ማክሰኞ 23 ኦክቶበር 2012

የኢየሩሳሌም የመንፈስ ተጓዥ




የኢየሩሳሌም የመንፈስ ተጓዥ


…እነሆ ለሕዝብ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ደስታ
የምሥራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ ዛሬ በዳዊት ከተማ
መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ የሆነ መርገመ ሥጋ መርገመ
ነፍስ የሌለበት በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስ የሚያድል የዓለም
መድኃኒት የሚሆን የባህርይ አምላክ ክርስቶስ በዳዊት ከተማ
በዳዊት ባህርይ ተወልዶላችኋላና..
                                                                                                                                             አዘጋጅ ፡-ደረሰ ረታ
ዘመነ ጽጌ
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስትያን ስርአትና ደምብ መሠረት በየዓመቱ ከመስከረም 26 እስከ ኅዳር 6 ቀን ድረስ ወቅቱ ዘመነ ጽጌ ወይም ወርሐ ጽጌ  የሚባል ሲሆን፡ ይህ ወቅት በቤተክርስትያን ስርዐት መሰረት በየሳምንቱ ቅዳሜ ምሽት በዝማሬና በምስጋና ሊቃዉንተ ቤተክርስትያን እግዚአብሔርን እና እመቤታችንን ሲያመሰግኑ ያነጋሉ። ሊቃዉንቱ ምስጋና የዘወትር ስራቸዉ ቢሆንም ቅሉ ይህንን ወቅት ደግሞ በተለየ ሁኔታ ማኀሌተ ጽጌ በሚባለዉ ዜማ እመቤታችንን ሲያመሰግኑ ያድራሉ፤ የሊቃዉንቱ በረከት ይደርብንና እኛም በማብዛት ሳይሆን በማሳነስ፣ በማስረዘም ሳይሆን በማሳጠር እንዲህ በማለት እናመሰግናታለን።   

ድንግል ሆይ ለምስጋና በሚመች ቃላትና አንደበት አይደለም የማመሰግንሽ በረከሰ አንደበቴ ነዉ እንጂ፣ መላዕክት ዘወትር የሚያመሰግኑሽ ቅዱሣንም እንዲሁ በመራድና በመንቀጥቀጥ ያለማሰለስ የሚያመሰግኑሽ የእኔ ምስጋና እንደምን ያንስ ይሆን? ማርያም ሆይ ያንን በረሃ በጽምና በረሃብ ስለኔ  ሐጥያትና በደል ማቋረጥ ሳያንስሽ ማዘንሽ? በዚያ በበረሃ ለተንከራተቱት በበረሃዉ ሙቀት ለተቃጠሉት እግሮችሽ፣ ባዘንሽ ጊዜ ላነቡት አይኖችሽ፣ የበረሃዉ ግለት በፈጠረዉ ጽም የተነሳ ለደረቁት ከንፈሮችሽና ጎሮሮዎችሽ፣ ክብር ምስጋና ይገባቸዋልና አመሰግንሻለሁ።
  ድንግል ሆይ በደሌ ከአዳምና ሔዋን በደል እጅጉን ልቋልና፡ ነፍሴም ጎስቁላለችና የእናት ልመና ፊት አያስመልስ አንገት አያስቀልስምና ለበደሌ አሳስቢ!
ይህንን ወቅት አስመልክቶ መጠነኛ ዝግጅት እነሆ!!!!
                     በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ
አሜን
የኢየሩሳሌም የመንፈስ ተጓዥ
ክፍል ፩
    

-->
ማናችሁ ?ምንድናችሁስ? ስራችሁስ ምንድን ነው? ብትሉ፤ የሰው ልጆች ፍጥረት የመጀመሪያ የአዳም የልጅ ልጅ የሆን  የስላሴ አርአያ እና አምሣያ በስተምሥራቅ አፍሪካ ከምትገኝ ከኢትዮጵያ የፈለስን ስንሆን፣ስራችን ታሪክ ፀሐፊነት ነዉ፡፡
ታዲያ እኔና የስራ ባለደረባዬ ለስራችን የሚያገለግሉንን መሣሪያዎች አንግተን የበረሀውን ንዳድ ታግሰን ከፊታችን ደረቱን አስጥቶ የሚጠብቀንን የተያያዘ ዳገት ስንወጣ የዘመኑ ቴክኖሎጂ ያላየውንና የፎቅ መውጫ መውረጃ/ሊፍት/ሳያስፈልገን ቁልቁለቱን ስንወርድ ከርመን የእግራችን አሻራ እስኪጠፋ  በመጓዝ በዚያን ጊዜ ዘመን ተቆጥሮለት ትንቢት ተነግሮለት ስለተወለደው ህጻን  የመወለዱን ዜና ለመዘገብ እንዲሁም ፈርኦን ሊገለዉ ያሳድደዉ ስለነበር ወደ ግብጽ ስለተሰደደዉ ስለዚሁ ህጻን ለማወቅ በመንፈስ ወደ ኢየሩሳሌም ተጉዘናል። ኢሣይያስ አማኑኤል ብሎ ከ740 ዓመት በፊት በትንቢት የተናገረለት ዩሴፍም በትንቢቱ መሰረት በተወለደ በስምንተኛው ቀን ኢየሱስ ብሎ  ስለሰየመው ድንቅ ነገር ለመጻፍ ከስፍራችን ይህ ምሥጢር ወደተፈጸመበት እና ወደሚያቁት ሰዎች አመራን፡፡
ታሪኩንም በደንብ ግልጽ ሆኖልን እንድናውቀው ትንቢት የተናገሩለትንም አንዳንድ የእድሜ ባለፀጋ በሕይወት ስለምናገኛቸው ከልደቱ ጀምረን ያለውን ለማወቅ የዳዊት ከተማ ወደሆነች በያዕቆብ ዘመን ኤፍራታ እየተባለች   ወደምትጠራዋ ከአየሩሳሌም ወደ ደቡብ   ዘጠኝ (9) ኪሎ ሜትር ርቃ ወደምትገኝ ቤተልሔም ተጓዝን፡፡
-ቤተልሔም ማለት የስሟትርጓሜ የእንጀራ ቤት ማለት ነው፡፡
የታሪኩን ሙሉ መረጃ ለማግኘት ያነጋገር ነው የባለታሪኩን እናት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያምን፣ ጠባቂዋ/እጮኛዋ/ የነበረውን የዕድሜ ባለፀጋ የሆነው ቅዱስ ዩሴፍን፣ በተተነበየለት ትንቢት መሰረት እስከዚያን ዕለት እና ከዚያም በኋላ የቆየውንና በጣም አርጅቶ ሳለ ህጻኑን ሲታቀፍ እርጅናው የታደሰለትን ስምኦንን የልደቱን ሁኔታ ለማየት በሰዓቱ ከሩቅ ምስራቅ መጥተው የነበሩ ሰብዓ ሰገልን እና እረኞችን እንዲሁም  የአካባቢዎች ሰዎች ነበር፡፡
ለመጀመሪያ ጊዜ ግን ያመራነውናጥያቄያችንን ያነሣነው ለሰብዓ ሰገል እና ለእረኞች ነበር፡፡  ከሁሉም በፊት የምናምንበትን ፈጣሪ ስራችንን እንዲባርክ በጸሎት በመጠየቅ ነበር፡-
ቅድመ ዓለም የነበርክ ዛሬም ያለህ ዓለምንም አሣልፈህ ለዘለዓለም የምትኖር ያለትናንት ቀዳማዊ ያለነገ ደሀራዊ የምትባል ጥንታዊ እና ቀዳማዊ የሆንክ በባህሪ ሞት በመንግሥትህ ሽረት የሌለብህ የሠራዊት ጌታ  እግዚአብሔር  አምላክ  ሆይ ራስህን ዝቅ በማድረግ በቤተልሔም በከብቶች በረት ውስጥ ከእናትህ ከድንግል ማርያም የተወለድህ ክብር ምስጋና ይድረስህ፡፡
በመቀጠልም የአምላክነቱ ድንቅሥራ ተደርጎላቸሁ በቦታው በመገኘት እና ታላቅ ምሥጢሩን ለማየት የታደላችሁ ቅድስት ሰሎሜ እና ቅዱስ ዩሴፍ እንዴት አላችሁ?እናንተስ በአካባቢው ሰዎች ዘንድ ተንቆ የነበረን ስራ በመስራት በእረኝነት ላይ ያላችሁ የሀገረ ገሊላ እረኞች ዛሬን እንዴት ደረሣችሁ? ሠላምታችንን እንዲህ ከጀመርን በሁላ ጥያቄያችንን የቀጠልነው እንዲህ በማለት ነበር፡፡
ከሩቅ ምሥራቅ ኮከብ መርቷችሁ ለአምላካችሁ እጅ መንሻን ለማቅረብ ወደጌታ ዘንድ የቀረባችሁ ሰብዓሰገል ከመንገዱ ብዛት የተነሣ ካልደከማችሁ አንዲት ጥያቄን ልጠይቃችሁ?
ዘጋቢው፡-ለመሆኑ ጌታ እንደሚወለድ እንዴት አወቃችሁ?
ከቦታችሁስ ስትነሱ ብዛታችሁ ስንት ነበር? ይህ መንፈሳዊ ጉዞአችሁሰ ስንት ቀን ፈጀባችሁ? እናንተስ በመላእክት አብሣሪነት መወለዱን ያወቃችሁ እና በእልልታና በዝማሬ ጌታችሁን ያመሰገናችሁ የሀገረ ገሊላ አረኞች፡ መወለዱን ሥትሰሙ ምን ያህል ደነገጣችሁ፤ በእውነቱ መወለዱን አይታችሁ ሥተመለሱስ የቱን ያህል ተደሰታችሁ?
ሰብዓሰገል፡- የጌታን መወለድ ያወቅነው ነበዩ ሚኪያስ በትንቢት ተናገሮ ስለነበረ በዚያ ምክንያት እና ጊዜውም መድረሱን በአባታቻን ጃንደራሽ ትምህርት አማካይነት ኮከቡን በማየት ነበር፡፡ ከቦታችንም ስንነሣ ከየነገዳችን ከካም ነገድ ሶስት እልፍ፡ ከሴም ነገድ ሶስት፡ እልፍ ከያፌት ነገድ ሶስት፡ እልፍ በአጠቃላይ ዘጠኝ እልፍ በመሆን ነበር፡፡
ጉዞአችንም ኮከቡን በምስራቅ እያየን በኮከብ እየተመራን ሄሮድስ በተንኮል እንደነገረን ሣይሆን በህልም መልዐኩ እንደነገረን በሌላ ጐዳና በመሄድ ነበር የደረስነው፤ ወዴት ነው? እያልን እንዳልመጣን አገኘነው እያልን ተመለሰን፣ ንጉስ አይሁድ ብለን እንዳልሄድን አምላክ መሆኑን አምነን/አውቀን/ተመለስን፣ ስንሄድ ድፍን ሁለት ዓመት ሙሉ እንዳልፈጀብን በ40 ቀናችን ሀገራችን ተመልሰን ገባን፡፡
እረኞች፡-  መወለድ የሚለው ቃል ምንም አያስደነግጥም ትንሽ ግራ የሚገባው እና የማያስደነግጠው ምንም እንኳን ትንቢት ተነግሮለት ዘመን ተቆጥሮለት ሱባዔ ተገብቶለት የተወለደ ቢሆንም የሰዎችን ልጆች ለመውለድም ሆነ ለመወለድ የሚያበቃ አምላክ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ ለዚያውም በከብቶች በረት መወለዱ ነበር ያሰደነገጠንና ግራ ያጋባን፡፡
መወለዱን አይተን ደስታውን እየተካፍለን ስንመለስ የተሰማን ደስታ ልክና መጠን የለውም ይህን ይመስላል፣ ይህን ያክላል አይባልም፡፡ አንልምም፡፡
---የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ ወዴት ነው ? እያላችሁ ስትመጡና ንጉስ ሄሮድስ ግቢ ስትደርሱ ንጉስ ሆኖ ሣለ ሌላ ንጉስ ወዴት ተወለደ ብላችሁ በመጠየቃችሁ አልፈራችሁም?
ሰብዓሰገል፡-ንጉስ ሲባል እንኳን ሠራዊቱን አልፎ ድርጊቱንና አስፈሪውን ፊቱን ታይቶ ይቅርና ስሙ ራሱ ሲጠራ በጣም ያስፈራል፡፡  ከዚያም ባሻገር ንጉስ እራሱን ሌላ እርሱን የሚተካ ከስልጣን የሚያወርደው ንጉስ የታለ ብሎ መጠየቅ ያስፈራል፡፡ ነገር ግን ነብዩ ኢሳይያስ እንደሚለው ኃያልነቱ በግፍ ተገዝተን ችግር ተደራርቦብን የኑሮ ጫና ወገባቸውን ያጐበጠውን የግፍ አገዛዝ የመረረንን ያስወግድልናል፣ ያቃናልናል፣ ከበታቹም ቀኝ አዝማች እና ግራ አዝማች ብሎ ይሾመናል፣ የቅርብ ወዳጆቹም የመንግስቱ አማካሪዎችም ያደርገናል ብለን አስበን ስለነበር የወደፊት ደስታችን/ተስፋ/የዚያን ሰዓቱን ፍራቻችንን አስወግዶልን ስለነበር አልፈራንም፡፡
-ሁለት ዓመት ሙሉ ተጉዛችሁ ቤተልሔም ዋሻ ስትደርሱ ምን ተሰማችሁ?
ሰብዓሰገል፡- መቸስ የእግር ጉዞ ስትጓዝ ምን ያህል አድካሚ እንደሆነ ልነግርህ አልችልም፤ እንኳን እኛ ህፃኑን ለማግኘት የተጓዝነው ቀርቶ እናንተ ይህንን ጥያቄ ለእኛ ለማቅረብ የፈለጋችሁትን ፍለጋ ብዙ እንዳደከማችሁ አይታችኋል፡፡  እኛ እንግዲህ ስንጓዝ አንድ ነገር ማለትም የምናገኘውን ንጉስ /አምላክ/ ተስፋ አድርገን ስለነበረ ተስፋው ያበረታን ነበር በተጨማሪም ይመራን የነበረው መልዐክ ስለሚያጽናናን አንዳች ፍራቻ የለብንም ። በጉዞአችን ያጋጠሙን ገጠመኞች ደስታ ስለነበሩ ከደስታው በቀር ሌላ የምናስታውሰው አንዳችም የለም፡፡እንግዲህ የተሰማን ደሰታ ብርታት ነበር፡፡
--አስቀድመን ጥያቄውን እንደጀመርንላቸሁ በቂውን መልስ ማግኘት የምንችለው ከእናንተ መሆኑንና በዕለቱም እንደነበራችሁ ተነግሮናል ይህ እንዴት ነበር?
እረኞች፡-የዚህን ታሪክ መፈጸም ልጆች ስለነበርን ከሰዎች ጋራ ስለማንገናኝ እንዲሁም ሁልጊዜ ውሉአችን ከከብት ጋር ስለነበር ምንም የምናውቀው ነገር የለም ነበር። ነገር ግን ድንገት ከብቶች እያገድን ሳለን ከሰዎች ወገን ያልነበረ ነጭ ልብስ የለበሰው መጣ፤ ወደኛ ዘንድም የሚያበራው ብርሃን እየቀረበን ሲመጣ ከታላቅ ምስጢርነቱም በተጨማሪ ልጅነትም ስለነበር ከመደናገጣችን የተነሳ ያቺን ዕለት ረገምን የተፈጠርንባትን ቀን እንደ ዕለተ ሞታችን አየናት መሬት ተስንጥቃ ብትዉጠን ተመኘን። መቸስ የዚያን ዕለት ፍራቻና ደስታ ምን ቃላት ይገልጸዋል እጅግ ፈራን እጅግም ደስ አለን፡፡
---ምን ደስ የሚያስኝና የሚያስፈራ ነገር አያችሁ?
እረኞች፡-እኛ እረኞች ስለሆንና በሰዎች ሁሉ ዘንድ የተናቅን ስንሆን ይህን ከሰው ወገን ያልሆነ ነገር ማየት እጅግ ያስፈራን ነበር (መልዐክ ማየታችን)፡፡  ምክንያቱም ለማጥፋትም ለመራዳትም ይመጣሉና፡፡
--ይህ ወደ እናንተ የመጣው ነጭ ልብስ የለበሰ መልዐክ ምን አላችሁ?
እረኞች፡- ይህ ግርማ ሞገሱ የሚያስፈራ መልዐክ ወደኛ ሲመጣ እንዲህ የሚል ቃል ነበር የተናገረን… …  እነሆ ለሕዝቡ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ደስታ የምስራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ ፤ ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ የሆነ መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስ የሌለበት፤ በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስ የሚያድል፣ የዓለም መድኃኒት የሚሆን የባህረይ አምላክ ክርስቶስ በዳዊት ከተማ በዳዊት ባህርይ ተወልዶላችኋልና  አለን፡፡  ለመልዐከ  ፍርሃት አርቆ መናገር ልማድ ነውና አትፍሩ አለን። ይህ ቃል ነበር በተለይ በጣም ደስ እንዲለን ያደረገው፡፡  ያው እኛም ስለተደናገጥን  ለተወሰነ ሰዓት በመካከላችን ዝምታ ሰፈነ ድንገት እንደመጣ ድንገት በአፋጣኝ ሁኔታ ተለይቶን ሣይሄድ መጠየቅ ያለብንን ጥያቄ አቀረብን ጥያቄውም እርሱ መሆኑን በምን ዓይነት ምልክት ማወቅ ይቻላል? የሚል ነበር እርሱም ለጥያቄያችን መልስ እንዲህ ሲል ነገረን … “….ሕፃን ተጠቅልሎ በግርግም ተኝቶ ታገኙታላችሁ” ብሎን ወደ መጣበት ሄደ፡፡ እኛም እርስ በርስ መልዐኩ የገለጠልንን ይህን የሆነውን ነገር ለማየት ወደቤተልሔም እንሂድ በመባባል ጉዞአችንን ወደ ቤተልሔም ቀጠልን፡፡
-ለመሆኑ ወደዚህ ወደተባለው ሥፍራ ሥትጓዙ ሁላችሁም ተስማምታችሁ ነው የሄዳችሁት? ምንም ችግርስ የለም ነበር?
እረኞች፡- መቸስ አንድ ነገር ሲታቀድ እንከን አያጣውም ገና ከመጀመሪያው ጀምሮ ፍርሀት  በውስጣችን ነግሶ፤  በመሐል ላይም አለመግባባት ተፈጥሮ ስለነበር ግማሾቻችን እንሂድ ስንል ግማሹ አይ አንሄድም ምን እንደሆነ አውቀን ነው የምንሄደው? መሽቶብናል፣ ስንቅም ጨርሰናል፣ አንሄድም የሚል አለ። ከፊሉ ደግሞ ይህ አሁን ተገልጾ የተሰወረው ያኔ አዳምን “… እኔ የብርሃን መልዐክ ነኝ” ብሎ ይዞ ከወጣ በኋላ ደም እንደ ጅረት እስኪፈሳቸዉ ድረስ የወገራቸው ሰይጣን ቢሆንስ ብሎ ያመነታ ነበር፡፡
--መጠርጠር መልካም ነው፡- ታዲያ በጨረሻ ምን ላይ ደረሳችሁ?
እረኞች፡-በመጨረሻ ሰዓት እግዚአብሔር የወደደውን እና የፈቀደውን ነውና የሚያደርገው ሁላችንም የምስጢሩ /የደስታው/ ተካፋይ ሆንን፡፡
-ወደእዚሀ ስፍራ ስትደርሱ ማንን አገኛችሁ?
እረኞች፡-  ይህንን ስፍራ ከዚህ ቀደም ምንም እንኳን ብናውቅም በዚህን ዕለት ግን በጣም ለየት ያለ ነበር፡፡  ቦታዋ እንኳን እጅግ ከብራለች ጸጋንም ተጐናጽፈለች፣ከዚህ ቀደም የምናዉቃት መንደር አትመስልም። በዚህ የተከበረ ስፍራ በሐመልማለ ሲና የምትመሰለዋን ምራገ ጸሎት የሆነች የህፃኑን እናት ማርያምንና ዩሴፍን ህፃኑን በግርግም/ በከብቶች በረት/ ተኝተው አገኘነው፡፡
----እንኳን እናንተ ተአምረኛውን ያገኛችሁ እኛ እናንተን ስናገኛ በጣም ደስታ ተሰምቶናል፡፡  እናንተስ ምን ተስምቷችሁ ነበር ምንስ አላችሁ?
እረኞች፡- መቸስ በልቦናችን የተሰማንን ደስታ ለመግለጽ  ቃላት አይገኝለትም ብቻ ባጭሩ ወደር የማይገኝለት ደስታ ተሰምቶናል፡፡ እንደደረሰንም በህፃኑ ፊት ፍግም ብለን ከሰገድን በኋላ ስለእርሱ የተነገረን ነገር ነገርናቸው ከመላዕክትም ጋራ አመሰገንነው፡፡
-እዚያ ስትደርሱ ምንም ችግር አላጋጠማችሁም ነበር?
እረኞች፡- አጋጥሞን ነበር አንድ ሀሩር የሚባል ሰው ህፃኑ የተወለደበትን ቦታ ላሳያችሁ ብሎ በልቡ ተንኮል አስቦ ወደሌላ ስፍራ ሊወስደን ቢል መላዕክት አንገቱን ቆርጠው ጥለዉት እኛም አንገቱን  ቅሌ/ገና/ ተጫውተንበታል፡፡
-እረኝነት ብዙ ሰዎች እነደተራ ይቆጥሩታል፡፡ እናንተስ እረኝነተችሁን እንዴት ትመለከቱታላችሁ?
-   እረኞች፡-  ሁሉም ነገር ክብደትና ቅለት የሚሰጠው እንደተመልካቹ እና እንደነገርየው ዓይነት ነው፡፡ እኛም ምስጢሩን ስንመለከት የዓለም ጠባቂ/እረኛ/ የሆነው የኢየሱስ ክርስቶስ ምሣሌ መሆን ማለት በጣም ትልቅ ክብር ነው፡፡  ስለዚህ ይህ ክብር ለእኛ በፍጹም የሚገባ አልነበረም፡፡  ታናናሾችን ከፍ የሚያደርግ አምላክ ግን ሁሉን አደረገ፡፡
-ለጊዜው ከእረኞች ጋር ያለንን ጥያቄ  በዚህ አቋርጠን አብረው ወደነበሩት ሰብዓሰገል ጥያቄአችንን እንዲህ በማለት ሰነዘርን፡-
እንግዲህ ባለፈው ስንነጋገር ከሩቅ ምስራቅ ለህፃኑ  ልትሰግዱ የመጣችሁት በነቢዩ ሚክያስ ትንቢት መሰረት እንደሆነና ስትመጡም ወደ ንጉስ ሄሮድስ ዘንድ እንደደረሣችሁ ነበር የነገራችሁን መንገዱም ሁለት ዓመት መፍጀቱን ነገራችሁናል፡፡ ለመሆኑ  ወደ እዚህ  ስፍራ  ስትመጡ ሁለት ዓመት በመጓዝ ከዚያ ደረሳችሁ ንጉስ ሄሮድስ ፈት ስትቀርቡ ህፃኑ ወዴት እንዳለ ሲነግራችሁ ያላችሁ ነገር ነበር?

ሰብዓሰገል፡-   ንጉስ ሄሮድስ ጋርም ስንደርስ ህፃኑን አገኝታችሁ ሰግዳችሁ ስትመለሱ መጥታችሁ ለእኔም ወዴት እንዳለ ንገሩኝና ሄጄ እሰግድለታለሁ ብሎ ነበር፡፡  እኛ ግን ስንመለስ በዚያ አልተመለስንም፡፡
ንጉሥ ሄሮድስ እኔም እንድሰግድለት መጥታችሁ ንገሩኝ  ሲላችሁ ለምን ነበር ያልነገራችሁት  ለምንስ በሌላ መንገድ ሄዳችሁ?
-ሰብዓሰገል፡-  “ሄጄ እስግድለታለሁ” የሚለው ቃል ደባን ያዘለ ቃል ነበረና፤ሊሰግድለት ሣይሆን ሊገለው ነበር ተመልሣችሁ ንገሩኝ ያለው ለዛብለን ነዉ። አንድም መልዐኩ በመጣችሁበት በኩል አትሂዱ ስላለን ነበር በዚያ ያልተመለሰነውና በሌላ መንገድ የሄድነው።
-ይመራችሁ የነበረው ኮከብ ሁለቱንም ዓመት ያበራ ነበር እንዴ?
ሰብዓሰገል፡-መንደር ሲገባ ከሰው ሥንገናኝ ይሰወራል፡፡  በረሀ በረሀውን ስንጓዝ ግን አቅጣጫውን ይመራን  ነበር፡፡
- ከዚህ ቀደም አመጣጣችሁ ከወዴት ነው ስንላችሁ ከሩቅ ምስራቅ እንደመጣችሁ ነበር የገለጻችሁት ከሩቅ ምስራቅ ስትሉ ከየት ከየት አካባቢ ነበር?
-ሰብዓሰገል፡- ከብዙ ቦታ ቢሆንም ልብ አምላክ ዳዊት በትንቢቱ፡- “በፊትም ኢትዮጵያ ይስግዳሉ ጠላቶቹም አፈር ይልሣሉ” መዝሙር 71፣9 የሚል ስላለ ከኢትዮጵያም የመጣን ነበርን፤



-->
-ሰብዓሰገልንም በዚሁ መልኩ ጥያቄአችንን ካቀረብንላቸው በኋላ በቀጣዩ ደግሞ በስደቱ ላይ አብረው ወደነበሩት አምርተን ቅዱስ ዩሴፍን ቀዳሚ ተጠያቂ አድርገናል፡፡  በዘመኑ ወደነበረው ቆጠራ ሄዶ ስለነበር ለምን እንደሄደ  ላነሳንለት ጥያቄ እርሱም እንዲህ ሲል መልሶልናል፡፡
..ዩሴፍ፡- ለቆጠራ የሄድኩት ሰው ሁሉ ይቆጠር ዘንድ ለ41 ዘመናት በሮም የነበረ አገረ ገዥ አውግስጦስ ቄሳር ባወጣው ትእዛዝ መሰረት ለመቆጠር ነዉ፡፡
--ለ41 ዘመን በሮም ላይ አገረ ገዥ የነበረው የአውግስጦስ ቄሳር ማን ነዉ እንደሆነ ብትነግረን?
ዩሴፍ፡- አባቶቻችን ፡ውሃ ከጥሩ ነገር ከስሩ ይላሉ እኔም ታሪኩን ከስር መሰረቱ ልንገራችሁ ድሮ ያኔ የሮም ንጉስ  ከአንድ ጐልማሣ ሚስት ዘንድ ያለፈቃድዋ ደረሰባት/ደፈራት/ ባልዋን  ከልብ የምታፈቅር ሴት ነበረችና ያለፈቃድዋ ሌላ ወንድ ስለደረሰባት ታንቃ ሞተች፡፡ ወንድሞቿ እህታችን የሞተችው በእርሱ ምክንያት ነው ብለው ከቤተ ጣዖት ገብቶ ሲወጣ አንቀው ገደሉት፣ ኋላም ሕዝቡ እርሱም እርሷም የሞቱት አንድ ሰው ኃጢያት ሲሰራ ዝም ስላልን አይደለምን? ብለው ነገር የሚወስኑላቸው 120 ሽማግሌዎች ሾመዋል፡፡ ከ120 ሽማግሌ የአንዱ ሽማግሌ ሚስት ጸንሣ ሳለች በምትወልድበት ግዜ ሞተች ገንዘን እንቀብራለን ሲሉ ጽንሱ በማህጠኗ ተንቀሣቀሰ፣ ሕያውን ከምውት ጋር እንቀብራለን? ብለው ሆዷን ቀደው አወጡት አደገ ኃያልና ምሁር ሆነ፡፡  በስተመጨረሻም ሁሉንም አጥፍቶ ለንግስና በቅቷል ታሪኩ እንዲህ ነበር፤ተረዳችሁ?
- አመጣጡን ና አነጋገሱን እንዴት እንደነበር ግልጽ ብታደርግልን?
ዩሴፍ፡- ሽማግሌዎች ወገን ስለነበር /ስለተወለደ/ ስሙን ብልዮስ ቄሳር ብለዉታል።ብልዮስ ቄሳር ጋስዮስ ቄሳርን ጋስዮስ ቄሳር አዉግስጦስ ቄሳርን ይወልዳል፤የአዉግስጦስ ቄሳር አመጣጥ እንግዲህ  ይህንን ይመስል ነበር።አነጋገሱ ደግሞ ህዝቡ በሀገራቸው አንድ ኃይለኛ ጠላት ተነስቶ አስቸገራቸዉ አጥፋልንና  እናነግስሀለን አሉት፡፡ እርሱም ኃያል ስለነበር በኃይሉ ተማምኖ ከአነገሣችሁኝ እሺ  በእጄ ብሎ አጥፍቶላቸዋል፡፡  እነርሱም ቃል  እንደገቡለት አንግሰውታል፡፡በቃ…..
-ታድያ አዉግስጦስ ቄሳር ህዝቡ እንዲቆጠር ያደረገዉ ለምንድን?
ይህንን እና ሌሎችን ቀሪ ምሥጢር በክፍል ሁለት እንዳስሳለን፤ በመንፈስ አብራችሁን ስለተጓዛችሁ እያመሰገንን ለክፍል ሁለት ያበቃን ዘንድ ጸልዩ። መልካም የጽጌ ዘመን ይሁንልን፣ ይቆየን።

ማክሰኞ 16 ኦክቶበር 2012

የጉዞ ማስታወሻ


     የጉዞ ማስታወሻ

እንደባቡር ፋርጎ ሳይነጣጠሉ እደተቀጣጠሉ መጓዝ ግድ ይላል ትልቁ ትንሹን ትንሹ ትልቁን በስተጀርባው እያስከተለ መጓዝ ግድ ይላል የቸኮለከሰንሰለተማው የጎዞ ውህደት ውስጥ ይነጠላል ደርቦ ማለፍ ለማለፍ መንሰፍሰፍ መሽሎኪያ ቀዳዳ መፈለግ የሾፌሮች ስራ ነው ተሳፋሪመጣደፉ መሳቀቅ መፀለይ የየሰዓቱ ሥራቸው ነው 12፡30 ከአ.አ መነሐሪያ የወጣው 2ኛ ደጃ አውቶብስ 2፡10 ደብረ ዘይት መንገድደረሰን መንጋቱን ማመለከቻውና የቁርስ ሰዓት ብስራቱን ለማሰማት ሁለት የመኪናው ረዳቶች ከፊት ከኋላ ፌስታለቸውን ማንኮሻኮሽ ጀመሩአፍታም ሳይቆይ አንባሻዎችን ለተሳፋሪ ማደል ጀመሩ፡፡ ቁርስ መሆኑ ነው ቁርሱን ምሳውና እና እራቱን የሰነቀው መኪና በአሽከርካሪው አማካይነት አስፋልቱን ለሁለት እየሰነጠቀ ይፈተለካል ወደ ሐረር የመቻቻልና የትብብር ከተማ፡፡
     የደብረ ዘይት (ቢሾፍቱን) እንደ ወጡ ትላልቅ ድንኳን የመሰሉ ቤቶችን ማየት ሲጀምሩ የኦሮሚያ ክልል ውስጥ የሚገኙ መሆንዎን መዘንጋት የለብዎትም በአንጻሩም ያቆጠቆጡ ሰብሎችና ጥቋቁር መሬቶች የአይንዎ ማረፊያ ናቸው ጆሮዎትን ጣል ካደረጉ ፌስታል የሚል ሰው ድምጽ ይሰማሉ ሊያባላሹም ይችላሉና፡፡ ሽንቱ የመጣበት ሰው እንዲሁ ለረዳቱ ያሳውቃል ረዳቱ ለሹፌር መኪና ይቆማል ተንፍሰው ይመለሳሉ አንዳንድ ቤቱ የደረሰ ይመስለውና ወደ መኪናው በቶሎ ባለመመለስ ጉዞውን ያዘገያል የተለመነው የመኪና ረዳት እባካችሁ ግቡ በማለት ተሳፋሪውን ያስገባል፡፡ ግራ ቀኙን እየቃኙ ተፈጥሮን እያደነቁ ይሄዳሉ 2፡35 ሞጆ ከእንቅልፍ ነቅታ ተግታ ህዝቧን ለሥራ እያሰማራች ነው እኛም ወደ ጉዞአችን ሞጆ ሜዳ ላይ ደረቱን ያሰጣው ደረቅ ወደብና ተርሚናል መንጋቱ ስለሆነ ፀጥረጭ ብሏል፡፡
     በየመንገዱ ግራ ቀኝ ቅጠሎቻው ረግፈው ቅርንጫፎቻቸው የቀሩ የግራር ዛፎች የክረምቱን የምስራች ድምጽ ሰምተው ማቆጥቆጥ አንገታቸውን ቀና ማድረግ ጀምረዋል፡፡
     ከንፋስ የኤሌክትሪክ ኃይልን የሚሰጡ ተርባይን ሲመለከቱ የአዳማ መዳረሻ ምልክት እንጂ ሌላ ስራ ያለው አይመስልም እንደየዋህ ፀባዩን አሳምሮ ቆሞ ሲመለከቱት እርሱን እየተመለከቱ ሲጓዙ ኦሮሚያ ፖሊስ ኮሌጅን ያገኙታል፡፡
     የአዳማ ውበት አባ ገዳ ህንጻ አ.አ ሳትነቃ አመልጣችው የመጣችው ተጓዦች እንኳን ደህና መጣችሁ ይህ ሥፍራ የስምጥ ሸለቆዋ እንቁ የአዳማ ከተማ ነው ይላችኋል፡፡ አሁን ከነጋ 3፡00 ሠዓት ሆኗል፡፡
     ይቺን ሞቃታማ ከተማ የኦሮሚያ ክልል ንግሥት እንደ ዋዛ የክረምት ጎም እንዳጠላበት እንደከረፈች ፈገግታዋን ሳናይ ጥለናት እብስ አልን እኛም ቅር ብሎን እርሷም ከአቅሜ በላይ ነው ጊዜው ክረምት ነው እያለች ህፃን ልጅ ከእናቱ እንዲነጠል ተነጣጠልን፡፡ ጊዜው እርሷ ዝናብን እያነባች እኛም እያዘንን እርስ በርስ ተያይዞ የቆመውን ተራራማ ምድር እየሰነጠቅን በመጓዝ ወለንጭቲን ያለፍነው ጠዋት 3፡30 ሰዓት ላይ ነበር፡፡ አሁንም ቢሆን ደፍሮ እንደሰንሰለት የተያያዙትን ተራሮች ሊለያያቸው የሚችል የለም፡፡ ለእድሜ ዘመናቸው ላይለያዩ በምድር ተማምለው ፍቅር መስርተዋልና አሁንም አብረው ናቸው፡፡ ወደ ፊትም አይለያዩም የፈጠራቸው ደግሞ እሰኪመጣ በዚህ መድር ላይ ዘር ሊዘራ ሲወጣ የግራር ዛፍ ብቻ የዘራ ይመስላል በተንጣለለው አስፋልት ግራና ቀኝ ተበትነው ሲመለከታቸው ከአብ ከወልድ ከመንፈስ ቅዱስ አንጥረኛው የቱ ነው እስኪሉ የኢትዮጵያ መልክዐ ምድር ማድነቅ የተለመደ ቢሆንም እኛም የአዋሽ አዋሳኝ የሆኑትን ሰንሰለታማ ኮረብቶች አሰፋፈር እያደነቅን ድፍን 4፡00 ሰዓት ሆኗል፡፡
     ግራና ቀኛችንን አልፎ አልፎ እንደ ግራር ዛፍ አጃበውን የሚጓጓዙት የከፍተኛ ኃይል የኤሌክትሪክ ተሸካሚ ማማዎችን ለምስራቅ የአገራችን ክፍል ብርሃን ላመዳፈም እየገሰገሱ ይመስላሉ፡፡
     አልፎ አልፎ ጣል ጣል ብለው የሚያገኛቸው ጎጆ ቤቶች እንኳንስ የእህል ማጠራቀሚያ ጎተራ ሥንቅ መቋጠሪያ አገልግሎት ከቤት ያላቸው አይመስሉም፡፡ በየቦታው ስፍራው በረሃውን ከማድመቅ ውጭ ከአዋሽ ሃይቅ ደረቱን ስትሮ ሲመለከቱት ለጥፋት እንጂ ለልማት አለመሆኑን ሲያዩ እጅግ ያዝናሉ ዛሬም ዓባይን በደፈርንበት ዘመን አልደፈር እጄን አልሰጥ ብሎ ይልቅስ ነዋሪውን ዕንባ እያራጨ ከማፈርቀል ባሻገር አዋጅ ማን ያውቃል አንድ ቀን እንደ ባንኩ የበረሃው የልምላሜ የብልጽግና ፈር ቀያሽ ይሆንና ታሪክ ይቀየር ነገር ይገለበጥና የተሰደደው የተፈናቀለው ሁሉ መልሶ ሰፋሪ ይሆናል፡፡ ማን ያውቃል? ማንም
     አውራ ጎዳናዎቹ መኪናዎቹ ሰው ብቻ አይደለም ወደ ማቅረብም አ.አ መኪናውም መኪና ጭኖ መኪና ነዳጅ ጭኖ ላይ ታች ሲል ይታዘባሉ የአ.አ ጎዳናዎች የመኪና ማቆሚያ ሥፍራዎች በመኪና ተጨናንቀው የገባው ሥፍራ ሳያገኝ ዛሬም መኪና ተጭኖ ይሄዱለታል፡፡ የሚገርመው ግን ያ ሁሉ መኪና አ.አበባን አጨናንቆ የዚያኑ ያህል በትራንስፖርት እጥረት መሰቃየቱን ሥናይ ግራ ያጋባል፡፡ ሲባል እንደሰማሁት ጁቡቲያውያን ወደ ኢትዮጵያ የሚገባውን የመኪና ብዛት ተመልክተው በመገረም ኢትዮጵያውያን ምግብ መብላት ትተው መኪና መብላት ጀምረዋል ወይ? አሉ የተባለውን በድጋሚ ይህ መንገድ እንደገና አስታወሰኝ፡፡
     አሁንም አዋሽን በስተቀኝ እያየን እንጓዛለን 4፡20 ሠዓት ሆኗል፡፡ በስተግራ የሰንሰለታማዋን ተራራ አብይ ቅርንጫፍ እየታከክን በአዋሽ ምድር ላይ ከኤሌክትሪክ ምሶሶ በስተቀር ለመሃላም ቢሆን ሌላ ዛፍ አይመለከቱም የአዋሽን ሙቀትና ከተማ ‹‹እንግዲህ ቻው ቻው›› በማለት ጥቂት ደቂቃዎች ይቀሩታል፡፡
     የአዋሽን ሐይቅ እየታከለ የሚሄደው አውራ ጎዳና በመሰራት ላይ ስለሆነ ተለዋጩን መንገድ መጠቀም የሰውነት እንቅስቃሴ ማድረግ የግድ ነው፡፡ ምንም ክረምት ቢሆን ቦታው አዋሽ ነውና የሰውነት ሙቀትም መጨመር ግዜ ይለዋል፡-
     አሁን አዋሽን በሩቅ ማየት የለም አዋሽ በርሶ ግራ እና ቀኝ እርሶ ደግሞ አዋሽን ለሁለት ከፍሎ መጓዝ (ሰንጥቆ) መጓዝ ግድ ይላል፡፡ አዋሽን ለሁለት ተባብረው የሰነጠቁትን የመኪና መንገድና የድሮ የባቡር ሐዲድ(የግመል ሃዲድ) ከሐይቁ ጋር ውሃ ልካቸውን ሲመለከቱ ዕፁብ ድንቅ እያሉ ሐይቁን ግድብ ያስገዛ ፈጣሪ እያመሰገነ መተሐራ ከመግባት በስተቀር አማራጭ የሉትም፤ሀይቁ ቢያገሳ፣ አሻፈረኝ እምቢኝ ቢል በአንበሳው ሐይቅ ከመዋጥ የዘለለ ዕጣ ፈንታ የሉትምና፡፡ መተሐራ 4፡40 ሠዓት አዲሱ ነገር የመተሐራ ትራፊኮች መግቢያና መውጫ ላይ ሁለት ጊዜ ያስቆማሉ አለመቀናጀታቸው ሲያሻቸው የበረሃ አበል ይቀበላሉ ተብለው ይታማሉ፡፡ ትርፍ ቢኖረው ባይኖረውም ቢሳሳቱም ባይሳሳቱም ተሳፋሪው መኪናው ቆሞ ትራፊክ ሲገባ ሆዳም፣ ከርሳም፣ የሚሉ ድምጾች ይሰማሉ እኛም እንሰማለን ትራፊኩም ይሰማል፡፡
     መተሐራ ካለፉ ሰንሰለታማው ተራራ እየተበጣጠሰ በስተቀኝ ያለው እየራቀ ሥፍራውን ለተንጣለለ ሜዳ ይለቃል፡፡ ቁጥቋጦውና ግራሩ ግን የት ድረስ እንደሚሄድ አይታወቅም ይከተሎታል፡፡ ከ12ቱ ሐዋርያት ቅ/ዮሐንስ ብቻ እስከ መስቀሉ እንደ ዘለቀ ከመሐል አገር የተነሱት ዕፅዋቶች ከግራር በስተቅ በመንገድ የሚከተልዎት የለም ከከተማ ሲወጡ ይክድዋታል፡፡ ግራር ሆይ ብፅዕ ነህ ባህር ዛፍ ከከተማ ስርቅ ትከዳኛለህ፡፡
     6፡10 ሠዓት አዋሽ 7ኪሎ 3ኛው ትራፊክ 20 (ሃያ ብር) ተቀበለ፡፡ አዋሽ 7ኪሎ ሙቀቷ ከመጨመር በቀር ልማት አይታይበትም እንዲያውም በድንጋይ ካብ የታጠሩ ባዶ ስፍራዎች ይበዙበታል፡፡ ለመሃላ ከተማዋን ወጣ ብሎ የነዳጅ ማጠራቀሚያ ጋን የመሰለ ነገር የአይን ማረፊያ አለ፡፡
     ከጁቡቲ አዲስ አበባ የሚያስመጣው የባቡር ሃዲድ  ፍተሻውን ሳይደርስ ከምድር ከፍ ያለው ድልድይ ዛሬ የጦጣ መሸጋገሪያ ኖኗል፡፡ አዋሽ አርባን እያለፉ ሲጓዙ ከተማን የሚያስታውስዎት ሁሉት ህንጻዎች ከመንገድ በስተቀኝ ቆመው ያገኛሉ፡፡
     አስቀድመው መተሐራ ላይ የከዱትና የተለዩን ስንሰለታማ ተራራዎች በስተቀኙን እንደተማረከ የጠላት ወታደር እጃቸውን ወደ ላይ ይዘረጋሉ ምህረት ጥያቃ እንከተላችሁ፣ አብረን እንሂድ በማለት። በስተ ግራ ግን ለጥ ያለው ሜዳ ላይ ከበረሃው ባቡር (ከግመል) በስተቀር ሰንሰለተማው ተራራ ላይታይ ምሏል መሰል የለም፡፡ ጊዜ ታክሲ አይደለም ቆም አይጠብቅም 5፡25 ሠዓት ለመሐላ በረሃ ውስጥ ያገኘናቸው ምሶሶዎች የበረሃውን ግለት አልቻሉም መሰል በየቦታው ወድቀዋል በቦታቸው የአርማታ ምሶሶ ቆሟል ከወደቀበት ቀና ሳያደርገው፡፡
     ቦርዳዴን ወደ ቀኝ በመተው 5፡35 ሰዓት መሆኑን ስናውቅ ወደ አሰበ ተፈሪ አመራን፡፡ 316 ኪ.ሜ መጓዝ ግድ ይላል ከተራራ ግርጌ የምትገኘዋን አሰበ ተፈሪ ለማግኘት ምሳ ሠዓት ደመቅ ሸብረቅ ሽርጉድ ትላለች እንግዶቿን ለማስተናገድ ‹‹ጥሩነሽ ምግብ ቤት›› አንዱ ነው፡፡ ‹‹እንኳን ደህና መጣችሁ›› ብለው ይቀበላችኋል ምሳዎትን ይበላሉ፡ ቡና በጀበና እዚያው ይጠጣሉ፡ አዲስ አበባ ላይ ጉሊት ሽንኩርት፣ ጎመን፣ በቆሎ ሲሸጥ እዚያው ሆቴሎች በር ላይ ጫት እንደ ጎመን ይሸጣል፡፡ ፡ምሳ ሰዓት ተጠናቀቀ፡ አሰበ ተፈሪ ደህና ሰንብች 7፡20 ሠዓት አሰበን ሻገር ካሉ ለምለሚቷን ምስራቃዊ ክፍል እየጎበኙ ሞቀታማውን በተመጣጠነ አየር ያጣጥሙታል፡፡
     ኦሮሚያ ክልል ቱሉ አረዳ ላይ ሌላ ትራፊክ 4ኛ 20 ብር ወጪ ተደርጓል ኬላ መሻገሪያ፡፡ ደበሶ 8፡00 ሠዓት ።የትራፊኮችን ጉዳይ መንግስትም ህብረተሰብም አንድ ሊላቸዉ ይገባል፡ህዝብን ሊያገለግሉ እንጂ ሊበዘብዙ አይደለምና አደራ የተጣለባቸዉ። ለመሆኑ 300 እና 400 ኪ.ሜ. ከአዲስ አበባ ሳንርቅ እንዴት እንዲህ አይነት ተግባር ሲፈፀም መንግስት ዝም ይላል? ደሞዝ አይከፈላቸዉ ይሆን?
     …ሜዳው ጨርሰን ዳገት ወተን ወደ ሂረና ለመግባት ደግሞ ቁልቁለት መውረድ ግድ ይላል፡፡ (ጠሎ ወረዳ) ከአሰበ ተፈሪ ወጥተን የሐረማያ ዮኒቨርስቲን እንዳለፉ ከአራት ሠዓታት በላይ የሚፈጀውን ዳገታማ ስፍራ ዓይንዎትን እስኪደክምዎት ግራ ቀኙን መቃኘት ነፍስ ይማርካል መቸስ የዚህ መንገድ ልምላሜ ዋነኛው ምሥጢር አልፎ አልፎ የሚታየው የበቆሎ ተክልና ከጫት ተክል ያለፈ አይደለም፡፡
     ሂረና ፣ ገለምሶ፣ ካራሚሌ፣ ቆቦ፣ ሜታወረዳን እንዳጠናቀቅን ቁልቢ 10፡25 ሠዓት ደረስን ሙስሊሙም ክርስቲያኑም ቁልቢ ከተማ አፋፍ ላይ የሚገኝን ተአምረኛውን የቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን መኪናው ከፍና ዝቅታ ያሳልመዋል ከሩቅ ያለ የሚመስለው ቤተክርስቲያን እንደ እኔ ለቦታው እንግዳ ከሆኑ ገና ለገና እደርስበታለሁ ሲሉ ተራራውን በስተግራ እየታከኩ ያልፉት ጳንገጐ ይገባሉ፡፡

     ከቁልቢ (ቁልቢ በኦሮምኛ ሽንኩርት ማለት ነው) የአንድ ሰዓት መንገድ ከተጓዙ በኋላ የበረሃዋን ንግስት ድሬን በስተግራ በመተው ለሃያ ደቂቃ ከተጓዙ በኋላ የሐሮማያ ዩኒቨርስቲ ዋና ካምፓስ መቀመጫ የሆነውን አለማያን ያገኟታል ጉዞአችን በህዝብ ትራንስፖርት እንደመሆኑ መጠንና ወቅቱም ሐምሌ ስለነበር የሐሮማያ የሐረር የጅጅጋ ዮኒቨርስቲ ተማሪዎች ነበሩ የተጓዡች ቁጥርን አብላጫ የያዘውና አለማያ ላይ ለ30 ደቂቃ ያህል ቆመናል የጫኑትን ሻንጣዎች ቁሳቁሶች እስኪያወርዱ፡፡
     ከአሥር እና አስራ አምስት ደቂቃ ጉዞ በኋላ ምስራቅ ውስጥ በትክክል መድረስዎትን የምታበስራዋ አንዳንዴም የአረቡ ክፍለ ዓለም ውስጥ ነው ወይስ ቻይና ነው ያለሁት ብለው እስኪጠረጠሩ ድረስ ሰዎች በሥራ ላይ የሚያዩበትን ከተማ አወዳይን ያገኛሉ፡ ጊዜው ባይመሽና 12፡00 ሠዓት ባይሆን (ይቅርታ አወዳይ ላይ ጀንበር አትጠልቅም፡ ድካም ዝር አይልም፡ የሚዘጉ በሮች የሉም፡ ሁሉም ቀን ከሌሊት ለሥራ ይፋጠናል፡ አረንጓዴ ወርቃቸውን ወደተለያየ አቅጣጫ ለመላክ ይፋጠናሉ እንጂ፣) ጎራ ብዬ ባያት ቁጭ ብዬ ብታደማት ደስ ባለኝ ነበር እኔም ጎራ ሳልልባት እናንተንም ሳላስቃኝ ማለፌ እኔንም ቅር አሰኝቶኛል፡፡
12፡20 ሐረር የአምስት በሮች እመቤት ምሥራቃዊና ጥንታዊት ከተማ የብሔር ብሔረሰቦች መገኛ ሐረር፤
ሐረር ሲገቡ በየትኛውም አቅጣጫ ሲመጡ አምስቱም በሮች እንኳን ደህና መጡ እያሉ አቀባበል ያደርጉልዎታል፡፡ ሸዋ በር፣ ፈላና በር፣ ዱክ በር፣ኤረር በርና ሰንጋ በር ምሽት ላይ ቀዝቃዛ የምትለዋ የሐረር ከተማ ምንም አስቸጋሪ ነገር አይታይባትም ወደፈለጉት ለመጓዝ በጃጆች ሁሌ ንቁ ሁሌም ዝግጁዎች ናቸው፡፡ ታክሲዎችም እንዲሁ የምሥራቁ እመቤት ሐረር ሙስሊሙም ክርስቲያኑም በጋራ የሚኖሩበት ፍቅር የሆነች ከተማ ብትሆንም ጊዜ ያመጣውን ጊዜ እስኪፈታው እምነትን ሰበብ እያደረጉ የሚመጡ በሽታዎቸ (ግማቶች) አይታጡም በቤተክርስቲያን ላይ ድንጋይ መወርወር፣ አማራው ላይ መዛት፣ ጊሌ ይዞ ሰላማዊ ሰልፍ መውጣት፣ ፓሊስ ሳይቀር ከእምነት የፀዳ ተቋማዊ ግዴታን አለመወጣትና ለእምነት እያደሉ ፀጥታን ያለማስከበር መጠነኛ ድክመቶች አሉባልታ ይሁን እንጂ የሐረርን ፀጥታ ለማስከበረ መንግስት አይተኛም አያንቀላፋም ፈጣን እርምጃ ከድሬደዋ በሚመጡ ፌዴራል ፖሊስ ሁከታውን ብጥብጡን ዛቻና ማስፈራራቱን ድንጋይ ውርወራውን ፀጥ ረጭ ያደርገዋል፡፤

     አዲስ አበባ ሆነው በመገናኛ ብዙሐን ሐረር ሲነሳ ለማዳ ጅቦች፣ የጃጎል ግንብ፣ አምስቱ የሀረር በሮች፣ የሐረር ሰንጋ…..ወዘተ የሚዘነጉና የማይጎበኙ አይደሉም። ፈጣሪ ዕድሉን ከሰጠን ጊዜው ካደረሰን አብረን እንጎበኘዋለን፡፡ ሐረር ልትተኛ ነው እኔም ድካም ተጫጭኖኛል ሰላም እደሩ ሐረር ሥትነቃ እኔም በርትቼ ስነሳ አብረን የሐረርን ጓዳ ጎድጓዳ እንቃኛለን ሐምሌ 12 ቀን 2004 ዓ.ም ፡፡
     ንጋት ሐምሌ 13 ቀን 2004 ዓ.ም የሐረር ሌሊት ለንጋት ቦታውን በመልቀቅ 12፡30 ሰዓት ሆኗል፡፡ አየሩ መጠነኛ ቅዝቃሴ ይታይበታል፡፡ አገር ለማየት ቆርጦ የመጣ ብርድ ሙቀት ዝናብ ንፋስ ብሎ መተኛት አይጠበቅበትምና በጠዋት ተነስቻለሁ ጉዞ ከሸንኮር በእግር ወደ ሐረር እምበርርት በሐረር በር አድርገን ወደ ጨለንቆ አደባባይ፤ ከጨለንቆ አደባባይ ወደ ተለያየ አቅጣጫ መጓዝ ይቻላል አንደኛ መንገድ (ወደኤራር በር)፣ ወደ ሐረር በር፣ ወደ ሸዋ በር፣ ወደ ጀጎል በር፡ሰንጋ በር(ጅቦች ወደሚታዮበት) እዛው ጨለንቆ አደባባይ ላይ አሚር አብዱላሂ አዳራሽ (የቀድሞው የራስ መኮንን አዳራሽ) ይገኛል:: ለሁሉም ጊዜ አለውና ታሪክ በታሪክ ተደምስሷል በአንደኛ መንገድ ሲጓዙ እንዲሁ የታሪክ ሹም ሽረት ጥንት ጁግለን ይባል የነበረው ጁገል ሆስፒታል በመባል ተቀይሮ ያገኙታል ሙዝየሞች የባህልና ቱሪዝም ቢሮዎች የሐረሪ ብሔረሰብ ባህላዊ ሙዝየም ሁለት መስጅዶች… ያገኛሉ፡፡ እዚሁ ወደ ጨለንቆ አዳባባይ መግቢያ ላይ ሁላችን በተለያዩ መገናኛ ሚዲያ የምናየው የሐረር በር አንድ ነገር ያመላክተናል፡፡ ‹‹ሐረር የሰላም የመቻቻልና የትብብር ከተማ›› ሐረር ጃጎል የዓለም ቅርስና የመጨረሻው የሐረር ንጉስ ፎቶ ግራፍ የአሚር አብዱላሂ ይታያል፡፡ 

   በአካባቢው ሲንቀሳቀሱ ይህቺ በ72 ነገስታት ሥትመራ ወይም ስትገዛ የኖረች ጥንታዊት ሀገር ባላት የውስጥ ለውስጥ ሽኩቻ እውን የመቻቻል አገር ናት? ብለው ጥያቄ ሊያነሱ ግድ ይልዎታል፡፡ የዛሬን አያርግና የፍቅር፡ የመቻቻል ከተማ ነበረች ነገም ተስፋ አለን ጠንካራ ህዝብ ነዉና ህዝቡ ታሪኩን ቀይሮ እንደገና ያመጣዋል።እንግዳ ኖትና አቦ ይመችዎት ወቅቱ ስለሆነ ዛሬ በሚዛን ቢሸጥም ድካሙን ያስረሳልና ማንጎ ይብሉ ተጋብዘዋል፡፡
ድሬ የምሥራቅ የበረሃዋ ንግስት የምትገኘው በ90 28.1 እና 90 49.1 በስተሰሜን ላቲቲውድ በ410 38.1 በስተምስራቅ እና በ420 19.1 ምስራቅ ሎንጊትውድ መካከል ሲሆን 505 ኪ.ሜ ከአ.አ ርቀት ላይ የምትገኝና በ1288 ኪ.ሜ ካሬ ላይ የሠፈረች፡ ደረቅና ሞቃታማ ስትሆን በ31.40Cከፍተኛ እና በ18.20C ዝቅተኛ መካከል ትገኛለች ዓመታዊ የዝናብ መጠኗ 604 ሚሊ.ሜትር እንደሆነ ይነገራል፡፡ ከባህር ጠለል በላይ ከ960-2500 ሜትር መካከል ያለች ውብ ከተማ ናት። ህዝቦቿ ተግባቢና የሥራ ፍቅር ያላቸው እንግዳ ለመቀበል የማይሰለቻቸውና በብዙ ብሔር ብሔረሰብ ስብጥርና ዕምነት ደምቃ ያለች በብዛት የውጭ ዜግነት ያላቸው ሰፈርውባት ያለች ከተማ ናት፡፡
 አስራ ስምንት ኪሎ ሜትር ወደ ታች ቁልቁል መውረድ ይጠበቅብዎታል ድሬ ከባህር ጠለል 960-2500 ሜትር የምትገኝ ሲሆን በኢትዮጵያው ውስጥ በፌዴራል ከሚመሩ ሁሉት ከተሞች ከአ.አበባ በመቀጠል የምትገኝ ሞቃታማ፣ደማቅ፣ ግርግር ቀን ከሌሊት የማይለያት፣ ሃያ አራት ሰዓት በስራ ላይ የተጠመደች፡ የተለያዩ የብሔር ብሔረሰቦች መኖሪያ፣ የእንዱስትሪ መገኛ፡ የሸቀጣ ሸቀጥ መደብር፣ የዕውቀት ምንጭ፣ የቆንጆዎች ምድር፣ መቃሚያ ቦታ፣ መጨፈሪያ መድረክ፡ መገበያያ መደብር …..በቃ ድሬን ቃላት አይገልጻትም፣ ዓይን አይቶ አይጠግባትም፣ ቢኖሩባት ቢኖሩባት አትሰለችም ሲገቡ ተንደርድረው ደስ እያለዎት ወደ ከተማዋ ይገባሉ መውጣት ምጥ ነው፣ እጅግ ይጨንቃል፡፡ ድሬ መጥተው የት አርፋለሁ ብለው አይጨነቁም እርሶ ተዘጋጅተው ይምጡ እንጂ የፀዱ ደረጃቸውን የጠበቁ ሆቴሎቻቸው በራቸውን ከፍተው “እንኳን ደህና መጡ” ብለው ይቀበልዎታል፡፡ በአንዱ ሆቴል የእረፍት ጊዜውን አድርገው ገላዎትን ከተለቃለቁ በኋላ ወጣ ይበሉ የትራንስፖርት ችግር የለም አያስቡ ባጃጅ ሞልቷል ሁለት ብር ከፍለው መንሸራሸር ነው አሥር ብርማ ከከፈሉ የሚፈልጉት ቦታ ይደርሳሉ፤ ብቻ እርሶ የት መሄድ እንደሚፈልጉ፣ ምን ማየት እንደናፈቁ ዝግጁ ይሁኑ እንጂ ለዛሬ ብቻ መሄድ እንጂ ወደየት መሄድ እንዳለቦት ግራ ከገባዎት መንገድዎን ለባጃጅ ሹፌር ይስጡ እርሱ ያስጎበኝዎታል፡፡
     ደቻቱ ሠፈር፣ መጋላ ሠፈር፣ ኮኔል ድልድይ፣ ከዚራ፣ ሳብያን፣ ነምበርዋን፣ ታይዋ፣ ፖሊስ ሜዳ፣ ለገሃሬ፣  አሸዋ፣ ወዘተ… የሚጎበኙ ናቸው፡፡

ጦማሩን ስለጎበኙ አመሰግናለሁ!

መልካም ነገርን ለሌሎች ማጋራት ባህላችን እናድርግ፤ ላልደረሰዉ በማጋራት ድርሻችንን እንወጣ፡፡

ትቶ እና ችሎ

  ትቶ እና ችሎ ብጹእ ወቅዱስ አቡነ መርቆርዮስ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ በደረሰ ረታ ብጹዕነታቸው ለሶስት አሥርት አመታት እኛ በማናውቀው እግዚአብሔር በሚያውቀው በብዙ መከራ በብዙ ፈተና ውስጥ ነው ያሳለፉት። ...