት ትንሽ እውነት አለው። ነገር ግን ትንሽ እውነት ትልቁን እውነት አይበልጠውም። ሂሱን ዋጡት ለመቼ ሊሆናችሁ ነው ዋናው የራሳችን ችግር እራሳችን ዛፎች ነን። ተንጋደን እናድጋለን ለመጥረቢያ እጀታ እንሆናለን የሰው ልጅም በመጥረቢያ እየጠረበ ይማግደናል። መፍትሄው ጨረሱን እያሉ ከማዜም ተንጋዶ አለማደግ ነው።
እድሜ እንዳስተማረኝ የሰው ልጆች ተንጋዶ ማደግ ለእርስ በርስ እልቂት ዋናው መንስኤ ነው። አስተዳደግ ወሳኝ ነው። በተለይ የሰው ልጅ ሲያድግ ዝም ብሎ እንዳገኘ ማደግ የለበትም። አስተዳደጉ መጨረሻውን ይነግረናል። ምን በልቶ አደገ ብቻ ሳይሆን ምን ሰምቶ፣ ምን ተምሮ፣ ምን አይቶ፣ ወዘተ አደገ የሚለው ለሰው ልጅ መሰረታዊ ጥያቄ ነው።
ዛሬ የሰው ልጅ ስለሚለብሰው፣ ስለሚጫማው፣ ስለሚይዘው ሞባይል፣ ስለሚያሽከረክረው መኪና፣ ... እንጂ ስለሌላው አይገደውም።
ሌላው ቢቀር በያዘው ሞባይል ስንት ሸርና ተንኮል እንደሚንሸራሸርበት አይመረምርም። ያገኘውን ሁሉ ያምናል። ተነስ ሲሉት ይነሳል ፣ ተቀመጥ ሲሉት ይቀመጣል፣ መንገድ ዝጋ ሲሉት ይዘጋል፣ አቃጥል፣ አፈናቅል፣ ግደል፣ ስቀል፣ ሲሉት ያሉትን ሁሉ አምኖ ያደርጋል።
ትውልዱ የአክቲቪስቶች፣ የፖለቲከኞች፣ የክፉ ሰወች፣ ... ማስፈጸሚያ እጀታ ሆኗል። አይመረምርም። አይመራመርም።
ይኸን ዝም ብሎ መነዳት፣ አስፈጻሚ፣ ፈጻሚ መሆን እኛ ከሰው ተማርን? ወይንስ ሰው ከኛ ተማረው?
መልስ አልነበራቸውም።
እንዲህ ከተሰባሰብን አይቀር ብዙ የማጫውታችሁ ነገር አለ እንኳን ስለኛ ሰለ ሰውም ጭምር።
ለክፍል አምሥት ይቆየን። የኚህን ታላቅ ዋርካ የታሪክ ምሥክርነት የመፍትሔ አቅጣጫ እንዳስሳለን።
ይከታተሉን።
ሐሳብ አስተያየትዎን ከመስጠት አይቆጠቡ።
መልካም ቀን ይሁንልዎ።
ደረሰ ረታ
ነሐሴ 12/2012 አ.ም.

እራስን ተጠያቂ ማድረግ መለማመድ (ክፍል ሶስት)

 

ነሐሴ 11/2012 አ.ም.
እንደ ሰው ልጅ በምክንያት በሰበብ ጥፋተኝነታችንን ወደሌላ አናሸጋግር ሰወች ለችግራቸው መፍትሔ ያጡት ችግሩ ስለከበደ አይደለም። የችግሩ ባለቤት ራሳቸው ሆነው ሳለ መፍትሔ የሚፈልጉት ከሌላ ጉያ ነው። ራሳቸው ላጠፉት ጥፋት ምክንያት ይደረድራሉ።
ሁላችሁም እንደምታውቁት ሁላችንም የተፈጠርነው ለአዳም ጥቅም ሲባል ነበር ነገር ግን የሰው ልጅ የክፋት ሁሉ ምንጭ የሆኑት አዳምና ሔዋን እርስ በርስ ባለመተማመናቸው እና ሐላፊነትን ባለመውሰዳቸው አትብሉ በተባሉት አንዲት ዛፍ ፍሬ አንዳንዳቸው በአንዳቸው ሲመከኛኙ ከገነት ተባረሩ።
እኛስ ለችግራችን መፍትሔ እንድናገኝ እዚህ ተሰብስበን ከሆን መፍትሄውን ከልባችን ሽተን ከሆነ መፍትሔ ከሌላ ስፍራ ከመፈለጋችን በፊት እስኪ ራሳችንን እንመርምር፣ ራሳችንን እንይ፣ ችግሩ የመነጨው ከውስጥ ነው ከውጭ የሚለውን በጥሞና እንፈትሽ።
የሰው ልጅ በዚህ በ21ኛው ክ/ዘመን እንዲህ የሚባላው፣ የሚተላለቀው የችግሩን ምንጭ ባለማግኘቱ ነው። ችግሩን ከጉያቸው ተሸክመው መፍትሔውን ከአጎራባች አገር፣ ከታናናሽ አገር፣ ከኢኮኖሚው አቻቸው፣ ከፖለቲካ ተፎካካሪዎቻቸው ዘንድ ስለሚፈልጉ ነው፤ ይህ ደግሞ ከሰው ልጅ የምንማረው እነርሱ እንደሚተርቱት " ላም ባልዋለት ኩበት ለቀማ " ይሆንብናል።
ስለሰወች ልጆች በማውራት ጊዜያችንን አናባክን እስኪ ሁላችንም ራሳችንን እንይ ... የጥፋታችን ምንጭ ምንድን ነው? ጠላታችን ማነው? ማነው ያጠቃን ማንስ ነው ያጠፋን? ያልን እንደሆነ ሁላችሁም ከዚህ ቀደም ደጋግሜ እንደጠቀስኩት የሰው ልጅ፣ እንስሳት፣ በሽታ እነዚህ ዋነኛ ተጠቃሽ ነው። ነገር ግን እነዚህ እንደ ዋና ችግር የሚጠቀሱ ሲሆን ዋናው ተዋናይ እኛው ነን።
ጉርምርምታው ጨመረ፣ የነበረው ጸጥታ ደፈረሰ፣ ዋርካው ዛፍ አንገታቸውን ዘንበል አርገው ዝም አሉ። በየ አቅጣጫው ጫጫታው ሰሚ አጣ ሁሉም ተናጋሪ ሆነ፤ አድማጭ ጠፋ ሽማግሌው ዛፍ ንትርኩ ማብቂያ እንደሌለው ሲገነዘቡ ከቦታቸው አረፍ አሉ።
ተንጫጭተው ሲያበቁ ወደ ተናጋሪው ቢመለከቱ የሉም። መናገሩን ትተው ዝም ብለው ቁጭ ብለዋል። ይንጫጫ የነበረው ሁላ ተደናግጦ ዝም አለ።
ሰብሳቢ ተሰብሳቢ ጠፋ ሁሉም መንጋ ሆነ ... መንጋነትን ሰወች ከእንስሳት ተረከቡ ዛሬ ደግሞ እጽዋት ከሰወች ተረከቡት ማለት ነው።
የሰው ልጅ መስማት/ማድመጥ ስለተሳነው ነው ዛሬ እንደ እንስሳ ክብሩን የተነጠቀው እና ማስተዋል የተሳነው። ለዚህ ነው እንደተንቀሳቃሽ ሮቦት በሰው አስተሳሰብ የሚነዳው። ክፉና ደጉን መለየት ያቃተው። ሰው በሰው ላይ በራሱ ወገን ላይ በጠላትነት የተነሳው።
አዛውንቱ ዛፍ ብድግ አሉ፤ ሁሉም አፍሮ አቀረቀረ። ጸሐይ እንደመታው ለጋ ቅርንጫፍ በእፍረት ጠወለጉ። እኚህ ትልቅ ዛፍ አንድ የተጣመመ ዛፍ በእጃቸው ምልክት ሰጥተው ወደርሳቸው እንዲመጣ ጠሩት ... መጣ ... ይታያችኋል? ... እስኪ ለሁሉም እንድትታያቸው ወደ መድረኩ ውጣ ... እስኪ ከዚህ ወንድማችን ከዚህ ዛፍ ምን ተመለከታችሁ? ሁሉም በአንድ ድምጽ ከየአቅጣጫው ጠማማ ነው፣ ጎባጣ ነው፣ ... እያለ በተለያየ ቃላት ዛፉን የሚገልጠውን ነገር ተናገረ።
በሰው ልጆችም መካከልም ስንት ጠማማ፣ ስንት ጎባጣ አስተሳሰብ ሰው ያለ መሰላችሁ?
ከዚህ ዛፍ ምን ተማራችሁ?
ይህ ዛፍ የሰው ልጅ እጅ ሲገባ ምን የሚሆን ይመስላችኋል?
ዝምታ ሰፈን።
አይዟችሁ ድፈሩ ... ዝምታችሁ እውነታውን አይቀይረውም።
አብረን እንደመኖራችን ከሰው የወረስነው ብዙ ጠባይ አለ፤ ሰወችም ልክ እንደ እናንተው ናቸው ጥፋተኝነታቸውን ለመሸሸግ፣ እውነትን ለመሰወር፣ ... ዝም ይላሉ።
እውነት ሩቅ ብትሆንም ተሰውራ አትቀርም ፤ ትገለጣለች። የተገለጠች ቀን አንዳች ከፊቷ የሚቆም የለም። እስከዚያ ግን ትንሹም ትልቁም በጠማማ ልቡ ንጹሑን ያጎድፋል፣ ድሃውን ይበድላል፣ ፍርድ ያጓድላል፣ ያሳድዳል፣ ያፈናቅላል፣ ይገድላል።
እኛንም በዚህ ክፋቱ እኛኑ ተጠቅሞ በዚህ በምትመለከቱት ጠማማ ጫፍ ላይ መጥረቢያ ሰክቶ ይጨፈጭፈናል። ያወድመናል። ወደ እሳትም ይማግደናል። ይኽ ጥፋታችን ተሰውሮብን ወደ ወጥመዱ እንንደረደራለን፣ የክፉ ሰወች መጠቀሚያ እንሆናለን።
ሰውም እንዲህ ነው እርስ በርስ በዘር ፣ በሐይማኖት፣ በቀለም፣ በሰፈር፣ ... እየተከፋፈለ የሚጨራረሰው።
"ችግሩን አግኝተናል" አሉ ሰብሳቢው ዛፍ በተናጋሪው ጣልቃ ገብተው፤ ተናጋሪውን ማቋረጥ ፈልገው አይደለም።በስሜት እንጂ መልሳቸው ልባቸው ስለኮረኮረ እነርሱ ያልተመለከቱትን ስላስገነዘቧቸው ለትልቁ ዋርካ አድናቆታቸውንም ለመግለጥ እንጂ።
ጭብጨባ ከአራቱም ማእዘን አስተጋባ።
ችግኞች ፣መካከለኛ ዛፎች፣ ዋርካዎች እየደጋገሙ አጨበጨቡ።
ዋርካው ዛፍ ወደ መቀመጫቸው አመሩ፤
ይቆየን። ወደ አራተኛ ክፍል ሰላም ያሻግረን።
ይከታተሉን።
ሐሳብ አስተያየትዎን ከመስጠት አይቆጠቡ።
መልካም ቀን ይሁንልዎ።
ደረሰ ረታ
ነሐሴ 11/2012 አ.ም.

ጦማሩን ስለጎበኙ አመሰግናለሁ!

መልካም ነገርን ለሌሎች ማጋራት ባህላችን እናድርግ፤ ላልደረሰዉ በማጋራት ድርሻችንን እንወጣ፡፡

ትቶ እና ችሎ

  ትቶ እና ችሎ ብጹእ ወቅዱስ አቡነ መርቆርዮስ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ በደረሰ ረታ ብጹዕነታቸው ለሶስት አሥርት አመታት እኛ በማናውቀው እግዚአብሔር በሚያውቀው በብዙ መከራ በብዙ ፈተና ውስጥ ነው ያሳለፉት። ...