ማክሰኞ 25 ሜይ 2021

የጌታ ቃል ትዝ አለው

 " የጌታ ቃል ትዝ አለው " የሉቃስ ወንጌል 22፥61

በደረሰ ረታ

ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስን ክርስቶስን " ሌሎች ቢክዱህ እንኳን እኔ አልክድህም " ብሎት ነበረና ጌታም " ዶሮ ሳይጮህ ሶስት ጊዜ ትክደኛለህ " አለው።

ጊዜው ሲደርስ ጌታን ያዙት ወደ ሊቀካህናቱ ቤትም ወሰዱት

• ጴጥሮስም ርቆ ይከተለው ነበር።
• ጴጥሮስ በመካከላቸው ተቀመጠ።
• ይህ ደግሞ ከእርሱ ጋር ነበረ አለች።
• አንቺ ሴት፥ አላውቀውም ብሎ ካደ።
• አንተ ደግሞ ከእነርሱ ወገን ነህ፡ አለው።
• ጴጥሮስ ግን፡— አንተ ሰው፥ እኔ አይደለሁም፡ አለ።
• ሌላው አስረግጦ፡— እርሱ የገሊላ ሰው ነውና በእውነት ይህ ደግሞ ከእርሱ ጋር ነበረ፡ አለ።
• ጴጥሮስ ግን፡— አንተ ሰው፥ የምትለውን አላውቅም፡ አለ።
• ያን ጊዜም ገና ሲናገር ዶሮ ጮኸ።
• ጌታም ዘወር ብሎ ጴጥሮስን ተመለከተው፤
• ጴጥሮስም፡— ዛሬ ዶሮ ሳይጮኽ ሦስት ጊዜ ትክደኛለህ እንዳለው የጌታ ቃል ትዝ አለው።
• ጴጥሮስም ወደ ውጭ ወጥቶ ምርር ብሎ አለቀሰ።
የቅዱስ ጴጥሮስ አቋም ከችኩልነቱ የተነሳ ወላዋይ ይመስላል፤ ችኩልነቱ እና ባለማገናዘብ የሚመልሳቸው መልስ ከፍቅር የመነጨ ነው።

መጠራጠር እና ክህደቱ የተፈጠረው ግን በፍርሃት፣ ከነበረበት ስፍራ፣ ከወቅታዊ ሁኔታው የተነሳ ነበር።

1. ጌታን ሲይዙት ርቆት መከተሉ
2. ሲበርደው እሳት ለመሞቅ ጌታን ከያዙት ወገን ከመካከላቸው መቀመጡ
3. የጌታን ወደዚህ ዓለም የመምጣት ዓላማ በአግባቡ ሳይለይ የልብ መሻቱ
እነዚህ ተደማምረው ቅዱስ ጴጥሮስ መጀመሪያ ጌታን አላውቀው፣ ቀጥሎ ራሱን ክዶ አይደለሁም፣ በመጨረሻም ጌታን ሊክደው እና አላውቀውም እንዲል አድርጎታል።

ከዘረኛ ጋር ስንውል ዘረኛ፣ ከነፍሰ ገዳይ ጋር ስንውል ነፍሰ ገዳይ፣ ከመንፈሳዊ ጋር ስንውል መንፈሳዊ እንሆናለን። ወፍጮ ቤት የዋለ አይደለም የገባ ሰው ዱቄት ሳይነካው አይወጣምና።

" ቃሌ ከሚያልፍ ሰማይና ምድር ቢያልፍ ይቀላል " ያለ አምላካችን ያለው ቃል ተፈጸመ። ዶሮ ሳይጮኽ ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታን ሶስቴ ካደው።

ጌታም ዘወር ብሎ ጴጥሮስን ተመለከተው።

ጴጥሮስም የጌታ ቃል ትዝ አለው፦ ።" ዶሮ ሳይጮኽ ሶስት ጊዜ ትክደኛለህ "

ጴጥሮስም ወደ ውጪ ወጥቶ (ከወንበዴዎቹ ተለይቶ፣ ጌታን ሊገሉት ከሚፈልጉት አጠገብ ርቆ፣ እሳት ከሚሞቅበት ቦታ ተነስቶ ) ምርር ብሎ አለቀሰ።

የቅዱስ ጴጥሮስ መራር ለቅሶ የንሰሐ ለቅሶ ነበረ።

እኛስ?

ከቅዱስ ጴጥሮስ የሕይወት ተሞክሮ ምን ተማርን?

ጌታን በቅርበት ነው የምንከተለው ወይንስ በርቀት?

ውሎአችን ከነማን ጋር ነው?

አውቀን አምነን ነው እየተከተልነው ያለነው፣ በስሜት ነው፣ ከቤተሰቦቻችን ስለወረስን ነው፣ ወይንስ እንዴት ነው?

አሁናዊ ማንነታችን ምን ይመስላል?

ብዙዎቻችን የቅዱስ ጴጦሮስ አይነት ሕይወት ያለን ይመስለኛል፤ መመላለስ ነገር ግን መራር የንሰሐ ሕይወት የሌለን። እንደዛ ከሆነ እንመለስ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የሰማነው የጌታ ቃል ትዝ ይበለን።

አካሄዳችንን እናቅና ( ቤተክርስቲያን መሄድ የምንፈራ፣ ማስቀደስ የምንጠላ፣ መጾም የማንችል፣ የጸሎት ሕይወት የሌለን፣ ማመን የማይታይብን፣ ውሎና አዳራችን ከማይመስሉን ጋር የሆነ፣ ከማያምኑት ጋር ወዳጅነት የመሰረትን ) እንመለስ።

ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታውን እንዲክድ ያደረገው፦
መፍራቱ፣
ከማያምኑት ጋር መቀመጡ፣
ጽኑ እምነት አለመኖሩ፣
ወዘተ ናቸው ለመካድ እና መሪር እንባን እንዲያነባ ያደረጉት።

ስለዚህ እኛም ፍርሃትን የሚያርቅ ጽኑ ፍቅር እንዲኖረን ጌታን ቀርበን እንወቀው። ከማያምኑት ጋር ውሎአችንን አናድርግ፣ ( ከላም ጋር የዋለች ጊደር ምን ተምራ ትመጣለች እንዲባል) ውሎአችንን እናስተካክል።

አንዳንዶቻችን በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አዳኝነት፣ አምላክነት፣ አማላጅ አለመሆኑን፣ ማመናችንን፣ ክርስቲያን መሆናችንን ለመደበቅ እንጥራለን፣ የአንገት ማኅተማችንን እንደብቃለን፣ መጾማችንን ሳይቀር እንዋሻለን። ( የዘፈን ዳርዳሩ ... እንደሚባለው እንዳይሆን እፈራለሁ። )

በጌታ ቃል ራሳችንን እንመልከት። አንዳንዶቻችን ታሪክ ቀመስ እንሆናለን በልጅነቴ ሰንበት ተማሪ ነበርኩ፣ ዘማሪ ነበርኩ፣ ዲያቆን ነበርኩ፣ ቆራቢ ነበርኩ፣ መምህር/ አባ እገሌን አውቀዋለሁ፣ የቄስ ልጅ ነኝ ወዘተ እንላለን። አሁን የት ነን? እንደ ቅዱስ ጴጥሮስ ራሳችንን እንይ። እሳት ሐጢያትን እየሞቅን፣ ጌታን አሳልፈው ከሰጡ፣ ከሸጡ፣ ከገደሉ ጋር ነን? ወይስ ቃሉ ከሚነገርበት አትሮኑስ ስር ነን?

በጌታ ቃል ራሳችንን ካየነው ምንም ጥያቄ የለውም በድለናል። ( ሁሉ በደለ እንዲል የአምላካችን ቃል። ) ክደናል የሚያስብል ደረጃ ላይ ነን። እንደ ቅዱስ ጴጥሮስ ፈጥኖ የሚመለስ ልብ፣ የሚጸጸት ልብ፣ ወደ ንሰሐ የሚመለስ ልብ ካለን ንሰሐ እንግባ፣ አምርረን እናልቅስ፣ ያሳለፍነው ዘመን ይበቃናል እንበል።

የቀማን መልሰን፣ የበደልን ክሰን ወደ ንሰሐ ሕይወት እንገስግስ።

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምህረት ዐይኑ ይመልከተን።

አሜን።
ይቆየን።

መልካም የሕማማት ሳምንት ይሁንላችሁ።
❤❤######################❤❤

የእለት ተለት ጽሑፎቼን ለመከታተል ከዚህ በታች ባሉት ሁሉ እገኛለሁና ይከታተሉኝ። ከተመቸዎት ለሌሎች ያጋሩት።
My Facebook page link (በፌስቡክ ገጽ እንገናኝ)

https://www.facebook.com/deresse2020/

Main facebook account (ዋናው የፌስ ቡክ ገጼ ይቀላቀሉት)

https://www.facebook.com/DeresseReta

Follow me through telegeram (በቴሌግራም ሊከታተሉኝ ከፈቀዱ) ሁሉም ምልከታዬን የማጋራባቸው ማህበራዊ ድረ ገጾች ናቸው።

https://t.me/deressereta

ከአሥር አመት በላይ ከ50ሺ በላይ አንባቢዎች ያሉት መጦመሪያም አለ።

www.deressereta.blogspot.com

https://anchor.fm/deresse-reta/episodes/ep-ev5j5o

ሥራን አውቆ መሥራት

 ሥራን አውቆ መስራት


አንድ ሰው በቅርስ ጥበቃ ተቋም በጥበቃ አገልግሎት ተቀጥሮ እየሰራ ሳለ አንድ ቀን በቅርስ ማዕከሉ ውስጥ ሲንቀሳቀስ ብዙ ዘመናትን (1500ዓመታት) ያስቆጠረ ብርጭቆ ሰበረ።

ተቆጣጣሪው በጣም ተበሳጩ ተቆጡ ጥበቃው ምን እንደሚያበሳጫቸው ግራ በመጋባት ጠየቀ።

ኃላፊው እንዴ ብርጭቆኮ ነው የሰበርከው ብርጭቆው ደግሞ 1500 ዓመት ያስቆጠረ ትልቅ ቅርስ ነው አሉት።
ጥበቃውም ግራ ከመጋባት ውስጥ ወጥቶ ዘና በማለት እንደውም እንዲህ ያረጀ ብርጭቆ እዚህ ምን ይሰራል። እንደውም በአዲስ እተካዋለሁ አይጨነቁ በማለት ሊያረጋጋቸው ሞከረ።

ሰውየውም እጅግ ተበሳጩ። ቁጣቸው ጨመረ።

የሥራ ኃላፊውን ያስቆጣቸው ጥበቃውን ያረጋጋው ጉዳይ ምንድነው?

ጥበቃው ቅርስን ያህል ነገረ ሰብሮ እንዲህ ያረጋጋው ምን አይነት የጤና ሁኔታ ላይ ቢሆን ነው? ትሉ ይሆናል።

እስኪ ስለ እነዚህ ሁለት ሰወች በማውራት ጊዜ ከምናባክን ስለ እያንዳንዳችን እናስብ።

እኛ ምን አይነት ሰወች ነን?

ቁጡ?

ግዴለሽ?

ዝምተኛ?

እስኪ ምን ያስቆጣናል? ምንስ ዝም ያስብለናል? ግዴለሽ የሚያስደርገንስ ምንድን ነው?

ግድየለሽነት የጤናማነት ምልክት አይሆንም ሲወድቅም፣ ሲሰበርም፣ ሲጠፋም ግዴለሽ ከሆንን ጥቅሙ አልገባንም አልያም ችግር አለ።

አንዳንዶች ምናልባት ተስፋ ከመቁረጥ ግድየለሽ ሊሆኑ ይችላሉ። የፈለጉትን ከማጣት፣ በጣም የተማመኑበት ነገር ሲከዳቸው፣ ቃል ሲታጠፍባቸው፣ አምነው ሲከዱ ወዘተ ለግድየለሽነት ምንጭ ሊሆን ይችላል።

ምን ያስቆጣናል?

በተለምዶ እውነተኛ ሰው እውነቱን በምሬት ሲናገር ቁጡ ይባላል። ሌሎች ደግሞ " የሌባ አይነደረቅ መልሶ ልብ አድርቅ " እንዲሉ ጥፋታቸውን ለመደበቅ ይቆጣሉ። ጥቂቶች ደግሞ የግንባራቸው ሥጋ ቅርጽ (መሸብሸብ/ ኮስተር እንደ ማለት) ቁጡ ያስብላቸዋል።

እኔን መሰሎች ደግሞ ስራ ሲበላሽ እና ያለ አግባብ ሲሰራ በተለይ እንደ ቅርስ ጥበቃው ሰራተኛ ለደሞዝ ብቻ ገብተው በሚወጡ፤ ነገር ግን የሚሰሩት ሥራ ዓላማው ካልገባቸው ሥራቸውን በአግባቡ ካልተወጡት ያስቆጣል።

ዝምተኞችን ስንመለከት በአጭሩ ለመፈረጅ ቢያስቸግርም ሥራው ቢሰራ ባይሰራ፣ ቢበላሽ ባይበላሽ ምንም የማይመስላቸው "ያው በገሌ ነው" ብለው እንደ ድመት የሚያስቡ። ተናግሬ ሰው ከሚቀየመኝ ዝም ብዬ ተመሳስዬ አልኖርም ብለው የሚያስቡ ናቸው። እንደዚህ አይነት ለኔ ልዝብ ነው።

ለነገሩ ሁሉም ነገር ስለተናገሩት፣ ዝም ስላሉት አይፈታም አንዳንዴ ሲናገሩ የሚፈታ እንዳለ ሁሉ ዝም ሲሉት የሚፈታም አለና።

እኛ እንደ ተቋም እንደ አገር የተሰጠንን ሥራ የምንሰራው እንዴት ነው? እንደ ጥበቃው ሳይገባን ነው ወይስ እንደ ቅርስ ጥበቃ መስሪያ ቤት ኃላፊ በያገባኛል፣ በኔነት፣ ሥራው ገብቶን ነው?

ከትንሣኤ ማግስት

 የትንሣኤ ማግስት ቀናት

በደረሰ ረታ

ሰኞ ፦ ማዕዶት መሻገር ማለፍ በሲኦል ወደ ገነት በጨለማ ወደ ብርሃን የመሻገራችን ነፍሳት ከሲኦል የመውጣታቸው መታሰቢያ ነው። ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ የመምጣቱ አላማ ይኸው ነውና።

በባህሪው ሞት በመንግሥቱ ሽረት የሌለበት አምላክ የሞተው ለዚህ ነውና።

በዚህ በትንሣኤ ማግሥት ሰኞ በዚህ ዕለት በፋሲካችን በክርስቶስ ትንሣኤ ከድቅድቅ ጨለማ ወደ ሚደነቅ ብርሃን፣ ከሞት ወደ ሕይወት፣ ከሲኦል ወደ ገነት፣ ከሃሳር ወደ ክብር መሻገራችንን እናስባለን፡፡


ማግሰኞ፦ ማግስተ ሰኞ ቶማስ ሲባል ቶማስ ጌታን አይቶ ማመኑ ጌታዬ አምላኬ ብሎ መመሥከሩ

እንደምናውቀው ቶማስ በጌታችንም ሆነ በእመቤታችን ትንሣኤ ወቅት በአገልግሎት ምክንያት አልነበረም ወንድሞቹ ሐዋርያት ነበሩ ስለ ትንሣኤዋ የነገሩት ነገር ግን አላመነም። በጌታ ትንሣኤ ጌታን ቢጠራጠር እርሱ ስለመሆኑ ጌታ ማረጋገጫ የሰጠው ሲሰቀል የተወጋ ጎኑን እንዲያይ ነበረ። እጁን ወደ ተቸነከረበት ቢሰደው ጣቶቹ እሳት እንዳየ ጎማ ተኮማተሩበት። አምኖም መሰከረ። ዮሐ. 20፡27-29

በዚህ እለት ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ አለማመናችንን እንዲረዳ፣ አምነንም እንድንመሰክር እንዲረዳን እናስበዋለን።

ረቡዕ፦ አልአዛር ሲባል ጌታ አልአዛርን ከሞት እንዳስነሳው እናስባለን።

አልአዛርን ከሞት እንዳስነሳው ስናስብ ክርስቶስ የሞትን ስልጣን የሻረ የሕይወት ራስ፤ የመቃብርን ሥርዓት ያጠፋ ትንሣኤ፡ ድልም ያረገ ዘለአለማዊ ንጉሥ መሆኑን እንመሰክራለን፡፡

በዚህ ወቅት ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያውያን በብዙ ጭንቅና መከራ፣ በሞትና በሕይወት መካከል ስለምንገኝ፣ ኢትዮጵያዊ ማንነታችን እንደ ጉም በንኖ እየጠፋ ስለሆነ ጌታችን ለእኛም ትንሣኤ ልቡና እንዲያድለን እንለምነዋለን።


ሐሙስ፦ አዳም ሐሙስ ይባላል ለአዳም የሰጠው ተስፋና የተገባለት ኪዳን እንደተፈጸመ አዳምና ልጆቹ ነጻ እንደወጣን ይታሰብበታል።

በበለስ ምክንያት ከገነት እንደወጡ ሁሉ የአለም መድኀኒት ጌታችን ለአለመ ድህነት ከወጣንበት ገነት እንመለስ ዘንድ ከአምስት ቀን ተኩል በኋላ ለአዳም በገባው ቃል መሠረት አድኖናልና።

አርብ ፦ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ይባላል ቤተ ክርስቲያን በክርስቶስ ሞትና ትንሳኤ መመስረቷ ይሰበካል።

በዕለት አርብ ቤተክርስቲያን በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ስለመመስረቷ ይሰበካል፡፡ ክርስቶስ ስለ እርሱ ራሱን አሳልፎ ሰጥቶ ቤዛ ሆኖ በደሙ አንጽቶ በትንሣኤው ድል ሰጥቶ ቤተክርስቲያንን እንዳከበራት ይነገራል፡፡

ቤተክርስቲያን ስንል ሕንፃውን ሳይሆን አማኞችን ነው፤ ክርስቶስ ለሕንፃ አልሞተምና፡፡

ቅዳሜ፦ ቅዱሳት አንስት ሲባል የጌታን አካል ሽቱ ለመቀባት ጨለማ አቋርጠው ወደ መቃብር መምጣታቸው፣ ትንሳኤውን ቀድመው ማየታቸው ይሰበክባታል።

እሁድ፦ ዳግም ትንሳኤ ሲባል ለደቀ መዛሙርቱ ለ3ተኛ ጊዜ መገለጡንና ሰላምን መስበኩ ይሰበካል።

ማጠቃለያ

እንደ ክርስቲያን በአብይ ጾም ወቅት የምናሳየው መንፈሳዊ ማንነት ፍሬ የሚያፈራበት ነው። ከአብይ ጾም በኋላ ከትንሣኤው ማግሥት በቤተክርስቲያን ምሥጢር ብዙ መታሰቢያ ነገሮች አሉት አንዱ ሐምሳው ቀናት ከጾም የምንከለከልበትና አርብ እና ረቡዕ ሳይቀር የፍስክ ምግቦችን የምንመገብበት ነው።

ከዚህ በቀረው ከላይ የዘረዘርናቸው ምሥጢራትን ቤተክርስቲያን ለመጀመሪያው ሳምንት ስያሜ ሰጥታ አመሥጥራ ታስተምራለች።

እኔም ከብዙ በጥቂቱ፣ ከረጅም በአጭሩ፣ አምልቼ አስፍቼ ሳይሆን በማይም አቅሜ አቅርቤያለሁ።

እንደ ክርስትናችን የሁለት ወር መንፈሳዊ ተግባራችን የሚያፈራበት ነው። ጾም፣ ጸሎታችን፣ ስግደት፣ ምጽዋታችን፣ መውደቅ መነሳታችን ያበቃለት ሳይሆን በእምነት የዘራነው መንፈሳዊ ዘር አብቦ የሚያፈራበት ነው።

ነገር ግን አብዛኞቻችን መንፈሳዊነት ያለቀ ሥጋዊነት የተጀመረ እናስመስለዋለን። ፋሲካ ሲሆን ሥጋዊነት እንዲሰለጥንብን አይደለም።

ጾም እና ንሰሐ ገብቶ ቀኖና መቀበል ቢቀር ሌሎች ተግባራት አይቀሩም። ስለዚህ የትንሣኤ ማግሥት የልቡና ትንሣኤ እንዲሆንልን እመኛለሁ።

ይቆየን።
አሜን።

ሐሙስ 29 ኤፕሪል 2021

ጸሎተ ሐሙስ

 ምሴተ ሐሙስ / ጸሎተ ሐሙስ


" እኔ ለእናንተ እንዳደረግሁ እናንተ ደግሞ ታደርጉ ዘንድ ምሳሌ ሰጥቻችኋለሁና። "

የዮሐንስ ወንጌል 13፥1-15 ፣ ማቴዎስ 26፥1-
(በደረሰ ረታ)

በሕማማት ሳምንት በዕለተ ሐሙስ ጌታ ደቀመዛሙርቱን እግር ያጠበበት ነው፤ ሌሎቹ ፈቅደው ወደው ሲታጠቡ ቅዱስ ጴጥሮስ አታጥበኝም ብሎ አስቸግሮት ነበረ። ምሥጢሩን እና ምሳሌውን አላስተዋለም ነበረና።

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አስተምሮ መክሮ ገስጾ መልሶታል። እርሱም ለመመለስ ልቡ ቅርብ ነበረና እሺ በጄ ብሎ ታጥቧል።

ይህ ዕለት የትህትና ዕለት ነው። ጌታ እግራቸውን አጥቦ ሲጨርስ እኔ መምህር ስሆን ዝቅ ብዬ የተማሪዎቼን / የደቀመዛሙርቴን እግር ካጠብኩ እናንተም እንዲሁ አድርጉ ብሎ አስተማራቸው።

ቅዱስ ያሬድም ስለዚች ዕለት ይለናል፦

“ሐዋርያቲሁ ከበበ
እግረ አርዳኢሁ ሐጸበ
ኮኖሙ አበ ወእመ
ወመሀሮሙ ጥበበ”

ሲተረጎም፦ ሐዋርያቱን ሰበሰበ፤ የደቀ መዛሙርቱንም እግር አጠበ፤ እንደ አባትና እናት ኾናቸው የትሕትና ጥበብን አስተማራቸው። ማለት ነው።

ከዚህ ዕለት ብዙ የምንማረው ነገር ቢኖርም አንዱና ዋነኛው የጌታን ትሕትና ነው። ጌታ ሲሆን እግር አጠበ። በተግባር ያሳየ የትህትና መምህር ነው።

ቅድስት የሆነች ኦርቶዶክሳዊት ተዋህዶ ቤተክርስቲያናችን በየአመቱ ይህን ምሥጢር በጸሎተ ሐሙስ ታከናውናለች። ከቅዱስ ፓትሪያርኩ ጀምሮ ዐዕይንተ እግዚአብሔር ካህናት በእርሱ ምሳሌ የምዕመኑን እግር ወገባቸውን ታጥቀው ዝቅ ብለው ያጥባሉ። ምሳሌ ነው።

መምህረ ትህትና ኢየሱስ ክርስቶስን ቅዱስ ጴጥሮስ እግሩን አልታጠብም ብሎ እንዳስቸገረ እንዲሁ መምህራንን ቅድስ ቤተክርስቲያንን አስተምሮቷን አንቀበልም የሚሉ ለሥርአቷ የማይገዙ ደንዳና ልብ ያላቸው አሉ። እንደ ቅዱስ ጴጥሮስ ያሉ ትምህርት ሲያገኙ የሚመለሱ አሉ። እነዚህን አስተምራ ትመልሳለች እንደ ይሁዳ ያሉትን ልበ ደንዳኖች አውግዛ ትለያለች።

እኛም አስተምህሮቷ ገብቶን እና የምሥጢሩ በረከት ተገብቶ ይድረሰን።

የሰው ልጅ ክቡር እና እኩል ቢሆንም ቅሉ። ካለንበት እንዳለንበት ደረጃ በትህትና ዝቅ ብለን ልንታዘዝ፣ ልናገለግል ይገባናል።

ትሕትና የመንግሥተ ሰማያት መወጣጫ መሠላል ናትና ትሕትናን ገንዘብ እናድርግ። እርፍ የጨበጠ መሰላል ላይ የወጣ ከመጨረሻው እስኪደርስ ድረስ ወደኋላ አይልምና ዘወትር ትሕትና አይለየን።

ይሕ ቀን ሌላ ተግባር ተከናውኖበታል። በአልአዛር እና ኒቆዲሞስ ቤት ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ለደቀመዛሙርቱ ይህ ነገ የሚፈሰው ደሜ፣ የሚቆረሰው ሥጋዬ ነው ጠጡ ፥ብሎ ሰጣቸው። ምሥጢረ ቁርባንን የጀመረበት ዕለትም ነው። የአዲስ ኪዳን ተግባር የተጀመረበት ዕለት ነው።

ሥጋውን ደሙን ከመቀበላቸው አስቀድሞ በእግራቸው በኩል ሕሊናቸውን፣ ሰውነታቸውን፣ ነፍሳቸውን አጽድቶ አጥቦ ለቁርባን አቀረባቸው።

እኛም ርስት መንግሥተ ሰማያትን የሚያወርሰውን ሥጋውንና ደሙን እንድመገብ ንሰሐ ገብተን ጸድተን እና ነጽተን እንቀረብ፤ ለዚህም እግዚአብሔር ይርዳን።

አምላካችን ዐይን ያላየውን፣ ጆሮ ያልሰማውን፣ በሰው ልቡና ያልታሰበውን፣ እግዚአብሔር ለሚወዳቸው ያዘጋጀውን ርስት መንግስተ ሰማያትን ያውርሰን።

ይቆየን።
አሜን።

ሰኞ 26 ኤፕሪል 2021

ሰሙነ ሕማማት ሰኞ ( መርገመ በለስ)

 ሰሙነ ሕማማት ሰኞ ( መርገመ በለስ)

ማቴዎስ 21 : 10 - 19

ከእለተ ሆሳእና ማግስት ኢየሱስ ክርስቶስ ተራበ ይለናል። ፍጹም ሰው መሆኑን ለማጠየቅ ተራበ ተብሎ ተጻፈ። ስለተራበም ረሃቡን ማስታገሻ ምግብ ፈለገ። አንዲት በለስ ተመልክቶ ወደርሷ አመራ። ከቅጠልም ብቻ በቀር ምንም አላገኘባትምና " ለዘለዓለሙ ፍሬ አይገኝብሽ አላት " በሌሊትም ያንን ጊዜውን ደረቀች።

ወንጌላዊው ማቴዎስ በሰሙነ ሕማማት ሰኞ ስለተፈጸመው ተግባር ሲጽፍ ጌታ የረገማት በለስ ወዲያው እንደ ደረቀች የጌታ ደቀመዛሙርትም ይህን አይተው እንደተደነቁ ይነግረናል።

በሌሊቱ የተረገመችው በለመለመችና ፍሬ በምታፈራበት ወቅት ነበረ። ይህን ሲያስረግጥልን ቅዱስ ማርቆስ በምዕራፍ 11 ቁጥር 13 ላይ " የበለስ ወራት አልነበረምና " ይለዋል።

ታዲያ ቅዱስ ማርቆስ የበለስ ወራት እንዳልሆነ ካረጋገጠልን ጌታ ስለምን ከበለሲቱ ፍሬ ፈለገ? የሚል ጥያቄ ያስነሳል።

አባቶቻችን እንዲህ ብለው ይኸን ጥያቄ ይመልሱታል። ከበለሷ ፍሬ መፈለጉ፥
• አንዳንድ በኩረ በለስ አይታጣም ብሎ ነው ይላሉ፣
• አንድም አላዋቂ ሥጋን እንደ ተዋሃደ ለማጠየቅ ነው ይሉናል፣
• አንድም አውቃለሁ ብሎ ሥራውን አይተውምና በዚያው ሥራውን ለመሥራት ነው።
ቅዱስ ማቴዎስ እና ቅዱስ ማርቆስ የጻፉለት በለስ ምሳሌ አላት። በበለስ የተመሰለው:-
፩. እስራል ናት

በበለሷ በረሃብ ሰአት የሚባላ መልካም ፍሬ ሊያገኝባት በወደደ እና በፈቀደ ጊዜ እንዳላገኘባት ሁሉ በእስራኤልም እንዲሁ ሃይማኖት፣ ምግባር ባገኝባቸው ብሎ ሄደ። አንዳች አላገኘባቸውም እስራኤል ከመባል በቀር። ደግ ሰው አይገኝብሽ ብሎ ረገማት። ያን ጊዜ ደግ ሰው ጠፋ።
" አቤቱ አድነኝ ደግ ሰው ጠፍቷልና " እንዲል ልበ አምላክ ንጉስ ዳዊት።

በለሷ እንደ ደረቀች እስራኤልም የተሰጣቸው የመመለሻ 40 ዘመን ሲያልቅ ምድረ እስራኤል ጠፋች።

፪. ህገ ኦሪት ናት

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ እስራኤል ሰው ፣ ምግባር ፣ ሃይማኖት ፣ በጎነት ፣ፍለጋ እንደ ሄደ ነገር ግን የሚገድል እንጂ የሚያድን ህግ ሆኖ አላገኘውም።

ህገ ኦሪት ሰውን አልጠቀመምና ህገ ኦሪትን አሳለፈው። ሻረው።

ቅዱስ ጳውሎስ ወደ ሮሜ ሰወች በላከው መልዕክቱ ምዕራፍ 8፥2 ላይ " በክርስቶስ ኢየሱስ ያለው የሕይወት መንፈስ ሕግ ከኃጢአት ከሞት ሕግ አርነት አውጥቶኛልና። " እንዲል ሕገ ኦሪት የሞት ሕግ ነበረ ማለት ነው።

ኦሪት ሕግና ሥርአት ነበራት የማይጠብቋትን መቀጣጫ ናት።

፫ . ኃጢአት ናት

ኃጢአት እንደ በለስ ቅጠል ሰፍታ በዚህ ዓለም ሞልታ አግኝቷታልና ረገማት። ኃጢአት በሶስት ነገር በበለስ ተመስላለች።
1. አዳምን ከገነት ያህል ቦታ እንዲወጣ እግዚአብሔርን ከመሰለ ጌታ የለየችው ዕፀበለስ ናትና።
2. የበለስ ቅጠል ሰፊ እንደመሆኑ መጠን የኃጢአትም መንገድ ሊጓዙበት የሚያመች ሰፊ መሆኑን ሲያጠይቅ።
3. በለስ ሲበሉት እንደሚጣፍጥ ሲቆይ እንዲመር ኃጢአትም ሲሰሩት ለሥጋ ደስታን የሚሰጥ ፣ ስሜትን የሚያረካ ነገር ግን ፍፃሜው ሞት እና መከራ ያለበት ህይወት ነው።
ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ክብር ይግባውና ስለ ናትናኤል ሲናገር " ፊሊጶስ ሳይጠራህ ከበለስ በታች ሳለህ አየሁህ አለው " ዮሐንስ 1፥49

በለስ የኃጢአት ምሳሌ ነውና ኃጢአት ሰርተህ በበለስ ስር በተሸሸግህ ጊዜ አውቅሃለሁ ማለቱ ነበር። በአንድ ወቅት ናትናኤል የሰው ሕይወት አጥፍቶ በበለስጨስር ቀብሮ ነበረና።

በለስን መርገሙ ኃጢአትን መርገሙ ነው። መርገሙ ከዚህ በኋላ በሃጢአት አንዳች ሰው አይያዝ ማለቱ ነው።

ለዚህም ነው አባቶቻችን በቀመራቸው የሕማማትን ሰኞ መርገመ በለስ ብለው መሰየማቸው።

ምድራችን የሰው ልጅ ከኃጢአት ርቆ ከእግዚአብሔር ተጣብቆ የሚኖርባት ትሆንልን ዘንድ የእግዚአብሔር አምላካችን ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን።

ይቆየን።
አሜን።


የእለት ተለት ጽሑፎቼን ለመከታተል ከዚህ በታች ባሉት ሁሉ እገኛለሁና ይከታተሉኝ። ከተመቸዎት ለሌሎች ያጋሩት።
My Facebook page link (በፌስቡክ ገጽ እንገናኝ)

https://www.facebook.com/deresse2020/

Main facebook account (ዋናው የፌስ ቡክ ገጼ ይቀላቀሉት)

https://www.facebook.com/DeresseReta

Follow me through telegeram (በቴሌግራም ሊከታተሉኝ ከፈቀዱ) ሁሉም ምልከታዬን የማጋራባቸው ማህበራዊ ድረ ገጾች ናቸው።

https://t.me/deressereta

ከአሥር አመት በላይ ከ50ሺ በላይ አንባቢዎች ያሉት መጦመሪያም አለ።

www.deressereta.blogspot.com

https://anchor.fm/deresse-reta/episodes/ep-ev5j5o

ረቡዕ 21 ኤፕሪል 2021

አቤቱ የሆነብንን አስብ

 "አቤቱ የሆነብንን አስብ" ሰቆቃው ኤርሚያስ 5 : 1


ኢትዮጵያ እንደ አገር ሕዝቦቿም እንደ ሕዝብ በአራቱም አቅጣጫ ያልሆነባት ነገር የለም። ሕዝቦቿ አንዱን መከራ ተሻገርን ሲሉ ሌላ መከራ ይደቀንባቸዋል።

የተፈጥሮ ሲባል ፣ ሰው ሰራሽ ፣ ሰው ሰራሹን አለፍን ሲሉ ሌላ ይደቀናል።


ወደ መንግስት ጮኽን ወደ አንተ አንጋጠጥን መልስ አላገኘንም። አቤቱ እባክህ ቸሩ ሩህሩህ ይቅር ባይ አምላካችን ሆይ የሆነብንን አስብ።


• ሴት ልጅ እስከ ጽንሷ ተገድላ ከሜዳ ላይ ተጥላለች፣

• ህጻናት ያለወላጅ ቀርተዋል፣

• አባት በሚስቱ እና በልጆቹ ፊት ተገድሏል፣

• ልጃገረዶች ተደፍረዋል፣

• ወጣቶች ተሰደዋል ተገድለዋል፣

• የሰው ልጅ እንደ እንስሳ ተቆጥሯል፣

• አሟሟታችን ከእንስሳት አንሷል፣

• ተገድለን ቁልቁል እየተሰቀልን፣

• ሞተን መቀበር ቅንጦት ሆኗል፤ አቤቱ የሆነብንን አስብ።

• በአሕዛብ ፊት መሰደቢያ ሆነናል፣

• የመገናኛችን ቤተመቅስ ተቃጥሏል አጥር ቅጥርህ ተደፍሯል፣

• አምላኬ ሆይ፥ በፊትህ የምንለምን ስለ ብዙ ምሕረትህ ነው እንጂ ስለ ጽድቃችን አይደለምና ጆሮህን አዘንብለህ ስማ፤ ዓይንህን ገልጠህ ጥፋታችንና ስምህ የተጠራባትን ከተማ ተመልከት። አቤቱ፥ ስማ፤ አቤቱ፥ ይቅር በል፤ አቤቱ፥ አድምጥና አድርግ፤ አምላኬ ሆይ፥ ስምህ በከተማህና በሕዝብህ ላይ ተጠርቶአልና ስለ ራስህ አትዘግይ።" ትንቢተ ዳንኤል 9 : 16 - 19

እስላም ክርስቲያኑ በአንድነት ጸሎት አውጆ ከፊትህ ተንበርክኳል ወደ አንተ ይጮዃል ያነባል። አቤቱ የሆነብንን አስብ።


ረሐብ ቸነፈር በሽታ አንበጣ ጦርነት ስድት በዚህ ያልጠና ሰውነት እንዴት ይቻለናል?


ስለህጻናቱ ስትል ማረን፣ ጤዛ ልሰው ድንጋይ ተንተርሰው ስለሚማልዱት ብለህ ማረን፣ በጾም በጸሎት በፊትህ በአንድነት ስለወደቁት ብለህ ማረን፣ ይልቁንም ከሴቶች ሁሉ ስለተለየችው ጸጋን ስለተሞላችው ቅድስት ድንግል ማርያም ስትል ማረን፣ ስለአለሙ ሁሉ ስትል በቀራንዮ አደባባይ ስለቆረስከው ስጋህ ስላፈሰስከው ደምህ ብለህ ማረን ይቅርም በለን።


የሰው ልጅ ወደ ልቡ ይመለስ ዘንድ በዘር ከመከፋፈል ይልቅ ከአንድ አዳም መፈጠሩን ያስብ ዘንድ ሁሉም አንድ መሆኑን የቋንቋው እንደ የቀለሙ መለየት ልዩነት እንዳያደርግ በዚህም ተከፋፍሎ እንዳይተላለቅ እባክህ ፍቀድ።


በሽታውን አስታግስልን፣

ለነፍሰ ገዳዮች ልብ ስጥልን፣

የተጨነቁትን ልባቸው የተሰበረውን አካላቸው የጎደለውን አጽናናልን፣ ነፍስ ከሥጋቸው በክፉዎች ያለፉትን ማረፊያ በአንተ ዘንድ አዘጋጅላቸው፣ ለወዳጅ ዘመዶቻቸው ፍጹም መጽናናትን አድልልን።


አቤቱ የሆነብንን አስብ።


ቤተመቅደስ ሲቃጠል ግድ ይበልህ።


እኛ ቤተመቅደሶችህ ስንገደል ግድ ይበልህ።


በስም የተጠራን ልጆችህ እረኛው እንደተመታ መንጋ ስንበተን፣ ስንሳደድ ግድ ይበልህ።


እንባችን በላያችን ደርቋልና በግፍና በበደል ደማችን በከንቱ ፈሷልና የምህረት ዐይንህ ወደኛ ይመልከት።


አቤቱ ሆይ ፥የሆነብንን አስብ።


አሜን።

ይቆየን።


የእለት ተለት ጽሑፎቼን ለመከታተል ከዚህ በታች ባሉት ሁሉ እገኛለሁና ይከታተሉኝ። ከተመቸዎት ለሌሎች ያጋሩት።

My Facebook page link (በፌስቡክ ገጽ እንገናኝ)


https://www.facebook.com/deresse2020/


Main facebook account (ዋናው የፌስ ቡክ ገጼ ይቀላቀሉት)


https://www.facebook.com/DeresseReta


Follow me through telegeram (በቴሌግራም ሊከታተሉኝ ከፈቀዱ) ሁሉም ምልከታዬን የማጋራባቸው ማህበራዊ ድረ ገጾች ናቸው።


https://t.me/deressereta


ከአሥር አመት በላይ ከ50ሺ በላይ አንባቢዎች ያሉት መጦመሪያም አለ።


www.deressereta.blogspot.com 


https://anchor.fm/deresse-reta/episodes/ep-ev5j5o

ሰኞ 19 ኤፕሪል 2021

መንፈስ ወደ ምድረበዳ ወሰደው

 መንፈስ ወደ ምድረበዳ ወሰደው


ልበ አምላክ ዳዊት "ወደ ቤተ እግዚአብሔር እንሂድ ባሉኝ ጊዜ ደስ አለኝ" ይለናል።
ንጉስ ስለሆነ ወደ ወንዝ ዳርቻ፣ ከአለም ጥግ ሌላው ጥግ ድረስ፣ አሉ በተባሉ መዝናዎች፣ ትላልቅ አለም አቀፍ ክንውኖች ዘንድ፣ ከቤተመንግሥቱ ሕንጻ አናት ላይ ሆኖ አየር መቀበል እና ከተማውን መቃኘት፣ የቤተመንግሥቱን ጊቢ አየር መቀበል ይችል ነበረ። ደስታን ከሚፈጥሩ ክንውኖች መካከል እነዚህ ተጠቃሾች ስለሆነ።

በጌታ ደስ ይበላችሁ እንዲል ንጉስ ዳዊትን ምድራዊው ነገር አላስደሰተውም። ይልቁንም ወደ እግዚአብሔር ቤት መሄድ እንጂ የፈለገው።

መንፈሳዊነት የሚገለጥበት ሰው ከሚያዝናናው ነገር ይልቅ ነፍሱን ወደሚያጸድቀው ነገር ያደላልና።

ቅዱሳንን መንፈስ ቅዱስ ወደ ገዳም ይመራቸው ነበረ።
መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን መንፈስ ወደ ምድረበዳ ወሰደው ይለናል። መንፈስ ቅዱስ ያላለው መንፈስ ቅዱስ ለአብና ለወልድ ሕይወታቸው ስለሆነ ነው አንድም የራሱ ፈቃድ ስላነሳሳው ነው።

ምድረበዳ አለ፤ ገዳም ለማለት ነው።

ወደ ገዳም ስንሄድ ከፈቃደ እግዚአብሔር ውጭ አይቻልም። ሰው ያስባል እግዚአብሔር ይፈጽማልና መንፈስ ቅዱስ ያነሳሳናል። ለመንፈስ ቅዱስ ማደሪያነት የተመቸ ሰውነት ሲኖረን።

ወደ ገዳም የመሄድ ዝንባሌ ያለው ሰው መንፈስ ቅዱስ የሚያነሳሳው ሰው ነው።

ላይሞላ ነገር የዓለም ፈቃድ ወደኋላ ይስበናል። በዚህ ቀን ደፋ ቀና ከምንለው፣ ከምንሄድበት መርሃግብር ሁሉ የሚበልጥ ለቤታችንም፣ ለሕይወታችንም፣ ለቤተሰባችንም የሚሆን የነፍስ ገበያ ገብይተን የምንመለስበት ሥፍራ ገዳም ነው።

መንፈስ ቅዱስ አነሳስቶ እየመራ እግራችንን ወደ ገዳም ይውሰደን። ወደ ቤተ እግዚአብሔር እንሂድ ስንባል ከምክንያታችን በላይ ነፍሳችንን የሚያስደስት ነገር ያድርግልን።

ይቆየን
አሜን።

ጦማሩን ስለጎበኙ አመሰግናለሁ!

መልካም ነገርን ለሌሎች ማጋራት ባህላችን እናድርግ፤ ላልደረሰዉ በማጋራት ድርሻችንን እንወጣ፡፡

ትቶ እና ችሎ

  ትቶ እና ችሎ ብጹእ ወቅዱስ አቡነ መርቆርዮስ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ በደረሰ ረታ ብጹዕነታቸው ለሶስት አሥርት አመታት እኛ በማናውቀው እግዚአብሔር በሚያውቀው በብዙ መከራ በብዙ ፈተና ውስጥ ነው ያሳለፉት። ...