ማክሰኞ 22 ዲሴምበር 2020

የዳሰሱትም ሁሉ ዳኑ

 "የልብሱንም ጫፍ ብቻ ሊዳስሱ ይለምኑት ነበር፤ የዳሰሱትም ሁሉ ዳኑ።" 

/ማቴ 14፣36/
ደረሰ ረታ
13/04/2013ዓ.ም
$$$$$$$$$=====
በዓለም ላይ ብዙ ሐኪሞችና ብዙ ባለ መድኃኒቶች አሉ፡፡ ሐኪሞቹ መድኃኒት ያዝዛሉ እንጂ ራሳቸው መድኃኒት አይሆኑም፡፡

ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ሐኪምም መድኃኒትም ነው፡፡
እሱ የሥጋና የነፍስ መድኃኒት ነው፡፡ ሥጋ በቊስል፣ ነፍስ በኃጢአት ሲታመሙ ገዳዩን ገድሎ የሚያድነው መድኃኒት ኢየሱስ ክርስቶስ የድንግል ማርያም ልጅ ብቻ ነው፡!!

ሕክምናው ሲያድን ሲፈውስ ጠባሳ አያስቀርም።
ሲያድን ቀስ ብለህ አይደለም የምታገግመው አልጋህን ተሸክመህ ነው የምትሄደው። አስታማሚዎችህ ለርሱ ሲነግሩት ነው አንተ እቤት ሆነህ ከበሽታህ የምትገላገለው። እመን እንጂ ሲምርህ የጠሉህ ሁሉ ናቸው ጠብ እርግፍ የሚሉልህ፣ የገፉህ ያገለሉህ ሁሉ መንገድ ይመሩሃል፣ መንገድ ይለቁልሃል፣ በወንበራቸው ያስቀምጡሃል። ጠረንህን አጥፍቶ የማይታመን መአዛ ያውድሃል።

በእጁ መዳን ከእርሱ ወዲያ አዳኝ ከእርሱ መድኃኒት እንደሌለ ካመንክ እንኳንስ ዳሰኸው ጨርቁን ነክተህ ጥላው ሲያርፍብህ ስሙን ስተጠራ ትድናለህ።

ድንቅ አይበልህ እንኳን እርሱ በእርሱ የሚያምኑ ለሥሙ የሚገዙ እርሱ የሚያደርገውን ከርሱም በላይ ያደርጉ ዘንድ ስልጣን ተሰጥቷቸዋልና። ቅዱሳኑም ያድናሉ በጨርቃቸው እራፊ/ቁራጭ እና በጥላቸው ሳይቀር።

እነርሱ ስሙን ጠርተው ''በኢየሱስ ስም'' ሲፈውሱ አጋንንትን ሲያሳድዱ እርሱ ግን በሃይሉ እና በስልጣኑ በእርሱ ፈቃድ በአባቱ በአብ ፈቃድ በመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ ይህን ያደርጋል።

በዚህ የመጽሐፍ ክፍል ጌታችን መደኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብዙዎችን እያዘነላቸው አድኗቸዋል። አንደኛው ከደቀመዛሙርቱ አንዱ የሆነውን ቅዱስ ጴጥሮስን ሲሆን ሌላኛዎቹ የጌንሴሬጥ ሰዎችን ነበረ። የመጀመሪያ ሰው ቅዱስ ጴጥሮስ የእጁን ተአምራት የቃሉ ትምህርት የተከታተለ ብዙ ልምድ የነበረው ሲሆን የጌንሴሬጥ ሰዎች ይህ እድል ከዚህ ቀደም አልነበራቸውም። ይህንንም እድል ያገኙት ከታንኳ ወርዶ ወደ መንደራቸው ገብቶ ባገኙት ጊዜ ነበረ።

እነዚህንም ከመፈወሱ አስቀድሞ ከቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ቀብር መልስ ብዙዎችን እንደፈወሰ መጽሐፍ ይናገራል።በዚሁ ምእራፍ ቁጥር 14 ላይ ''ወጥቶም ብዙ ሕዝብ አየና አዘነላቸው ድውዮቻቸውንም ፈወሰ።'' ይለናል።

እነዚህ የጌንሴሬጥ ሰወች ማን እንደሆነ ባወቁ ጊዜ በአከባቢው ባሉ በሽተኞች ዘንድ ሁሉ ሰው ላኩ የታመሙትንም ሁሉ በአንድ ሰበሰቧቸው።

ከባንኮክ፣ ከአውሮፓ፣ ከአሜሪካ፣ ከኤሸያ እውቅ የጤና ባለሙያዎች ቡድን ስለመጣ፤ አልያም የኩላሊት፣ የልብ፣ የዲስክ መንሸራተት፣ የውስጥ ደዌ እስፔሻሊስት ቡድን ስለመጣ ብለው አልነበረም የሰበሰቧቸው በደዌ ዳኛ በአልጋ ቁራኛ የተያዙትን ሁሉ እንጂ።ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በበሽታ ላይ ሳይሆን በመፈወስ ላይ ስፔሻላይዝ ያደረገ ነውና።

የተሰበሰቡት ሁሉ፦''የልብሱንም ጫፍ ብቻ ሊዳስሱ ይለምኑት ነበር፤ '' በእርሱ ዘንድ የካርድ የከፈለ የመድኃኒት መግዣ ያለው ጥሩ ዘመድ ያለው ሳይሆን የሚድነው ሁሉም ነው። ለዚህም ነው ማቴዎስ ''የዳሰሱትም ሁሉ ዳኑ'' ያለን።

በዓለማችን፣ በአህጉራችን፣ በአገራችን፣ በከተማችን፣ በመንደራችን፣ በቤታችን ሥንት ሰው አለ በደዌ የተያዘ? ሥንት ሰው አለ መዳን የሚገባው? የጌታን መምጣት ወደ እኛ መቅረብ ሰምቶ ወጥቶ አይቶ ማንነቱን ተረድቶ መፈወሰ፣ መዳን ያለበት፤ ጌታ በደጅ ቆሟል ሁላችንም ከማዳኑ እንሳተፍ።

ጥቂት የማይባሉ አዳኙን አምላክ (ሎቱ ስብሐት) ለስም አጠራሩ ክብር ይግባውና እንደ ፍጡር እያዩት አማላጅ ይሉታል።እንደ ጌንሴሬጥ መንደር ሰዎች ማንነቱን የምንለይበትን አእምሮውን ለብዎውን ፈጣሪ ያድለን።

ወደ ጌንሴሬጥ ከመግባቱ አስቀድሞ ቅዱስ ጴጥሮስንና የተቀሩትን ደቀመዛሙርት አግኝቷቸው ነበረ።

"ሕዝቡንም አሰናብቶ ይጸልይ ዘንድ ብቻውን ወደ ተራራ ወጣ። በመሸም ጊዜ ብቻውን በዚያ ነበረ።
ታንኳይቱም አሁን በባሕር መካከል ሳለች፥ ነፋስ ከወደ ፊት ነበርና በማዕበል ትጨነቅ ነበር።ከሌሊቱም በአራተኛው ክፍል ኢየሱስ በባሕር ላይ እየሄደ ወደ እነርሱ መጣ።ደቀ መዛሙርቱም በባሕር ላይ ሲሄድ ባዩት ጊዜ፡— ምትሐት ነው፡ ብለው ታወኩ፥ በፍርሃትም ጮኹ።ወዲያውም ኢየሱስ ተናገራቸውና፡አይዞአችሁ፥ እኔ ነኝ፤ አትፍሩ፡ አላቸው። ጴጥሮስም መልሶ፡— ጌታ ሆይ፥ አንተስ ከሆንህ በውኃው ላይ ወደ አንተ እንድመጣ እዘዘኝ፡ አለው። እርሱም፡— ና፡ አለው። ጴጥሮስም ከታንኳይቱ ወርዶ ወደ ኢየሱስ ሊደርስ በውኃው ላይ ሄደ።ነገር ግን የነፋሱን ኃይል አይቶ ፈራ፥ ሊሰጥምም በጀመረ ጊዜ፡— ጌታ ሆይ፥ አድነኝ፡ ብሎ ጮኸ። ወዲያውም ኢየሱስ እጁን ዘርግቶ ያዘውና፡— አንተ እምነት የጎደለህ፥ ስለምን ተጠራጠርህ? አለው።
ወደ ታንኳይቱም በወጡ ጊዜ ነፋሱ ተወ። በታንኳይቱም የነበሩት፡— በእውነት የእግዚአብሔር ልጅ ነህ፡ ብለው ሰገዱለት።ተሻግረውም ወደ ጌንሴሬጥ ምድር መጡ።"

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የለመኑት ፈቃዳቸውን እንደፈጸመላቸው ቅዱስ ጴጥሮስ ማሳያ ነው በባህሩ ላይ እንዲራመድ ፈቅዶለታልና፤ ለተራቡት በልተው ጠግበው እስኪተርፋቸው መግቧቸዋል። ማእበሉን ጸጥ አድርጓል። ከዚህ በኃላ ነው የእግዚአብሔር ልጅነቱን ሲያምኑ ማዳኑን ያሳያቸው፤ የዳሰሱትም ሁሉ የዳኑት።

እኛ የአዲስ ኪዳን ትውልድ ሁላችን በአባቶቻችን በኩል ኢየሱስ ክርስቶስን አይተነዋል፣ ዳሰነዋል፣ አብረን በልተን ጠጥተናል፣ ስንቶቻችን መዳን ተደሮጎልናል?

የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ እንዳወቁ የልብሱን ጫፍ ብቻ ሊዳስሱ ይለምኑት ነበረ፤ እግዚአብሔር ዛሬ በአካለ ሥጋ በመካከላችን ቢመላለስ/ ለጸሎት በፊቱ ስንቆም የምንለምነው ምን ይሆን?

መዳን?

ብርና ወርቅ?

ቤትና መኪና?

ስልጣን?

ረጅም እድሜ?

ወይስ ... ምን ይሆን ልንለምነው የምንከጅለው?

ጌታን የአምስት ገበያ ያህል ሰው ይከተለው ነበረ ይላል ቅዱስ መጽሐፍ ነገር ግን ከ120 ቤተሰብ ውጭ ያለው አብዛኛው ገሚሱ ውብ ነበረና ደም ግባቱን ለማየት፣ ገሚሱ ደግሞ የእጁን በረከት እና ተአምራት ለመካፈል እና ለማድነቅ፣ የተቀሩትም ከቃሉ ትምህርት ስህተት ለመቃረም ነበረ።

እኛስ፥
• ክርስቲያን የመሆናችን ዋናው ዓላማ ምንድነው ?
• ለምንድንነው የምንከተለው?
• ግባችን ምንድነው ?
• አሁን የት ነው ያለነው?
• ከክርስትና ዓላማችን አንጻር አካሄዳችን እንዴት ነው?
• እያንዳንዳችን አሁን በዚህ ሰአት በፊቱ ለፍርድ ብንጠራ ምን ይለን ይሆን? ኑ እናንት የአባቴ ብሩካን የምንባል ነን? ወይስ,... ካልሆነ እስክንጠራ ምን እያደረግን ነው? (የንስሐ ፍሬ እናፍራ)
የእግዚአብሔር ልጅ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ (እግዚአብሔር ወልድ) ማዕበሉን ጸጥ ያድርግልን፤ ከውስጥ ከውጭ የሚንጠንን የፍርሃት ማዕበል ቀጥ ያድርግልን። በደዌ ዳኛ በአልጋ ቁራኝነት የተያዙትን ይፈውስልን፤ በዘረኝነት ደዌ በጽንፈኝነት ደዌ ከመመታት እግዚአብሔር ይጠብቀን። በክርስትና ሕይወታችን መጡ ሄዱ፣ ነበሩ የሉም፣ አመኑ ካዱ ከመባል ይሰውረን። ማመናችን፣ እርሱን መከተላችን ቸርነቱ ተጨምሮበት ጽድቅ ሆኖ ይቆጠርልን። እረኛው እንደተመታበት መንጋ ከመሆን ይጠብቀን።

በእዝነ ልቡናችን አይተነዋል፣ ሰምተነዋል፣ ዳሰነዋልና መዳን ይሁንልን።
በቀረው ዘመናችን ንሰሐ ገብተን ለዘለዓለም የማያስጠማውንና የማያስርበውን ሥጋውና ደሙን ተመግበን ለርስቱ ወራሾች ለመሆን ያብቃን።
ይቆየን።
@ deressereta


እሑድ 29 ኖቬምበር 2020

ቢቻላችሁ ከሰው ሁሉ ጋር በሠላም ኑሩ

 ቢቻላችሁ ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ

#######################

ደረሰ ረታ

ክፍል አንድ


የሰው ልጅ በምድራዊ አኗኗሩ ከሰው ጋር ሲኖር አኗኗሩን የሚለካበት ሶስት ዋና ዋና ሥፍራዎች አሉት።

1. በመኖሪያ ቤት እና አካባቢው

2. በመሥሪያ ቤት

3. በቤተክርስቲያን

ከነዚህ የአኗኗር ዘይቤ የወጣ ማንነት የለንም። ምናልባት እውነተኛዎች በረኸኛ መናኒ ባህታውያን ካልሆኑ በቀር፤ የከተማ ባሕታውያንን ሳይጨምር።


ከላይ ለተጠቀሱት እንደ ሰው የምንኖርባቸው ሥፍራዎች ዋና መሰረቱ መቻቻልና መከባበር ናቸው ከዚህ የወጣ አላማ የለውም።


በጥቂቱ ለመዳሰስ ከመጽሐፍ ቅዱስ ባሻገር ሁለት መጻሕፍትን ዋቢ አድርገን ዳሰሳችንን እንቀጥላለን። "ክርስትና በማኀበራዊ ኑሮ" ኅሩይ ስሜ እና ዳዊት ደስታ ያዙጋጇቸው እንዲሁም "በኢትዮጵያ የሃይማኖት መቻቻል አለን?" በብጹዕ አባኑ ሳሙኤል የተዘጋጁ።


መልካም አኗኗር ለመልካም አስተዳደር ትልቅ ሚና ስለሚጫወት አሰናስለን እንመለከታለን።


የሰው ልጅ ከ22ቱ ሥነ ፍጥረት የሚለይበት አንዱና ዋነኛው ነገር በሕግ እና በሥርአት መኖሩ እና አንዱ የሌላኛውን መብት እና ነጻነት አክብሮ መኖሩ ነው።


ከሌላው ዓለም ኢትዮጵያውያንን ለየት የሚያደርገን ባህሪይ እና ባህል አለን። ባህላችን እንግዳ ተቀባይ ሕጋችን ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ ሰውን አክባሪ መሆናችን ነው።


ለነዚህም ተግባራችን እንደ ምሳሌ በቀዳሚነት የምንመለከተው "ኢትዮጵያውያን የሰውን ሰብአዊ መብት በመጠበቅ አንፃር በመልካም አስተዳደር ሂደት በ70 ዓ.ም በጥጦስ አማካኝነት የኢየሩሳሌም ቤተ መቅደስ ሲፈርስና ኢየሩሳሌም ስትወረር በርካታ አይሁዳውያን ፈላሻዎች ኢትዮጵያ ውስጥ መጥተው ኖረው ምንም እንኳን ኢትዮጵያ የክርስትናን ሃይማኖት ገና በ34 ዓ.ም በኢትዮጵያዊው ጃንደረባ አማካኝነት ብትቀበልም (የሐዋርያት ሥራ 8:29) አይሁድ ክርስቶስን የሰቀሉ ናቸው በማለት ማረፊያ አልተከለከሉም።" 


የሰው ልጅን አክባሪነቱ ከመጽሐፍ ቅዱስ አስተምሮ የመነጨ ነው፦ የራሱን ፈቃድ ሲፈጽም የሌላውን ወገኑንም ሆነ ባለጋራውን (ጠላቱን) ጨምሮ ህሊና ጠብቆ የሚኖር ነው። 1ኛ ቆሮንቶስ 8:11 " ሰዎች በአንተ ላይ ሊያደርጉብህ የማትፈልገውን ነገር እንዲሁ በባልንጀራህ ላይ አትፈጽም ሰዎች ሊያደርጉላችሁ የምትሹትን በሙሉ እናንተም እንዲሁ አድርጉላቸው" በሚል መርህ የሚመራ ነው።


ከሕግም አንጻር የእያንዳንዱን ግለሰብ ተፈጥሯዊ እና መሠረታዊ የሆኑትን መብቶች ያከብራል። ለማስከበርም ይጥራል። እነዚህም፦

1. ፖለቲካዊ ነጻነት

2. ማህበራዊ ነጻነት

3. ኢኮኖሚያዊ ነጻነት ናቸው።

ከሕግ አግባብ እነዚህን ሶስት ነጻነቶች በጠንካራ መሠረት ላይ ከታነጹ ሕዝብም አገርም አትናወጽምና።


ለክርስቲያኖች ቅድስት ቤተክርስቲያን ከልደተ ክርስቶስ አስቀድሞ ከሙሴ ሕግ ጀምሮ እስከ አዲስ ኪዳን ሕግ ድረስ ትምህርቷ ፍቅር፣ ሠላም፣አንድነት፣እኩልነት ነው። "ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ" በሚል አስተምሮ ታንጻለች።


ከዚህ በመነሳት የሌሎች አገራት ዜጎችና መሪዎች እምነት ተከታዮች ሳይቀር ይሰደዱባታል፤ ይጠለሉባታልም። የእስልምና እምነት ተከታይ ወገኖቻችን፣ የፖለቲካ መሪው ኒንሰን ማንዴላ፣ ማህተመ ጋንዲ፣ የተለያዩ አገራት ስደተኞች ማሳያዎች ናቸው። በግንባራችን እንጂ በጀርባችን ጥይት አይመታንም ያሉ ጀግኖች አባቶቻችን ይህችን ድንቅ አገር እስከ ሙሉ ክብሯ አስረክበውናል። እኛስ?


ዛሬ ከላይ የጠቅስናቸው ተግባራትና መገለጫችን እየቀጨጩ ይገኛሉ። እኛ ዘመን ጋር ሲደርሱ ለምን ይህ ሆነ?


ዘመኑን ካየን የዘመነ፣ የሰለጠነ፣ በእውቀት የመጠቅንበት፣ በሳይንስና ቴክኖሎጂ የታገዝንበት ሲሆን ደካሞች ነን።


• ከባቢያዊ ግጭቶች በርክተዋል

• ሽብራዊ አመጽ በተለያዩ ሥፍራ ይቀሰቀሳል

• የጦር መሣሪያ ዝውውር በርክቷል

• ዓለም አቀፍ ይዘት ያላቸው በሽታዎች/ወረርሽኞች ተበራክተዋል።

ነገር ግን ይህንን ማስቀረት አልቻልንም። ለምን?


ዲሞክራሲ የብዙሃን የበላይነት የሚረጋገጥበት የአናሳዎች መብቶች የሚከበርበት ሥርዓት ሲሆን ሥልጣንን መሰረት በማድረግ አናሳዎች የበላይነት እየወሰዱ የሚገኙበት ሁኔታ ላይ እንገኛለን። በፖለቲካ ሴራ የብሔር ግጭት፣ የሃይማኖት ግጭት፣ እየተከሰተ ይገኛል። ሲፈተሽ ችግሩ የመልካም የማኀበራዊ ኑሮ አኗኗር ችግር/ውስንነት እንደሆነ ይታመናል። ይህም ተጽዕኖ በመልካም አስተዳደር እጦት ላይ ጠባሳውን ያሳርፋል ብሎም የፍርድ መጓደልን የድሃ መበደልን ያስከትላል። ይህ ሆኖ ሲገኝ እንኳን የዲሞክራሲን መኖር ማረጋገጥ ይቅርና ወጥቶ መግባት በስጋት ይሆናል። እኩልነት ቀርቶ የጥቂቶች የበላይነት ይሰፍናል። የብሔረሰብ እኩልነት፣ የእምነት ተቋማት እኩልነት፣ የባህል እኩልነት፣ የፖለቲካ እኩልነት፣ ኢኮኖሚያዊ እኩልነት፣ ማህበራዊ እኩልነት፣ የአስተዳደር እኩልነት አይኖርም። ልማትና ሠላም አይኖርም።


ስለዚህ ቅድስት ቤተክርስቲያን እና ምእመናን በአንድነት በሃይማኖታዊ እና በማሕበራዊ ተግባራት በብቃት ልትወጣ ይገባታል። ከፖለቲካ አስተዳደር ውጭ የሆነ የራሷ አስተዳደር ሊኖራት ይገባል። ይህ ሊሆን የሚችለው ደግሞ፦

• ራሷ በክርስቶስ ሠላም ውስጥ መኖርዋን ስታረጋግጥ

• መልካም አስተዳደር በውስጧ ሲጎለብት

• የውስጥ ችግሮችዋን በራሷ መፍታት ስትችል፣መከባበር፣ መደማመጥ ሲኖር፣

• ቤተክርስቲያኒቱ ያለባትን ኃላፊነት በግልጽ በማጤን በውስጧ ተሰግስገው ሰማያዊ ሳይሆን ምድራዊ ዓላማ ይዘው የሚጓዙትን ጠርጎ ሲያስወጣ 

• ቤተክርስቲያንን የመጠበቅ ግዴታ የምእመኑም በመሆኑ በክርስትና እምነት አስተምሮ የታነጸ ሲሆንና ተሳትፎአቸውን ይበልጥ በማጎልበት የአሠራር ግልጽነትን በማስፈን ወዘተ ብቻ የሚሆን ነው።

ቤተክርስቲያን ችግሮቿን በራሷ አቅም መፍታት ስትችል መልካም አስተዳደር ይሰፍናል፤ መንፈሳዊነት ይጸናል።


"የእግዚአብሔር ጸጋ እንደ ተሰጠኝ መጠን እንደ ብልሃተኛ የአናጺ አለቃ መሠረትን መሠረትሁ፥ ሌላውም በላዩ ያንጻል። እያንዳንዱ ግን በእርሱ ላይ እንዴት እንዲያንጽ ይጠንቀቅ።" 1ኛ ቆሮንቶስ 3:10


እኛም እንደ ምእመን እንዴት በጥንቃቄ መኖር እንዳለብን እንመለከታለን።

ክፍል ሁለት ይቀጥላል


@deressereta


እኔን ለማግኘት ጽሁፎቼን ለመከታተል ከዚህ በታች የተጠቀሱት ሁሉ ወደ'ኔ ይመሩዎታል።


My Facebook page link (በፌስቡክ ገጽ እንገናኝ)


https://www.facebook.com/deresse2020/


Main facebook account (ዋናው የፌስ ቡክ ገጼ ይቀላቀሉት)


https://www.facebook.com/DeresseReta


Follow me through telegeram (በቴሌግራም ሊከታተሉኝ ከፈቀዱ) ሁሉም ምልከታዬን የማጋራባቸው ማህበራዊ ድረ ገጾች ናቸው።

ሰኞ 23 ኖቬምበር 2020

በአባቴ ቤት እንጀራ የሚተርፋቸው አገልጋዮች ስንት ናቸው?

 በአባቴ ቤት እንጀራ የሚተርፋቸው አገልጋዮች ስንት ናቸው?

ሉቃስ 15: 17

ጌታችን መድኋኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ምድር በተመላለሰበት በዘመነ ሥጋዌው ለሶስት ዓመት ከሶስት ወር አስተምሯል።

እርሱም በሚያስተምርበት ወቅት የአምስት ገበያ ያሕል ሕዝብ ይከተለው ነበር ብሎ መጽሐፍ ይነግረናል።

ከነዚህ የቃሉን ትምህርት ከሚማሩት ከእጁ በረከት ከሚሳተፉት መካከል ገሚሱ ሃጥያተኞች ስለነበሩ ሊከሱት ይከተሉት በነበሩት መካከል ተቀባይነትን አላገኘም ፤ እጅግም አስነቀፈው። እንዴት ሃጢያተኞችን ሰብስቦ ያስተምራል ብለው አሙት። ወንጀሉት።

ክብር ይግባውና ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የነርሱን ትችት ወደ ጎን በመተው ይልቅስ መድሃኒት የሚያስፈልገው ለጤነኞች ሳይሆን ለበሽተኞች እንደሆነ በመንገር ከክፋታቸው ይመለሱ ዘንድ አስተማራቸው። እኔ ሐጥአንን ልጠራ መጣሁ እንጂ ጻድቃንን ልጠራ አልመጣሁም እንዲል ከሃጢያተኞች ጋር ዋለ። እነርሱም አጉረመረሙ። በማጉረምረማቸው ምክንያት ሶስት ምክንያታዊ የሆነ ትምህርት በምሳሌ አስተማረ።

፩ኛ. አንድ ሰው መቶ በጎች ነበሩት ቀኑን ሙሉ በለመለመ መስክ እያሰማራ ከምንጭ ውሃ እያጠጣ ዋለ ሲመሽም ወደ በረታቸው ያጉራቸው ዘንድ ወደ ቤቱ ተመለሰ። ከመሸ ከደከመውም በኋላ አንደኛው በግ እንደጠፋበትም ተረዳ ዘጠና ዘጠኙን በበረት ቆልፎባቸው በጨለማ አንዱን በግ ፍለጋ ወጣ። ያንን በግ እሲኪያገኝ ድረስ በከባድ ድካም ውስጥ ሆኖ ፈለገው። አገኘውም። እጅግም ደስ አለው። ጎረቤቶቹንም ጠርቶ አንዱ በጌ ጠፍቶ ነበር ተገኝቷል ከኔ ጋርም ደስ ይበላችሁ አላቸው።

፪ኛ. አንዲት ሴት አሥር ሳንቲሞች (ድሪም) ነበሯት ከአሥሩ ሳንቲሞች አንዱ ጠፋባት መብራት አብርታ ፈለገችው፣ የቤቱንም ቆሻሻ ጠርጋ ወደ አንድ ጥግ ሰበሰበች ፈለገችው አገኘችውም እርሷም እንደ ባለ በጉ ጎረቤቶቿን ጠርታ አንድ ድሪም ጠፍቶብኝ ነበር አገኘሁት ከኔ ጋር ደስ ይበላችሁ አለቻቸው።

፫ኛ. አንድ ባለጸጋ ሰው ሁለት ወንድ ልጆች ነበሩት ይህ ሰው የሃብቱ ወራሾች እነዚህ ልጆች ብቻ ነበሩ፤ ይሁን እንጂ ሐብት የሚወረሰው አባትየው ሲሞት ነው። ትንሹ ልጅ ከአባቱ የሚደርሰውን ሐብት ንብረት ተመኘ አባቱንም ቢያይ ቢያይ አይሞትም እጅግም ቸኮለ። ስለዚህ ወደ አባቱ በመሄድ የሚደርሰውን አንድ ሶስተኛውን ይሰጠው ዘንድ ጠየቀ አባቱም ኩፍሎ ሰጠው። ሐብቱንም ይዞ ወደ አንድ እሩቅ አገር ሄደ። በልቶ ጠጥቶበት ከጋለሞታዎችም ጋር አባክኖት በአጭር ጊዜ ጨረሰው።

ገንዘቡ ሲያልቅ ጓደኞቹም ከአጠገቡ አንድ በአንድ እየሸሹት ብቻውን ቀረ። ሀብቱም አልቆ ባዶ እጁን ቀረ፣ ተራበ፣ ተጠማ፤ መጠለያም አጣ። ወቅቱም በአገሩ ድርቅ ተከስቶ ነበርና ረሐብ ሆነ። ያስጠጋው ዘንድ ወደ አንድ ሰው ዘንድ ሄደ። እርሱም አስጠጋው ሰውየው ላስጠጋበት ዋጋ ይሆነው ዘንድ አሳማዎቹን እንዲጠብቅለት አደረገው።

አሳማ እጅግ አስጠሊታ ከመሆኑ የተነሳ እስራኤላውያን አሳማ መጠበቅ አይወዱም። የነካው ይረክሳል፣ ሥጋውንም አይበሉትም። ይህ የባለጸጋ ሰው ወጣት ልጅ ውሎና አዳሩ እጅግ በሚገማ የአሳማ በረት ውስጥ ሆነ። ወቅቱ ድርቅ እና ረሐብ የነበረበት ወቅት ስለሆነ እጅግ ከመራቡ የተነሳ አሳማው ከሚበላው ይመገብ ዘንድ ይመኝ ነበር።
ርሐብና እና ጽም እጅግ ጸናበት። ችግርም ጸናበት።
በስተ መጨረሻ ወደ ልቡም ተመለሰ። እንዲህም አለ፦ በአባቴ ቤት እንጀራ የሚተርፋቸው አገልጋዮች ስንት ናቸው? ተነስቼ ወደ አባቴ ቤት እሄዳለሁ አባቴ ሆይ የሚገባኝን ሁሉ ወስጄ ሄጃለሁ ከእንግዲህ ልጅህ ልባል አይገባኝም ከአገልጋዮችህ እንደ አንዱ አድርገኝ እለዋለሁ። ብሎ ወደ አባቱ ዘንድ ሄደ። አባቱም በርቀት ተመለከተው እጅግም አዘነለት ወደ እርሱም ሮጦ አቀፈና ሳመው።
ልጁም አባቴ ሆይ ልጅህ ልባል አይገባኝም አለው።
አባትም ከሁሉ የሚበልጠውን ልብስ አምጡና አልብሱት፣ ለእግሩ ጫማ ስጡት፣ የሰባውን ፊሪዳ አምጡና እረዱለት እንብላ እንጠጣ ደስም ይበለን። ልጄ ሙቶ ነበር ሕያው ሆኗል፣ ጠፍቶ ነበር ተገኝቷል፤ አለ።
እቤት የነበረው፣ ከአባቱ ሐብት ንብረት ያልተካፈለው ትልቅ ልጅ እርሻ ዉሎ ወደ ቤት ሲመጣ ከቤታቸው ቅጽር ድምጽ ሰማ፣ ያልተለመደ ድምጽ ነው የዘፈን ድምጽ፣ የደስታ ድምጽ የምስራች የያዘ ድምጽ፣ እኛ ቤት ምን ተፈጠረ? ምንስ ክስተት ተከሰት? እኔ ከቤት ከወጣሁ እኔ የማላውቀው ነገር ምንስ ተፈጠረ ብሎ ጠየቀ፤ ከጎረቤትም ልጅ መጣና ወንድምህ ነው አለው።

ወንድሜ ምን ሆነ?
ወንድሜስ ከዚህ የት አለ? ብሎ ጠየቀ።

የጠፋው ወንድምህ ተገኝቷል፤ አባትህም ተደስቷል። ለወንድምህ መምጣት በቤታችሁ ትልቅ ደስታ ሆኗል። አባትህም ትልቁን ፊሪዳ ለወንድምህ አርዶለታል። አዲስ ልብስም አልብሶታል። ለጣቱም ቀለበት አጥልቆለታል ብሎ ወሬውን አደረሰው።

ወንድሙም እጅግ አዘነ፣ እኔ በዚህ ቤት ስኖር ሥጥር ሥግር አንዳች ቀን ትልቅ እና የሰባ ፊሪዳ አይደለም ግለግል እንኳን ታርዶልኝ አያውቅም፣ አዲስ ልብስ እና የጣት ቀለበት አልተገዛልኝም። ሐብት ንብረቱን ተካፍሎ ቤቱን ጥሎ የሄደን ልጅ ተመልሶ መቀበሉ ስለምን ነው በማለት አኮረፈ ወደ ቤትም አልገባም አለ።

አባቱም ስለ ትልቁ ልጅ ተጨነቀ ሊያግባባውም ሞከረ። ስለ ጠፋው ልጁ/ወንድሙ መገኘት ሊነግረው ሞከረ።

ትልቅ ልጅ፦ ልጅህ ሲመጣ የሰባውን ፍሪዳ አረድክለት፣ ለጣቱም ቀለበት አጠለክለት፣ አዲስ ልብስም እንዳለበስከው ሰማሁ ... እኔ እስከ ዛሬ እንደ ባሪያ ሳገለግልህ ነበር አንድም ቀን ለእኔ እና ጓደኞቼ አንዲት ጠቦት አላደረክም ገንዘቡን ከጋለሞታዎች ጋር ሲበትን ለኖረው ልጅህ እንዴት እንደዚህ ታደርግ ዘንድ ልብህ ፈቀደ አለው።

አባትም ልጄ አንተ እስከ ዛሬ ከኔ ጋር ነበርክ የእኔ የሆነው ሁሉ ያንተ ነበር፤ ነገር ግን ይህ ወንድምህ ( ትልቅ ልጅ ወንድሙን ስለ ተናደደበት አባቱን ልጅ አለው አባት ግን ወንድም በማለት አስታወሰው) ሞቶ ነበር ሕያው ስለሆነ ጠፍቶ ነበር ስለተገኘ ደስ ሊለን ሐሴትም ልናደርግ ይገባል አለው።

ከላይ በተጠቀሱት ምሳሌዎች የጠፉ ሶስት ነገሮችን ተመልክተናል።
1. በመጀመሪያ በግ ጠፋ
2. በመቀጠል ድሪም (ሳንቲም) ጠፋ
3. በስተ መጨረሻ ሰው ነው የጠፋው
እግዚአብሔር በሉቃስ ወንጌል ምእራፍ 15 በመጽሐፍ ቅዱስ የሚገኙትን ሁሉን ጠቅልሎ ሊይዝ በሚችል መልኩ ያስተማረበት የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ነው። እዚህ የተጠቀሱት ምሳሌዎች ሳይቀር በጣም ወርቃማ ምሳሌዎች ናቸው።

ይህ የትምህርት ክፍል ከመደነቁ ባሻገር በሕይወታችን ውስጥ የሚያሳየን ትልቅ ምሥጢር አለ። ይኸውም አንድ ክርስቲያን ከቤተክርስቲያን እንዴት አድርጎ እንደሚጠፋ፣ ሕይወቱ እንዴት እንደሚቅበዘበዝ፣ እግዚአብሔር እንዴት እንደሚፈልገን፣ እንዴትስ ወደ እግዚአብሔር ቤት እንደምንመለስ ቁልጭ አድርጎ ያሳየናል። (ጽሑፉ ረዘመ እኔ ረጅም ጽሑም አልወድም የምትል ከሆነ ከዚህ ምሥጢር አትሳተፍም)

በምሳሌው በመጀመሪያ የጠፋው እንስሳ ነው፣ በመቀጠል የጠፋው እቃ ሲሆን በመጨረሻም የጠፋው ሰው ነው።

• ሰወች ስንጠፋ ሰው ሆኖ የማይበድል እንጨት ሆኖ የማይጨስ የለም እያልን እንጠፋለን።
• አንዳንዴ ከሰውነት ክብር ዝቅ ብለን የእንስሳ ተግባር ስንከውን እንገኛለን። (አውሬያዊ ጭካኔ ይታይብናል።)
• አንዳንዴ ከእንስሳት ዝቅ ብለን እቃ የምንሆንበት አጋጣሚ አለ። እንስሳት በዘር አይጣሉም እኛ ግን ከነርሱ አንሰን በዘር እንጣላለን። አንበሳ ምን ቢከፋ ምን ቢርበው አንበሳን አይበላም እኛ ግን እርስ በርስ እንበላላለን። የማንጠቅም ርካሽ የምንሆንበት ጊዜ አለ።
እግዚአብሔር በነዚህ ምሳሌ እንደምንመለከተው ሊያስተምረን የፈለገው እንደ እንስሳም ብትጠፉ እፈልጋችኋለሁ፣ እንደ እቃም ብትጠፉ እፈልጋችኋለሁ፣ እንደ ሰውም ብትጠፉ እፈልጋችኋለሁ ሲል ነው። አንዳንዴ ከሰውነት ክብር ወርደን እንደ እንስሳ የምንሆንበት ጊዜ አለና። " ሰው ክቡር ሆና ሳለ እንስሳትን መሰለ" እንዲል። ከእንስሳም ዝቅ ብለን በእቃ ልክ ስንገኝ እንደሚፈልገን ያጠይቃል።

በጠፉት ሶስት ምሳሌዎች በመጀመሪው ላይ ፈላጊው እረኛ ነው፣ ሁለተኛ ላይ እናት ነው፣ በሶስተኛው ላይ አባት ነው።

የሁላችን አባትም እናትም የሆነ እግዚአብሔር አምላካችን ነው። "አባታችን ሆይ " በሉ ብሎ እንዳስተማረን። ሊቃውንቱም እግዚአብሔር እናት እና አባት ብቻ ሳይሆን አያታችንም ነው ይሉናል።

ለዚህም ምሳሌ ሲጠቅሱ እንዲህ ይላሉ፦

እግዚአብሔር ራሱን በብዙ ምሳሌ እንዲመስል (በዶሮ በወፍ እየመሰለ እንዲያስተምር) ዶሮ ጫጩቶቿን ከእቅፎቿ በታች እንድትሰበስብ እንዲሁ የአለሙ መድህን እግዚአብሔር እኛን ይሰበስበናል።

ዶሮ ለጫጩት እናትም አያትም እንደሆነች እርሱ እናታችንም አያታችንም ነው። ምድራዊ እናት እና አባት በዋልንበት አይዉሉም በአደርንበት አያድሩም። እግዚአብሔር ግን በዋልንበት የሚውል ባደርንበት የሚያድር መልካም አባታችን/እረኛችን ነው። " እግዚአብሔር እረኛዬ ነው የሚያሳጣኝ የለም በለመለመ መስክ ያሳድረኛል በእረፍት ዉሃ ዘንድ ይመራኛል" እንዲል

እረኛ በጎቹን ቀን ከጠበቀ ሌሊት ይተኛል፣ እግዚአብሔር ግን እኛን ሲጠብቅ አይተኛም። "ሕዝቤን የሚጠብቅ አያንቀላፋም" ይላልና።

እረኛ በጉን ጠብቆ ካሳደገ በኋላ አርዶ ይበላዋል አልያም አርደው ለሚበሉት አሳልፎ ይሸጠዋል። እረኛችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ስለ መልካም እረኝነቱ በሰላሳ ብር ስለ በደላችን ተሸጠ። ተላልፎ ተሰጠ። ኢየሱስ ክርስቶስ በጎቹ የሸጡት እረኛ ነው።

እረኛው በጎቹን አርዶ ሲበላ የእኛን እረኛ ግን እኛ ተሰልፈን በቤተክርስቲያን ምሥጢር አርደን እንበላዋለን። የእረኛ ፍቅር እስከ ማረድ ነው። የእኛ እረኛ ግን ነፍሱን ስለ በጎቹ አሳልፎ እስከ መስጠት ነው።

ነገር በምሳሌ እንዲሉ ምሳሌው እንዲህ ነው፥

እረኛው እግዚአብሔር ነው
መቶ በጎች የተባሉት ሰውና መላእክት ናቸው።
አንድ በግ ጠፋ የተባለው ሰው ነው ዘጠና ዘጠኙ ነገደ መላእክት ናቸው።

ይሕ ምሳሌ የማዳኑን ሥራ ነው የሚያሳየን።

እኛ ሰዎች እንዴት ከቤተክርስቲያን እንጠፋለን ካልን፥

1ኛ. እንደ በግ ነው፦ በግ የሚጠፋው አውቆ አይደለም። የሚበላው ሣር የሚጠጣው ውሃ ፈልጎ የፊት የፊቱን ብቻ እያየ ሳያስበው ነው። እኛም ከቤተክርስቲያን ርቀን የሄድነው፣ ጠፍተን የሰነበትነው እንዲሁ እንደ በጉ ነው ሳናውቅ እንደምንጠፋ ሳናውቅ/ የጸናን ስለሚመስለን/የቆምን ስለሚመስለን ነው።

በጉ ስለሚበላ ስለሚጠጣ ሲል እንደ ጠፋው እኛም በእንጀራ ጉዳይ ከቤተክርስቲያን የጠፋን አለን። (ቢዚ ነኝ፣ ሥራ ይበዛብኛል፣ አይመቸኝም፣ እቤት ስገባ ይመሻል፣ ጠዋት ከቤት የምወጣው በሌሊት ነው፣ ቅዳሜና እሁድ ይደክመኛል፣ ማህበራዊ ጉዳይ አለብኝ፣ ቤተሰብ አስተዳዳሪ ነኝ፣ ልጅ አሳድጋለሁ ወዘተ እያልን በሰበብ ጠፍተናል። ከአንዱ ሥራ ሌላ ሥራ፣ ከአንዱ ትምህርት ሌላ ትምህርት እያልን ላንመለስ ሄደናል።)

የዚህ በግ ሳር መብላት ውሃ መጠጣት ክፋት የለውም ዋናው ችግር ከበረቱ መራቁ እንጂ። የኛም ችግር ሥራ መሥራታችን፣ ትምህርት መማራችን፣ ቢዚ መሆናችን አይደለም። ከቤተክርስቲያን መራቃችን እንጂ። በጉ ከበረት እየራቀ ሲሄድ ተኩላ ይበላዋል ወይም ሌባ ይሰርቀዋል የእኛም ከቤተክርስቲያን ያርቀናል ወይም በመናፍቃን ያስነጥቀናል/ያስክደናል፤ አልያም በዲያቢሎስ እንጠቀጥቃለን።

በጉ ሲጠፋበት እስኪያገኘው ድረስ ፈለገው፤ ሲያገኘውም እጅግ ደስ አለው አንስቶም በትከሻው ተሸከመው ይላል እግዚአብሔር አንድ አዳም ቢበድል ቢጠፋ እስኪያገኘው ድረስ እጅግ አሰልቺ በሆነ ትእግስት በሚጨርስ ፍለጋ ውስጥ አገኘው። ከቤቱ የጠፋን እኛንም እግዚአብሔር እስኪደክመው ሳይሆን እስኪያገኘን ድረስ ይፈልገናል። ለዚህም ነው በቃሉ ብርሃንነት ሊፈልገን በአደባባዩ አልገኝ ስንለው በማህበራዊ ሚድያ ሳይቀር ቃሉ እንዲነገረን ያደረገው። ለዚህኮ ነው ወደ እርሱ መሄድ ሲገባን ወደኛ የመጣው። እምቢ አሻፈረኝ ስንለው በመሰልቸት ሳይተው ወደ በረቱ እስክንመለስ ድረስ እየፈለገን ያለው።

አስቀድመን እንዳየነው የጠፋው በግ ሲገኝ በቤቱ ደስታ ሆነ በትከሻውም ተሸክሞ ወደ ቤቱ ወሰደው ሳያውቅ ነውና የጠፋውና። እኛንም የአለም መድሃኒት ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቤቱ ስንመለስ በዘጠና ዘጠኙ ነገደ መላእክት ዘንድ ደስታ ይሆናል ሳናውቅ ነውና የጠፋነው።

አውቆ ከመጥፋት ይሰውረን።

አሁን በዚህ ሰአት ይህን ቃል እንድናነብ ያደረገን፣ በቤቱ የሰበሰበን፣ በቤቱ እንድንኖር ያደረገን እኛ ፈቅደን መጥተን አይደለም እርሱ በፍቅር በትከሻው ተሸክሞን አምጥቶን እንጂ። ይኸን ጊዜ ከጽሁፍ ርዝመት ያልጨረሱት አሉ። አንተ እየጨረስክ ያለኸው በፍቅር በደስታ በትከሻው ተሸክሞህ ስለመጣ ነው እንጂ አንተ ከቃሉ ፍቅር ስላለህ አንተ ስለምትሻል አይደለም። እኛማ አለም እንዴት ሰነበተች?፣ የፖለቲካው ጡዘት የት ደረሰ?፣ ዋንጫውን ማን በላ?፣ ወዘተ የሚለው ሚድያ ላይ ነበርን። አሁን እዚህ የተገኘነው መርጠን አይደለም ተመርጠን እንጂ። ፈቅደን አይደለም ተፈቅዶልን እንጂ።
እኔኮ እፈልጋለሁ ለመምጣት ግን አይመራኝም እንላለን ዛሬ መርቶ ያመጣን እግዚአብሔር ነው የኛ ብርታት አይደለም። " በምህረትህ ብዛት ወደ ቤትህ እገባለሁ" እንዲል። እየፈለጉ ያልመጡትን እግዚአብሔር ያምጣልን። የመጣነውን በቤቱ ያለነውን አያርቀን።ያጽናን።

ክፍል ሁሉት ይቆየን።

ሐሙስ 29 ኦክቶበር 2020

ሁለት ምርጫ አለን

 ሁለት ምርጫ አለን

ደረሰ ረታ
19/2/2013

ሕጻናት ንጽሕ ናቸው፤ ለዚህም ነው ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋእለ ሥጋዌው ስለ መንግሥተ ሰማያት ሲያስተምር " እንደ ሕጻናት ካልሆናችሁ የእግዚአብሔርን መንግሥት አትወርሱም" ሲል ያስተማረው።

ሕጻናት:-
ከእናት እና ከአባታችሁ ማንን ትወዳላችሁ?
ከከረሜላ እና ከቸኮሌት የቱን ትመርጣላችሁ?
ከእናት ከአባት ከእህት ወንድማችሁ ማንን የበለጠ ትወዳላችሁ?
ወዘተረፈ
ተብለው ለምርጫ ሲጠየቁ
እናቴንም አባቴንም፣
ከረሜላም ቸኮሌትም፣
እናቴንም አባቴንም እህት ወንድሜንም ይሏችኋል።
ደግማችሁ ከሁለቱ አንዱን ምረጡ ብላችሁ ስታስገድዷቸው ሁሉቱንም/ሁሉንም ብለው ድርቅ ይላሉ። ሕጻናት ንጽህ ናቸውና። እምቢ ብትሏቸው እንኳን እምቢ ተጣልቼሃለው/ሻለሁ ብለው ጥለዋችሁ ይሄዳሉ አንዱን ብቻ አይመርጡም። ሌላኛውን ማጣት አይፈልጉምና።

እኛስ?

ከገንዘብና ከሰው፣
ከእምነትህ እና ከፖለቲካ፣
ከአገርህ እና ከጥቅምህ፣
ከወንድምና ከእህትህ፣
ከሥራህ እና ከሃላፊነትህ፣
ወዘተረፈ
ተብለን ስንጠየቅ ምላሻችን ብለን የምንሰጠው ይበልጣል ብለን ያሰብነውን አንዱ ነው እንጂ ምንም አይነት ማስረጃ አግኝተን አይደለም።ተልቀናል/አድገናል ብለን ስለምናስብ ስሌት ( calculation) ውስጥ እንገባለን።

አለማወቃችን ግን ከልጆች የዋህነት እና የልብ ንጽሕና ስለማይበልጥ ምርጫችን ስሕተት ይኖርበታል። በምሳሌ ስንመለከት ጥያቄው ከእናት እና ከአባት ለመምረጥ ምን መስፈርት ተቀምጦልን ነው አንደኛቸውን የመረጥነው? ከገንዘብ እና ከሰው እንዴት ልንመርጥ ቻልን? ሁለቱን አንድ የሚያደርጋቸው ምን መለኪያ ተገኝቶ ነው? እነዚህም እስኪ ይቅሩና ማን ነው አንዱን ብቻ ምረጡ ያለን? እንዲሁ ከሁለት ነገሮች መካከል አንዱን መምረጥ በምርጫ ሕግ ሥለምናውቅ እንጂ።

ሕጻናት ግን በቅንነት እና በፍቅር ሁለቱንም ይመርጣሉ።

አንዳንዶች ሰውን ከገንዘብ፣ ገንዘብን ከሰው ጋር ያነጻጽሩልንና አንዱን ከፍ አንዱን ዝቅ አድርገው በግድ አንዱን ምረጥ ይሉናል። ሁለቱም አስፈላጊነታቸውና መለኪያቸው ለየቅል ነውና።

ስለዚህ እንደ ሕጻናት ስንሆን ሁሉም የኛ ይሆናል። በ"እውቀት" ውስጥ ያጣነውን በየዋህነት እና በቅንነት ውስጥ ሁለቱንም እናገኘዋለን።

ሕይወትን በስሌት መኖር ሐጥያት ባይሆንም ቅሉ በየዋሕነት ሁለቱንም መምረጥ ግን ብልሕነት ነው ሁለቱንም ያስገኘናል እንጂ አያሳጣንም።

ገንዘብንም ሰውንም ይዞ መኖር ይቻላልና።

ከገንዘብ እና ከጤና ምረጡ ለሚሏችሁ ገንዘብንም ጤናንም እንደምትመርጡ ንገሯቸው።

አገርና እምነትን ለሚያስመርጧችሁ ሁለቱንም እንደምትመርጡ ንገሯቸው።

ከፖለቲካ እና ከመንፈሳዊነት ሲያስመርጧችሁ ሁለቱም ምርጫችሁ እንደሆኑ አረጋግጡላቸው።

የሰውን ልጅ ትክክል የሚያደርገው ከሁለት አንዱን መምረጡ ሳይሆን የመረጠውን እንዴት ይጠቅምበታል የሚለው ነውና። አንዳንዶች ገንዘብ ሃጢያት እንደሆነ ያወሩናል ድሕነት ጽድቅ ነው ወይ? ብዬ እጠይቃቸዋለሁ።

እንደዛ ቢሆን ኖሮ ድሆች ሁሉ ጻድቅ ሐብታም ሁሉ ሐጥአን በሆኑ ነበር። ነገር ግን እውነታው ሐብትን በአግባብ መጠቀም አለመቻል ነው ጽድቁም ሐጥያቱም።

ስለዚህ ሁላችንም ሁለት ምርጫ አለን። አንድም ሁለቱን አንድም ሁሉንም መምረጥ።

#######$$#######$$$#######

እኔን ለማግኘት ጽሁፎቼን ለመከታተል ከዚህ በታች የተጠቀሱት ሁሉ ወደ'ኔ ይመሩዎታል።

My Facebook page link (በፌስቡክ ገጽ እንገናኝ)

https://www.facebook.com/deresse2020/

Main facebook account (ዋናው የፌስ ቡክ ገጼ ይቀላቀሉት)

https://www.facebook.com/DeresseReta

Follow me through telegeram (በቴሌግራም ሊከታተሉኝ ከፈቀዱ) ሁሉም ምልከታዬን የማጋራባቸው ማህበራዊ ድረ ገጾች ናቸው።

https://t.me/deressereta

ከአሥር አመት በላይ ከ50ሺ በላይ አንባቢዎች ያሉት መጦመሪያም አለ።

www.deressereta.blogspot.com 

ረቡዕ 28 ኦክቶበር 2020

ባለሁበት አከባቢ መኖሬ እንዲታወቅ እፈልጋለሁ።

 ባለሁበት አከባቢ መኖሬ እንዲታወቅ እፈልጋለሁ።


ደረሰ ረታ
18/2/2013

ፍቅር ቃላት ብቻ ሳትሆን መስዋእትነትን፣ ክርስትና ምኞት ሳትሆን ሕይወት ናትና መኖርን፣ ማድረግን፣ ትሻለች። የአገር እና የቤተ እምነቶች ጥቃት፣ የክርስቲያኖችን እና የሙስሊሞች ስደትና ሞት፣ የአንድነታችን መላላት እየተመለከትን እንዲህ ቢሆን ኖሮ፣ እንዲህ ባይደረግ ኖሮ፣ እያልን ከመመኘት ባለፈ በተግባር የተፈተሸ፣በአርአያነት የተሞላ ማንነት፣ ፍቅርና ሕይወት ይፈልጋል።

ስለዚህ ባለን አጋጣሚ ሁሉ በተሰጠን እድሜና ጤና በየአጥቢያችን፣ በተለያዩ መንፈሳዊ ማህበራት፣ ተሰባስበን በያለንበት የተለያዩ ሕብረቶች በመሳተፍ መንፈሳዊነታችንን መገንባት፣ አገልግሎትን ማበርከት፣ አብያተ እምነትን እና ምእመናንን መርዳት፣ ወዘተ ይጠበቅብናል።ከአንድ ሁለት ይሻላልና።

አንዳንዶቻችን ከንፈር ስንመጥ እና ነገሮች አቅጣጫቸውን እንዲስቱ የተነሱበትን አላማ ይበልጥ እንዲያሳኩ ከማራገብ የዘለለ ፋይዳ የለንም።

አንዳንዶች ደግሞ አይተው፣ ሰምተው፣ ስሜቱን ተገንዝበው ዝምምምም የሚሉ አሉ። አይጠቅሙ አይጎዱ።

ነገር ግን ይህቺን አገር ወደፊት ለማስቀጠልም ሆነ ከጉዞዋ አደናቅፈው ወደኋላ ከሚያስቀሯት ይልቅ አፋቸውን ለጉመው ዝምታን በሚመርጡት ነው። ከአጥፊዎች ይልቅ የ"ገላጋዮች" ቁጥር እጅጉን ይልቃልና።

በልማትም ይሁን በጥፋቱ የሚሳተፉ፣ በማሳደድም ይሁን በማፈናቀል፣ በመግደልም ይሁን አካል በማጉደል፣ በመቀማትም ይሁን ባለማገላገል ከሚሳተፉት እንደ አገርም ሆነ እንደ መንደር ቁጥራቸው የሚበዛው አያገባንም ብለው ዝም ብለው የተቀመጡት ናቸው።

አገርም ሆነ ሕዝቡ አብዝቶ የሚጎዳውም ይሁን የሚጠቀመው ባጥፊዎች ወይም ባልሚዎች ሳይሆን በብዙ ዝምተኞች ምክንያት ነው።

አብዛኛው ሰው በመኖሪያ ቤቱ፣ በመኖሪያ ሰፈሩ፣ በመሥሪያ ቤቱ፣ በእድር በማህበሩ፣ በእቁብ በስብሰባው፣ መኖሩ አይታወቅም፤ እርሱም ብቻ አይደለም ምንም አስተዋጽኦ አያደርግም።ስለዚህ ሰዎች መኖሩን አያውቁትም። በክፉም በደግም ሥሙ አይነሳም።

እኔ ግን ባለሁበት አካባቢ፣ ባለሁበት ማህበረሰብ፣ ባለሁበት መሥሪያ ቤት፣ ባለሁበት እቁብና እድር ትልቅ ተጽዕኖ ፈጣሪ መሆን ቢያቅተኝ መኖሬ እንዲታወቅ እፈልጋለሁ። ኖሬ ከሌሎች በተሻለ ባልጠቅምም የለም በሚባል ግን በሥሜ ችግር እንዲፈጸም፣ በዝምታዬ ብዙዎች እንዳይጎዱ ስለምፈልግ።

እስኪ በየስብሰባው በዝምተኞች ችግር በጥቂት ተናጋሪዎች ስንት ውሳኔ እንዳለፈ፣ ስንት ጥፋት እንደተፈጸም፣ ስንት ሐብት እንደተመዘበረ፣ ስንት ሕይወት እንደተቀጠፈ፣ ስንት ትዳር እንደፈረሰ፣ ስንት ቤተሰብ እንደተበተነ፣ ስንትና ስንት ውድቀት አገሪቱ ላይ እንደ ደረሰ።

ከእድር ስብሰባ እስከ ፓርላማ ስብሰባ ስንት ዝምተኞች ስንት መኖራቸው እንኳን የማይታወቁ ሰዎች ዋጋ እንዳስከፈሉን የደረሰብን እናውቃለን።

ባላችሁበት ስፍራ፣ የሃላፊነት ቦታ፣ የተወከሉበት መድረክ፣ በተሰጠዎት አደራ፣ ... ብናገር ባልናገር ባደርግ ባላደርግ በማለትዎትና ዝም በማለትዎ ስንቶች ዋጋ ከፍለዋል? አገር ዋጋ ከፍላለች?

ትልቅ ቦታ አይሁን ተቀጥረውም ይሁን ተመርጠው፣ ተወክለውም ይሁን በበጎ ፈቃደኝነት በሚያገለግሉበት ቦታ የርስዎ ድርሻ ትልቅ እንደሆነ ያምናሉ? ሚሊዮኖች ከጀርባዎ እንዳሉ ይገነዘባሉ? የርስዎ ዝምታ፣ የርስዎ ዝንጋታ፣ የርስዎ አይቶ ማለፍና ሰምቶ መቻል ዋጋ እንደሚያስከፍል ምን ያህል ይሰማዎታል?

ባሉበት ቦታ የርስዎ እንዳሉ/መኖርዎ መታወቅ ማድረግ፣ ተጽእኖ መፍጠር፣ ድርሻዎትን በአግባቡ መወጣት፣ ... የምርጫ ጉዳይ አይደለም። የግዴታ ጉዳይ እንጂ።

ብዙዎች እያሉ እንደሌሉ ተቆጥረዋል፣ ብዙዎች ድምጸ ተአቅቦ አድርገዋል፣ ብዙዎች እስከ መፈጠራቸው ተዘንግተዋል፣ ... በነዚህ ምክንያት አገርና ሕዝቡ ዋጋ እየከፈሉ ነው።

እኔ ባለሁበት አከባቢ መኖሬ እንዲታወቅ እፈልጋለሁ። እርስዎስ?

#$$$#####@@@@####$$$$$&&&&$$#

እኔን ለማግኘት ጽሁፎቼን ለመከታተል ከዚህ በታች የተጠቀሱት ሁሉ ወደ'ኔ ይመሩዎታል።

My Facebook page link (በፌስቡክ ገጽ እንገናኝ)

https://www.facebook.com/deresse2020/

Main facebook account (ዋናው የፌስ ቡክ ገጼ ይቀላቀሉት)

https://www.facebook.com/DeresseReta

Follow me through telegeram (በቴሌግራም ሊከታተሉኝ ከፈቀዱ) ሁሉም ምልከታዬን የማጋራባቸው ማህበራዊ ድረ ገጾች ናቸው።

https://t.me/deressereta

ከአሥር አመት በላይ ከ50ሺ በላይ አንባቢዎች ያሉት መጦመሪያም አለ።

www.deressereta.blogspot.com 

ማክሰኞ 27 ኦክቶበር 2020

ከ"ሚሰበር ይሰንጠር"

 ከሚሰበር ይሰንጠር

ደረሰ ረታ
17/2/2013

አንዳንዶች ከትህትናም ይሁን ከስንፍና በተለይ መንፈሳዊ ነገሮችን ላለማድረግ እኔ ይቅርብኝ፣ እኔ ለዚህ ነገር ብቁ አይደለሁም፣ ከኔ የተሻሉ ሌሎች አሉ፤ በማለት ወደኋላ ሲያፈገፍጉ ይታያሉ።

ይሕ ተግባር ንሰሐ ለመግባት፣ ትዳራቸውን በመንፈሳዊ መንገድ ለመጀመር፣ በአገልግሎት ለመሳተፍ፣ ከዚህም አልፈው ስለአገራዊ ጉዳይ እነርሱን እንደማይመለከት ይሰማቸዋል። አገር የምትመራው በፖለቲከኞች ብቻ ይመስላቸዋል፤ ቢሆንም ቅሉ ፖለቲካን ይፈሩታል ይሸሹታልም።

ነገር ግን የእምነት ተቋምም ይሁን አገር ባላዋቂዎች ባህር ላይ እንዳለች ታንኳ ስትናጥ እነርሱም በዚህ ጉዳይ ጤናቸውን ያጣሉ። ደስታቸውም ሆነ ሰላማቸው ከሁለቱ ጋር በጥብቅ የተቆራኘ ነውና።

ስለዚህ:-

ጸሎት ከሚቀር በዝንጉእ ልቡናም ቢሆን ይጸለይ፣
ጾም ከሚቀር ንሰሐ ባንገባም ምጽዋት ባንሰጥም እንጹም፣ በጥቂቱ ስንታመን በብዙ የሚሾም ፈጣሪ ያበረታናልና።

ሥራችን ውጤት አልባ፣ ፍሬ ቢስ ቢሆንም፣ ምንም እንኳን እኛ ብንደክምም፣ ጥቅም ባናገኝበትም እንሥራ፣ ጋን በጠጠር እንዲደገፍ አገርም የኔ ድጋፍ ያስፈልጋታልና።

ውሃ ቢወቅጡት እንቦጭ የሆነ ማንነት ቢኖረንም ቅሉ ተመልሶ ጭቃ ብንሆንም ንስሐ እንግባ፤ እንጹም፣ እንጸልይ፣ ሥጋውን ደሙን እንቀበል፣ እናገልግል፣ ከስንፍና በራቀ ትህትና ውስጥ ሆነን ማገልገል ይጠበቅብናል መንፈሳዊነትም ይገባናል እንበል።

ሰይጣን እና ውሻ አንድ ናቸው፤ ውሻ የእውሩን በትር እንቅስቃሴ አይቶ እንዲሸሽ አይነስውርነቱ ውሻን በበትሩ መከላከል እንዳያግደው ሁሉ እንዲሁ ሰይጣንም በኛ ጸሎት እንደዛው ነው የምንጠራው ሥመ አምላክ ሃይል አለውና። ምንም የልብ ንጽሕና ባይኖረንም የአፋችንን እንቅስቃሴ ተመልክቶ ይሸሻልና እንጸልይ። ጸሎት ካለመጸለይ ይሻላልና። አገርን ማገልገል ካለማገልገልና በሙስና አገርን ከማቆርቆዝ ይሻላልና። ሁሉም ባለበት መስክ ታማኝ ሆኖ ካገለገለ አገር ትበለጽጋለችና።

እያንዳንዱ ሰው በየቤቱ በሕይወቱ ውስጥ እምነቱ የሚያስገድደውን ተግባር በትንሹም ቢሆን ቢያከናውን ካለማድረግ ይሻላል። ከ"ሚሰበር ይሰንጠር" ይላሉና አበው፤ የአገር ጉዳይ የአብያተ እምነት ጉዳይ ተሰብሮ ከሚጣል ተሰንጥሮም ቢሆን ቢቀጥል ይሻላልና። ነገ ስንጥሩ መደፈኑ አይቀርምና።

ስለዚህ ከአገር እና ከየእምነት ሥፍራችን ጋር ያለን ቁርኝት ተሰብሮ ከሚቀር ተሰንጥሮም ቢሆን ይቀጥል ነገ ሌላ ቀን ነውና።

በሌሎች አስተማሪ ጽሑፎች እንድንገናኝ ከታች ያሉትን ሊንኮች ይጠቀሙ።

My Facebook page link (በፌስቡክ ገጽ እንገናኝ)

https://www.facebook.com/deresse2020/

Main facebook account (ዋናው የፌስ ቡክ ገጼ ይቀላቀሉት)

https://www.facebook.com/DeresseReta

Follow me through telegeram (በቴሌግራም ሊከታተሉኝ ከፈቀዱ) ሁሉም ምልከታዬን የማጋራባቸው ማህበራዊ ድረ ገጾች ናቸው።

https://t.me/deressereta

ከአሥር አመት በላይ ከ50ሺ በላይ አንባቢዎች ያሉት መጦመሪያም አለ።

www.deressereta.blogspot.com 

እሑድ 11 ኦክቶበር 2020

በኛ ይብቃ ...

 በኛ ይብቃ ...

ደረሰ ረታ
1/2/2013

አደጋዎች በሽ ናቸው።

የትራፊክ አደጋ፣ በህክምና ስህተት የሚደርስ አደጋ፣ በብሔር ግጭት የሚደርስ አደጋ፣ በሃይማኖት ጥላቻ የሚደርስ አደጋ፣ በፖለቲካዊ አስተሳሰብ የሚደርስ አደጋ፣ በተፈጥሮ ክስተት የሚደርስ አደጋ፣ በሰው ሰራሽ በእቅድ የሚደርስ አደጋ፣ ወዘተረፈ በእነዚህና በሌሎች አደጋዎች የብዙዎች ንብረት ወድሟል፣ አካል ጎድሏል፣ ለስደት ተዳርገዋል፣ ለሞት ተዳርገዋል።

የተረፉት፣ የተጎጂዎች ቤተሰብ፣ የቅርብ ሰዎች በየሚድያው ይቀርቡና "በኛ ይብቃ ... ከኛ ተማሩ" ሲሉ ይደመጣል።

ከመች ወዲህ ነው ጥቃት መማሪያ የሚሆነው?

ከመች ወዲህ ነው ጥቃት መማሪያ የሆነው?

በምን መልኩ ነው መገደል መማሪያ ሊሆን የሚችለው?

እነማንስ ተምረው ድርጊታቸውን አቆሙ?

ከዚህ ልምድ የሚቀስሙት ገዳዮች ወይስ ሟች ነው ትምህርት የሚወስደው?

እኔ በበኩሌ ከዚህ አልማርም፤ በገዳዮች ስሕተት መሞት በቃኝ። በአጥፊዎች ተገፍቼ መኖር በቃኝ። በአሳዳጆች መፈናቀል በቃኝ።

እመራሃለሁ የሚለኝ መንግሥት ከስጋት ነጻ ሊያደርገኝ ይገባል፣ በዚህ ላይ ለተሰማሩት ፍርዲ ሊሰጥልኝ ይገባል፣ ሁሉንም እኔ እየሆንኩ በኔ ይብቅ እያልኩ መኖር በቃኝ።

በብሔር ግጭት የምሰደድ የምሞት እኔ፣ በፖለቲካ ሽኩቻ ንብረቴ የሚዘረፍ እና የሚወድም እኔ፣ በሐይማኖት ግጭት የምገፋ የማምለክ ነጻነቴን የማጣ እኔ፣ ... በቃኝ።

በኛ ይብቃ እያልኩ አልኖርም፤ ፍትህ ይገባኛል።

በሕክምና ስሕተት ህይወት የሚቀጥፉ፣ በፖለቲካ ቁማር ጫወታ ሕዝብ የሚያሰቃዩ አገር የሚያተራምሱ፣ በተረኝነት መንፈስ በሕዝብ ገንዘብ የሚጫወቱ፣ በግዴለሽነት በትራንስፖርት በመኪና አደጋ አካል የሚያጎድሉ ንብረት የሚያወድሙ ሕይወት የሚቀጥፉ የሚቀጡበት ሕግ ይሻሻልልን። ደማችን ፈሶ፣ ንብረታችን ተዘርፎ፣ ተስፋችን ሰልሎ፣ ሕይወታችን አልፎ አይቅር።

"በኛ ይብቃ" ይብቃን። በእነርሱም ተመጣጣኝ ቅጣት ይጣል።

#በወሊድ_ምክንያት_በሕክምና_ስሕተት_መሞት_በቃን
#በመኪና_አደጋ_መሞት_በቃን፣
#በሐይማኖት_ተለይቶ_መሞት_በቃን፣
#በእርስ_በርስ_ግጭት_መሞት_በቃን፣
#በተረኝነት_መገፋፋት_በቃን።

@deressereta

ከወደዱት ያስተምራል ብለው ካሰቡ like እና share ያድርጉ።
My Facebook page link (በፌስቡክ ገጽ እንገናኝ)

https://www.facebook.com/deresse2020/

Main facebook account (ዋናው የፌስ ቡክ ገጼ ይቀላቀሉት)

https://www.facebook.com/DeresseReta

Follow me through telegeram (በቴሌግራም ሊከታተሉኝ ከፈቀዱ) ሁሉም ምልከታዬን የማጋራባቸው ማህበራዊ ድረ ገጾች ናቸው።

https://t.me/deressereta

ከአሥር አመት በላይ ከ50ሺ በላይ አንባቢዎች ያሉት መጦመሪያም አለ።

www.deressereta.blogspot.com 

ጦማሩን ስለጎበኙ አመሰግናለሁ!

መልካም ነገርን ለሌሎች ማጋራት ባህላችን እናድርግ፤ ላልደረሰዉ በማጋራት ድርሻችንን እንወጣ፡፡

ትቶ እና ችሎ

  ትቶ እና ችሎ ብጹእ ወቅዱስ አቡነ መርቆርዮስ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ በደረሰ ረታ ብጹዕነታቸው ለሶስት አሥርት አመታት እኛ በማናውቀው እግዚአብሔር በሚያውቀው በብዙ መከራ በብዙ ፈተና ውስጥ ነው ያሳለፉት። ...