ረቡዕ 30 ሴፕቴምበር 2020

አርአያነት

 "አርአያነት"


ከምትሰሩት ይልቅ ስለምታጠፉት ነገር ተጠንቀቁ።

ደረሰ ረታ


ሰው የዘራውን ያንኑ ያጭዳልና እያንዳንዳችን ከምንሰራው ይልቅ ስለምናጠፋው ነገር ልንጠነቀቅ ይገባናል።


የአለማችን ትላልቅ ሰዎች ይጠቅማል ያሉት እና እውቀታቸውን ተጠቅመው የሰሯቸው የአእምሯቸው ውጤት ጥፋት ያስከተለባቸው ብዙዎች ናቸው።


የኖቬል ሥራዎች


ጠቢባን እውቀት አይነጥፍባቸውምና ባለቸው እውቅና እና እውቀት ተጠቅመው ጥፋትን አምክነዋል፣ እድሉን ያላገኙት ደግሞ በሌሎች ጠቢባን ጥፋታቸው እንዲመክን ተደርገዋል።


ዛሬ አለማችን በብዙ አቅጣጫ በብዙዎች ስህተት እና ክፋት ጥንስስ እየታመሰች ትገኛለች። አገራችንም ኢትዮጵያ በ"ምሁሮቻችን" ያልተገባ ንትርክ እና ትርክት፣ በልሂቃን ዝምታ፣ በሆድ አደሮች ጫጫታ፣ በፖለቲከኞቻችን ጽንፈኝነት፣ እየታመሰች ነው።


አንዳንዶች ሊነጋ ሲል ይጨልማል ሲሉ ገሚሶች ደግሞ ከድጡ ወደማጡ እያሉ የዳቦ ሥም ያወጡለታል። ግራም ነፈሰ ቀኝ ዋጋ እያስከፈለን ይገኛል።


ታድያ እኛ ከየትኛው ነን?


እያወቁ ከሚያጠፉት ወይንስ እየሰሩ ከሚጠፋባቸው ወገን ነን?


እንደ አብይ ያነሳነው የመዳሰሻ ርእሳችን "ከምትሰሩት ይልቅ ስለምታጠፉት ነገር ተጠንቀቁ" የተሰኘው ቃላችን ብዙዎቻችን አንድን ተግባር ስንከውን የሚታየን ፊትለፊት ያለው በጎ ነገር እንጂ ከበስተጀርባው ያለውን አሉታዊ ተጽዕኖ ልብ አንለውም። ችግሩ ከተከሰተ በኋላ ጥፋተኝነቱንም ለመቀበል እንቸገራለን።


ለዚህም ነው ችግሩ ከመከሰቱ አስቀድሞ ጥንቃቄ እንድናደርግ ለማሳሰብ የተገደድኩት። ወድጄም አይደለም ጥፋቱ በራሴው ስለተከሰተ ላስተምርበትም ብዬ እንጂ።


ነገሩ እንዲህ ነው፦ ትንሽ ልጅ አለችኝ ሁለት አመት ከመንፈቅ ሆኗታል። እንደ አብዛኛው ቤተሰብ ልጅ ሞባይል ትወዳለች።ሞባይል እጇ እንደገባ "ዩቲዩብ" ውስጥ ገብታ የልጆች መዝሙር እና ጨወታ ትከፍታለች። የሚገርመው ደግሞ አገርኛ አትወድም የውጭውን ካልሆነ በቀር። ይህ ድርጊቷ እንደ አገር በልጆች ፍላጎት ላይ ብዙ መሥራት ያለብን ነገር እንዳለ ይሰማኛል። ይሁን እንጂ "የኢትዮጵያ ልጆች ቴሌቪዥን" ሳላመሰግን አላልፍም።


ወደጉዳዬ ስመለስ ሞባይል መውደዷ እንዳለ ሆኖ ዛሬ ያስተዋልኩባት ነገር ትንሽ ሳይሆን በደንብ ትኩረቴን ስቧል። መሉ በሙሉ ጥፋቱ የኔ ነው። አሁን የጻፍኩላችሁንም ጨምሮ የምጽፈው ሞባይሌን ተጠቅሜ ነው። ታክሲ ውስጥም ሆነ የትኛውም ቦታ ላይ ሆኜ እጽፋለሁ። ርእሴ ማህበረሰቡ ስለሆነ የትም ሆኜ ይጎነትለኛልና።


ይህ የአጻጻፍ ክስተት እቤት ድረስም ይዘልቃል። ከዚህ ጋር ተያይዞ ታድያ የመጻፍ ትእዛዝ ከውስጤ ሲደርሰኝ፣ መጽሐፍ የማንበብ ዛር ሲመጣብኝ፣ ድካሜን ለማራገፍ ስሻ መኝታ ቤት የመግባት ልምድ አለኝ። ልጄ ሶልያናም የኔ ነገር መጣባት መሰል ወደ መኝታ ቤት ትገባለች። እኔ እንደማደርገው በጀርባዋ ተኝታ፣ እግሯን አነባብራ፣ ሲያሻት በሆዷ ተኝታ ሞባይሏን ትመለከታለች።


እዚህ ጋር ነው ስብራቱ። 


ልጄ ሶልያና ለሁላችንም በኔ በኩል ተናገረች፤


ልጄ ሶልያና ለኔም ለናንተም የሚሆን መልእክት አስተላለፈች መሰል አጋራኋችሁ።


በድርጊቶቻችን መካከል ሁሌም ልብ ልንለው የሚገባ ነገር እንዳለ ይሰማኛል፣ እንቅስቃሴያችን ድርጊታችንን ከመከወን ባሻገር አርአያነት ያለውና ከመሰናክልነት እስከሚችለው አቅም ድረስ የጸዳ መሆን አለበት።


ሁላችንም እንዲህ ነን ሥንሰራ እንስታለን፣ ሥንሰራ እናጠፋለን፣ ሥንሰራ ያልጠበቅናቸው ብዙ ነገሮች ይከናወናሉ፣ ሥለዚህ ስለምንሰራው ብቻ ሳይሆን ከበስተጀርባው ስላለው ስህተት እንድናስብ መልእክቴን ማስተላለፍ እፈልጋለሁ።


እኔ ለልጄ አርአያነት የጎደለው ተግባር በማሳየቴ አልያም ለስለስ ስናደርገው የምሰራውን ነገር ብቻ ስመለከት ያላየሁት ነገር ልጄ ላይ ተጽእኖ አሳድሯል። ስለምጽፈው ነገር፣ ስለማነበው ጉዳይ፣ ስለምሰራው ሥራ ብቻ ሲሆን በተዘዋዋሪ ግን ስህተት እየሰራሁ እንደሆነ ልብ አላልኩም።


ልክ እንደዚሁ ሁላችንም ለምናደርጋቸው ነገሮች ጥንቃቄ እናድርግ እላለሁ። በመቀጠልም ከፍ ስንል እንደ አገር እንደ ተቋም ትዝብቴን ልሰንዝር።


የተቋማት ሰው ሃይሎች ስለሚቀጥሩት እንጂ ስለሚያባርሩት የቀድሞ ሰራተኛቸው ጥንቃቄ ይጎድላቸዋል። (በአንድ ወቅት በምሰራበት ተቋም አዲስ ተቀጣሪ ሰራተኞች ሥራ ጀምረው ወራት አልያም አመት ይሰሩና ይለቃሉ፣ አልያም በዚያው ይቀራሉ፣ የቅርብ አለቆችም ማስታወቅያ ያወጣሉ በራሱ የለቀቀውን ሰራተኛ ያሰናብታሉ፣ ይሕን ነገር በተደጋጋሚ ማየቴ ሰላም አልሰጥ ሲለኝ ዋና የሥራ ሃላፊውን ገብቼ አነጋገርኩት "ሰራተኞች ከዚህ ክፍል ለምን በብዛት ይለቃሉ? የሚለው ቢጠና ሃላፊነቱ የሰው ሃይል ቢሆንም exit interview እየተጠሩ/መልቀቂያ ለሚወስዱት ቢደረግ" ብዬ ላቀረብኩት ሐሳብ የሚያሳዝን ምላሽ ነበር ያገኘሁት። " ከዚህ የተሻለ ክፍያ የሚያገኙ ከሆነ ይሂዱ እኛም ሌላ እንቀጥራለን" ነበር ያለኝ። እዚህ ጋር ነው ችግሩ ስለምንቀጥረው እንጂ ስለምንለቀው ሰራተኛ አንጨነቅም።


ሐሳቤና ሐሳቡ ተቃርኖ ነበረው እኔ ከስህተታችን እንድንማርበት ስፈልግ እርሱ ስለሚተካው ሰራተኛ ነበር፤ የለቀቅናቸውን ሰራተኛ ክብርና ጥንቃቄ ከሌለን በእጃችን ስላሉት ያለን ጥንቃቄ ምን ዋስትና አለው።


የሥራ ሃላፊዎች ስለሚያሰሩት ሥራ እንጂ ሥለሚሰራው ሰው ጥንቃቄ ይግግድላቸዋል።


የጦር መሪዎች ነጻ ስለሚያወጡት አገር እንጂ በጦርነቱ ስለሚገደሉት፣ ጥቃት ስለሚፈጸምባቸው፣ ስለሚወድመው ንብረት፣ ተልእኮ አሰጣጥ ላይ ጥንቃቄ ጉድለት ይታያል።


ቴሌ፣ መብራት ሃይል፣ ውሃና ፍሳሽ፣ መንገዶች ባለስልጣን ሥራዎቻቸውን ሲያከነውኑ የሚሰሩትን ብቻ ሳይሆን ስለሚጠፋው ነገር የተጠያቂነት ሥሜት ሊሰማቸው ይገባል።


መንገድ ሲቆረጥ እና መስመር ሲዘረጋ የሕብረተሰቡ መሰረተ ልማት እንዳይደረግ ከፍተኛ ጥንቃቄ ሊደረግበት ይገባል።


ግለሰቦች አጥራቸውንም ሲጠግኑም ይሁን ሕንጻዎችን ሲገነቡ የነዋሪዎችን እንቅስቃሳ በማያደናቅፍ እና ሕይወታቸውን በማያናጋ መልኩ እንዲሆን ይጠበቃል።


ሁሌም አንድ ወደልቤ የሚመጣ ጉዳይ ላንሳና ላጠናቅ።


አገሪቱ ላይ የተለያዩ ችግሮች ሲከሰቱ፣ የነዳጅ ዋጋ ሲጨምር፣ ኢኮኖሚው መረጋጋት ሲሳነው፣ ባለሃብትና ነጋዴዎች ለመንግሥት ቅሬታቸውን/አቤቱታቸውን ሲያቀርቡ ሁሉም መንግሥትን ጨምሮ መፍትሔ ሲሰጡ ጫናው የሚያርፈው ድምጽ በሌለው ሰፊው ሕዝብ ላይ ነው።


በቅርቡ የኮቪድ19 የኮረና አለም አቀፍ ወረርሽኝ ወቅት ኑሮ በሁሉም ላይ በትሩን ሲያሳርፍ፣ ኢኮኖሚው አለምን ባሽመደመደበት ዘመን የጤና ተቋማት እና የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ አካል የሆነው የትራንስፖርት አጠቃቀም ውሳኔ የትራንስፖርት ወጪውን እንዲሸፍን የተደረገው ድሃው ሕዝብ ነው።


ስለዚህ ውሳኔዎቻችን አንዱ ጋር መፍትሔ ሰጪ ሲሆኑ ሌላ ሥፍራ ችግር ፈጣሪ እንዳይሆኑ ልንጠነቀቅ ይገባል እላለሁ። ይህ የግሌ እይታ ነው።


እኛ ምርጥ የሚባሉ ሥራዎችና ሐሳቦች ይኖሩን ይሆናል፤ አሉንም። ታድያ እንዚህን እንደ ልጃችን እንደምንሰስትለት ሁሉ ሌላኛውን ያላየናቸውንም እንድናያቸው መልእክቴን አስተላልፋለሁ። ሥራዎቻችን ሃላፊነት እና አርአያነት የጎደለው እንዳይሆን ጥንቃቄ እናድርግ። ከምንሰራው እኩል ስለሚጠፋብን ነገር ትኩረት እንስጥ።


Follow me through 

@deressereta

እሑድ 27 ሴፕቴምበር 2020

ኦርቶዶክሳዊ የአለም እይታችን

 ኦርቶዶክሳዊ የዓለም እይታችን

( Orthodoxy Interpretive frame work )

የዓለም እይታችን በዓለማችን ውስጥ ነገሮች እንዴት እንደሚከናወኑ ለመረዳት እንዲያስችለን በማወቅም ይሁን ባለማወቅ በአእምሮአችን የምንይዛቸው የግምቶች (assumptions) ስብስብ ነው። በእለት ተዕለት ከተፈጥሮ ጋር በምናደርገው ግንኙነት ከእውነታው የራቀ ምኞታችንን የሚወስኑ እነዚህ ግምቶች ናቸው ፡፡

እነዚህ ግምቶች ወደ አዕምሯችን የምንወስዳቸውን ነገሮች የሚተረጉሙበት ለአዕምሯችን እኛን ለመምራት በሚያስችል መልኩ አንድ አምሳያ(model) ይሰጡናል ፡፡

የአስተሳሰባችን እና የሕይወታችን አንድነት አንዲሠምር መሰረት ስለሚያደርግ ይህ የዓለም እይታ ለእኛ በጣም አስፈላጊያችን ነው። ጥሩ ሕይወት ምን ማለት እንደሆነ እና ትርጉም ያለው ምን እንደሆነ ሕይወት እንድንረዳ ያስችለናል ፡፡ ከአካባቢያችን የሚፈጥሩት ተጽእኖዎችን በምንጋፈጥበት ጊዜ ወዲያውኑ ሀሳባችንን እና ድርጊቶቻችንን እንድንመርጥ ይረዳናል ፡፡

የዓለም እይታ ከሌለ በእያንዳንዱ ቅጽበት የሚኖሩ ሁሉንም የስሜት ህዋሳት ግብዓቶችን መረዳት አንችልም ነበር። እኛ ሁላችንም የዓለም እይታ አለን ፡፡ ጥያቄው የእኛ የዓለም እይታ በምን ዓይነት ግምቶች ላይ የተመሠረተ እንደሆነ እናውቃለን? ወይ ነው

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለቆላስይስ ሰዎች በጻፈው ደብዳቤ ላይ በጣም ግልፅ በሆነ ሁኔታ ለክርስቲያኖች በሰጠው ማስጠንቀቅያ- " እንደ ክርስቶስ ትምህርት ሳይሆን ፣ እንደ ሰው ወግና እንደ ዓለማዊ እንደ መጀመሪያ ትምህርት ባለ በፍልስፍና እና በከንቱም መታለል ማንም እንዳይማርካችሁ ተጠበቁ ። " ቆላ 2:8 ብሏቸዋል፡፡

የሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስን ማስጠንቀቂያ በማዳመጥ ከክርስቶስ ይልቅ በዓለም እና በዓለም ባህላዊ ባህሎች በኩል የሚሰጡን ፍልስፍና ማታለያዎች (philosophical deceptions) ምንድናቸው?

ጥቂቶችን እነሆ :-

1. ምክንያታዊነት (Rationalism)

ምክንያታዊነት ለሚደርስባቸው መደምደሚያዎች በአመክኖአዊ አዕምሮአችን ላይ ሙሉ እምነትን ይሰጣል ፡፡ የእውነት ምንነት የሚረጋገጥው እና የሚወሰነው በአእምሮ የማስተዋል አቅምና በሥነ አመክንዮታዊ አስተሳሰብ ላይ ስንደገፍ ብቻ ነው የሚል አመለካከት ነው ፡፡ “I think, therefore I am” የሚለው የፈረንሳያዊ ሬኔ ዴካርት የተለመደው ጥቅስ አስተሳሰባችን ማን እንደሆን እና እኛ የሃሳባችን ድምር እንደሆንን የሚገልጽ አመለካከት ነው።
በሃሳባችን ወይም በምክንያቶቻችን ላይ ሙሉ በሙሉ እምነት ሊኖረን እና እንደ ሥጋችን እና ደማችን እንደሆን አድርገን እንድንጠብቀው ይገፋፋናል።
ይህ አመለካከት የእኛን ፈቃድ በማስቀደም የእግዚአብሔርን ፈቃድ እንደ ሁለተኛ ስለሚቆጥር ከኦርቶዶክሳዊው የዓለም እይታ ጋር ይጋጫል ፡፡ ይህ ደግሞ አስተሳሰባችንን በእጅጉ ወደ ሚቆጣጠሩት ወደ ሌሎች ብዙ ጎራዎች ይመራናል ፡፡

2. ተሞክሮነት / ተዳሳሽነት (Empiricism)

ይህ አመለካከት የእውቀት መሠረት ከስሜታችን አንጻር ሲታይ ተሞክሮአችን እንደሆነ ይገምታል። ይህ የሳይንሳዊ ዘዴ መሠረት ነው። የዚህ አይነት የዓለም እይታ ፍፁም እውነት የሚገኘው ስሜቶቻችን ከሚሰጡን እና እኛ የምናውቀውን በስርዓት ባለው መልኩ በተደረገ ጥናት አማካይነት ብቻ መሆኑን ያረጋግጣል ፡፡ በቅዱስ መጽሐፍ ውስጥ የተመዘገበውን የመለኮታዊ መገለጥን እውነት ውድቅ ያደርገዋል።

3. ሰብአዊነት / ግለሰባዊነት

ሰብአዊነት እና ግለሰባዊነት የተመሰረተው እውነት እና ሥነ-ምግባራዊ በሆነ መንገድ በሚፈለጉት ግምት ነው። ይኸውም የግለሰቦችን ራስን በራስ ማስተዳደር እና እያንዳንዱ ግለሰብ የራሱን ወይም የራሷን እውነት መፈለግ አለበት የሚለውን ሀሳብ ይወስዳል። ይህ በእምነት እና መለኮታዊ በሆነ መንገድ በተገለጡት በእግዚአብሔር ሕግጋት ላይ የተመሠረተ ጥገኛነትን ስለማይቀበል ከኦርቶዶክሳዊው የዓለም እይታ ጋር ይጋጫል ፡፡ ከቤተክርስቲያኒቱ ስልጣን ይልቅ ለእያንዳንዱን ግለሰብ አመለካከት እና ውሳኔ ከፍተኛ ቦታ ይሰጣል ፡፡ ይህ ደግሞ ከመንፈሳዊ እሴቶቻችን ሁሉ አርቆ ፍጹም ወደሆነው አለማዊነት (secularism) ይወስደናል፡፡

4. አንጻራዊነት(Relativism )

አንጻራዊነት መነሻው የሁሉም የፍርድ መሠረቱ አንጻራዊ ነው በማለት ሲሆን ፣ ይህም እንደ ሁኔታውና እንደግለሰቡ ወይም ድርጊቱን ግለሰቡ እንደሚያይበት ሁኔታ ይለያያል ማለት ነው፡፡ የግለሰቡ ወይም የሰዎች ስብስብ እምነቶች እና ሃይማኖት ለእነሱ “እውነት” ነው ብሎ ያስባል ፣ ግን ለሌሎች ግን የግድ እውነት አይሆንም ፡፡ በዚህ ግምቶች ስብስብ በዓለም አቀፍም ሆነ ሙሉ በሙሉ እውነት የሆነ ሃይማኖት የለም ፡፡ እንደዚሁም ሥነ ምግባራዊ ፍፁምነት የሉም ፣ ትክክለኛ ወይም የተሳሳቱ የሥነምግባር አቋሞች የሉም ፡፡ ሁሉም የሞራል እሴቶች ለአንዳንዶች እውነት ናቸው ግን ለሌሎች ግን አይደሉም ፡፡ ይህ ከኦርቶዶክስ ዓለም እይታ ጋር ይጋጫል ክርስትና ፍጹም እውነት ነው ፡፡ ፡ በአንጻራዊነት አመለካከት ምክንያት የራሳችንን እውነት አንዳንድ ጊዜ እንክዳለን ፡፡ ዘመናዊነት ሁሉንም ባህሎች እና ትውፊቶች አይቀበልም ፡፡ የቀደመውን እና የቀደመውን ዘመን “የጨለማ ዘመን” ነው ብሎ ይገምታል። ይህ አመለካከት በመፅሃፍ ቅዱስ ውስጥ ያልተካተቱትን የቤተክርስቲያን አባቶች እና የቤተክርስቲያኒቷን ሁሉንም ትውፊት በእጅጉ ዋጋ ያሳጣችዋል ፡፡

እነዚህን ሁሉ አንድ ላይ ስናመጣቸው ወደ እግዚአብሔር መኖሩ አይታወቅም ( agnosticism) ወደማለት እና ፈጽሞ እስከመካድ (atheism) ያደርሳል ፡፡ በእነዚህ ሁሉ ጎራዎች እና በውስጣቸውም በያዙት ድብቅ ግምቶች (assumptions) በእኛ ላይ ተጽዕኖ እያሳደሩብን መሆኑን እና በኦርቶዶክሳዊው የሕይወት መንገዳችን ላይ በተቃራኒው እንደቆሙ መገንዘብ አለብን ፡፡ የክርስቶስን እና የቤተክርስቲያኒቷን ትምህርት ሙሉ በሙሉ ለመቀበል እንችል ዘንድ የራሳችንን የዓለም እይታዎችን መመርመር ፣ የተደበቁ ግምታችንን ማሻሻል ፣ መመርመር እና አስፈላጊ ከሆነ እንዲለወጡ መፍቀድ አለብን።

አምላካችን በቅዱሳኑ አድሮ እና በሥጋዌው የተገለጠውን እውነት ሁሉ ተቀብለን ቤተክርስቲያናችንን የነፍሳችን መዳኛ እና የደስታችን ቦታ ማድረግ ይኖረብናል። የራሳችንን የአዕምሯዊ ግንባታ በመተው ፣ “ጌታ ሆይ የማይገባኝ አገልጋይህን እዝነኝ ፥ ባለማወቄና እርዳኝና በእውነትህ ውስጥ ምራኝ ”እንበለው ።

ታሪካችንን አስታውሰን ፣ ኦርቶዶክሳዊነት ያለመለወጥ በሐዋርያት በኩል የጌታችን እና የአዳኛችን ትምህርቶች መሆኑን ተረድተን እንደ የማይለዋወጥ የእውነት ምንጭ መቀበል ይገባናል።

የኦርቶዶክስ የዓለም እይታ ምንድነው?

እኛ ክርስቲያኖች እንደመሆናችን መጠን በአዕምሮአችን የማሰብ ችሎታ ብቻ ለመረዳት ከሚያስችለን በላይ የሆነ እምነት አለን ፡፡ እግዚአብሔር ከሁሉም ምክንያታዊ እውቀት በላይ መሆኑን እናውቃለን ፡፡ በምክንያታዊ ሂደት ወይም በሳይንሳዊ ዘዴ ሊብራሩ የማይችሏቸውን ተዓምራቶች ለመቀበል ምንም ችግር የለንም። ሃይማኖታችን ፍጹም በተገለጠው እውነት ላይ የተመሠረተ በመሆኑ ምስጢራዊ እና የማይታየውን እንቀበላለን ፡፡ሁሉን ቻይ እና ፍጥረቱን አፍቃሪ በሆነ አምላክ እናምናለን እንዲሁም ሙሉ በሙሉ እንታመናለን። ከዚህ ሥጋዊ ዓለም ባሻገር በሚመጣው ዓለም ውስጥ የዘላለም ሕይወት ለማግኘት ድህነትን እና ከእርሱ ጋር ህብረት እንዲኖረን እንፈልጋለን ፡፡ ኑሯችን በቁሳዊ ደህንነታችን እና ደስታን በመፈለግ ላይ የተመሠረተ የሕይወት መንገድ አይደለም። የቤተክርስቲያኗን ትውፊት እንቀበላለን እናም መጽሐፍ ቅዱስን እንደ ቤተክርስቲያን ስጦታ አድርገን እንቆጥረዋለን። እኛ በቤተክርስቲያን እና በትውፊታዊ አውድ መሠረት እንተረጉማለን ፡፡ የቤተክርስቲያናችን አባቶች ያቆዩልንን ጥበብ በቀላሉ መጣል አንችልም። በቅዱሳት መጻሕፍት ትርጓሜያችን ውስጥ ልንመለከተው ይገባል ፡፡

እንደ ቤተክርስቲያኗ አባልነታችን የክርስቶስ ምስጢራዊ አካል አባላት ነን። ዘመናዊው ማኅበረሰባችን ያስተዋወቀንን የሐሰት እውነቶችን እና ወጎችን በመከተል ወጥመድ ውስጥ እንዳንወደቅ እና መዳንን እና ዘላለማዊ ህይወትን ከእኛ በማራቅ ከእግዚአብሔር ህብረት እንዳይለዩን ከሐሰት ግምቶች መራቅ አለብን። ይህ ቀላል ጉዳይ አይደለም ፡፡ የቤተክርስቲያኗን እውነቶች እና ልምዶች ለመከተል በመወሰናችንም ምናልባትም ከብዙኅኑ ጋር ማለት በሚያስችል ሁኔታ ተቀባይነትን ልናጣ እንችላለን ፡፡
አሁን ያለንበት እውነታ በአእምሯችን ውስጥ የተገነባው በዘመናዊ የአኗኗር ዘይቤያችን ፣ በኦርቶዶክስ ባልሆኑ ክርስትያኖች በሚሰጡ ትምህርቶች እና የዘመናዊው ትምህርት ስርዓቶቻችንን በሚመሠርቱ ጎራዎች ላይ በመመስረት የተደበቁ ግምቶች ናቸው ፡፡ እነዚህ መሠረተ ቢስ ግምቶች እምነታችንን ያዳክማሉ። እነሱን መመርመር እና ከእምነታችን ጋር የማይሄዱትን በደንብ መለወጥ አስፈላጊ ነው ፡፡ የኦርቶዶክስ የሕይወት መንገድ የኃጢያተኛ አኗኗራችንን እንድንከፍት ፣ የተሳሳቱ አመለካከቶችን እንድንገለጥ እና ባህርያችንን እንድንለውጥ ይመራናል።

እነዚህን የተደበቁ ግምቶች በውስጣችን መኖራቸውን መመርመር የመጀመርያው ሂደት ነው ፡፡ ከኦርቶዶክሳዊው የሕይወት መንገዳችን ጋር የሚጋጩ በገሃዱ ዓለም ያሉ አንዳንድ ነገሮችን ለመለየት የተወሰነ ጊዜ ውሰዱ ፡፡ ከዚያ እራስዎን ይጠይቁ ፣ ቤተክርስቲያኒቷ በእነዚህ ሁሉ ተቃርኖዎች በቅዱሳት መጻህፍቶችዋ እና በትውፊቷዋ እንዴት ልትረዳኝ ትችላለች? ብለው ይማጸኗት

እንጂ

• ብሔረተኛ ሆኖ ኦርቶዶክስ መሆን አይቻልም ! ! !
• እየተሳደቡ ኦርቶዶክስ መሆን አይቻልም ! ! !
• በሰዎች ላይ እየተደገፉ ኦርቶዶክስ መሆን አይቻልም ! ! !
• ቤተክርስትያን ያወገዘችውን እየተከተሉ ኦርቶዶክስ መሆን አይቻልም ! ! !

መልካም ቀን
ዲ. ኤልያስ ደፋልኝ 

በምን መታወቅ ይፈልጋሉ?

 በምን መታወቅ ይፈልጋሉ?

(ምን ሰርተው ታወቁ?)


ከስብ ሥም ይሸታል ይላሉ አባቶቻችን ሲተርቱ። ልጅ እያለሁ ለበአል የቤታችን ግድግዳ ከሚዋብባቸው ጋዜጦች ላይ ከማነባቸው አምዶች መካከል "ምን ሰርተው ታወቁ?" የሚሰኘው ቀልቤን ይገዛዋል።

ኢትዮጵያ የጀግኖች አገር እና ሉአላዊት አገር ለመሆኗ ማረጋገጫው "የአድዋው ጦርነት" ድል የግንባር ላይ ምልክት ያህል ይሁን እንጂ ያኔም ሆነ በዚሁ በዘመናችን ብዙ በሥም ጠቅሰን የማንጨርሳቸው የጦር ሜዳ ጀግኖች አሉን።

ዘመን ተሻጋሪ የአትሌቲክስ ጀግኖች ለመዘርዘር ከመነሳት አለመጀመሩ ሳይሻል አይቀርም። ሰማይና ምድር እንዳይቆጡን በሁለት ወገን የተሳለ ስይፍ የመሰለውን እንቋችንን አትሌት ሻለቃ ኃይሌ ገብረስላሴን አለማንሳት ነውር ነው እንደ ምሳሌ እንጥቀሰው።

መጽሐፍ "እንቁዎቻችሁን በእርያዎች ፊት አታስቀምጡ" የሚለውን ዘንግተን በእርያ ፊት በግብር ስንኩላን ከሆኑት ፊት ሃይሌን በማስቀመጣችን በእጅ የያዙት ወርቅ እንደ መዳብ ይቆጠራል እንዲሉ ሆነብን።

እርሱ ግን ጽናቱ እና ጀግንነቱ በድቡሽት መሬት ላይ ሳይሆን በአለት ላይ የተመሰረተ ነውና ወይ ፍንክች ያባ ቢላዋ ልጅ ሆኖ አግኝተነዋል። ለማንኛውም ኃይሌ በሁሉም መስክ ጀግናችን ነው።

እስኪ ወደራሳችን እንመለስ።

ምን ሰርተን መታወቅ እንሻለን?

ምንስ እየሰራን ነው ያለነው?

በአንድ ወቅት ካነበብኩት ነገር የማስታውሰው "በሕይወት ዘመንዎ ፍጻሜ በእርስዎ የቀብር ሥነሥርዓት ላይ የሕይወት ታሪክዎ ምን ተብሎ እንዲነበብልዎ ይፈልጋሉ?" የሚል ነበር።

እያንዳንዳችን የሕይወት ታሪካችንን በተግባር እየጻፉ/እየተገበሩ ማለፍ ግድ ቢሆን ሥምዎ በምን እንዲጠራ ይፈልጋሉ?

በሕይወት ዘመንዎ በምን መታወቅ ይፈልጋሉ?

ተማሪ ከሆኑ መምሕሮችዎ ምን አይነት ተማሪ ነበር ብለው እንዲያስታውስዎ ይፈልጋሉ? የትምህርት ቤት ጓደኞችዎሰ?

የመንግሥት ሠራተኛ ከሆኑስ ቀጣሪዎችዎ አልያም የቅርብ አለቃዎ በምን እንዲያውቁዎ/ ምን አይነት ሰው ነው ብለው እንዲጠሩዎ ይፈልጋሉ? የሥራ ሃላፊስ ከሆኑ ምን አይነት አለቃ መባል ይፈልጋሉ?

አገር ቢመሩ?
በንግዱ አለም ቢሆኑ?
የቤተሰብ አስተዳዳሪ (ባል/ሚስት) ሆነውስ?
ልጅ እያሉስ ቢሆን?
የሰፈር ሰው እና ጎረቤትስ?

ሥም ከስብ ይሸታልና እንዲህ ተባልኩ፣ ሰው አይወጣልኝም፣ ደመ መራራ ነኝ፣ እድሌ ጠማማ ነው፣ ወዘተረፈ ከማለት የነገ ሥምዎት ላይ ዛሬ አቅደውና አውቀው ቢሰሩ ይሻላል።

ሥምን ለመገንባት የሚፈጀውን ያህል ሥም ለመጥፋት ጊዜ አይፈጅበትምና በጥንቃቄ እንንቀሳቀስ።

አገሬ ምንም አላደረገችልኝም ከማለት ለአገሬ ምን አደረኩላት የሚለውን አስተሳሰብ እናበልጽግ።

አገር የምታድገውና የምትበለጽገው ተባብረን ሥንቦጠቡጣት ሳይሆን ተባብረን ሥንሰራላት ነውና።

ወጣቶች፣ አረጋውያን፣ ምሁራን፣ የእምነት ተቋማት መምህራን፣ የተቋማቱ መሪዎች፣ የቢሮ ሃላፊዎች፣ ሰራተኞች፣ ነጋዴዎች፣ የፖለቲካ ፓርቲ አመራርና አባላት፣አገር መሪዎች ወዘተረፈ ሁላችንም ከወዲሁ እናስብ፤ ምን ሰርተን መታወቅ? ምን ሰርተን አገራችንን ማስጠራት እንፈልጋለን?

ልብ በሉ ምን ሰርተው እንጂ ምን ሰርቀው አላልኩም።

ሁላችንም እድል ተሰጥቶናል የአዲስ አመት የመጀመሪያው ወር የመጀመሪያው ሳምንት ላይ ስለሆንን እቅዳችንን እናስተካክል፣ ያላቀድን እናቅድ፣ ያቀድን እንኑረው።

ልጆቻችንም ወላጆቻቸው ምን ሰርተን እንዳለፍን የሚመረምሩት ታሪክ ይኑራቸው፣ ያልፈጸምነው እነርሱ የሚጨርሱትን በጎ ነገር እንተውላቸው።

ቸር ይግጠመን።
ደረሰ ረታ
8/1/2013
@deressereta

የመስቀሉ ነገር

 


የመስቀሉ ነገር
ደረሰ ረታ
16/1/2013
(ደመራ)

በንግሥት እሌኒ ትእዛዝ መሰረት መስቀሉን ለዘመናት ከተቀበረበት የቆሻሻ ክምር/ተራራ ሥር ጎልጎታ ከኢየሩሳሌም በብዙ መከራ እና ፍለጋ አግኝታ እስክታስወጣው (ከመስከረም አሥራ ሰባት እስከ መጋቢት አሥር) ቀን ድረስ የመስቀሉ ሃይል አይታወቅም ነበር።

መስቀሉ አስቀድሞ ከባድ ጥፋት/ወንጀል የፈጸሙ ሰወች ምድርን እንዳያረክሱ ከምድር ከፍ ከሰማይ ዝቅ ብለው በሞት የሚቀጡበት የተመሳቀለ ከእንጨት የሚሰራ ነበር።

ኢየሱስ ክርስቶስም ክብር ይግባውና ከወንጀለኞቹ እንደ አንዱ ተቆጥሮ ተሰቀለበት። በእለተ አርብ መጋቢት ሃያ ሰባት ቀን በስድስት ሰአት በከበረ እጸ መስቀል ላይ ሰቀሉት። ሳዶር፣ አላዶር፣ ዳናት፣ አዴራ፣ሮዳስ በሚባሉ ችንካሮች ቸነከሩት። እንደ ወንበዴ ሊቆጥሩት ንጹሁን በወንበዴዎች መካከል ተሰቀለ።

የክብር ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስ አዳምን ያድነው ዘንድ በእንጨት መስቀል ተሰቀለ። መከራን በሥጋው ተቀበለ።

የወንበዴዎች መቅጫ መስቀል በመለኮት ደም ከበረ።
ብዙ ተአምራትን ሰራ፤ አይሁድንም አሳፈረ። ፈርተው ደነገጡ።

ከዚህ በኋላ የመስቀሉ ነገር የአደባባይ ምሥጢር ሆነ።

አይሁድ በቅናት አይናቸው ስለቀላ የማዳኑን ሃይል ለመደበቅ በደላቸውንም ለመሸሸግ ያንን የወንበዴ መቅጫ የተመሳቀለ እንጨት/መስቀል በመለኮት ደም ከብሯልና ክብሩን ለመሸሸግ ወስደው ከምድር በታች ጥልቅ ጉድጓድ ቆፍረው ቀበሩት። የወንበዴዎቹንም መስቀል ከላይ አደረጉበት። እስከ አራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ድረስ (327አ.ም) ድረስ በኢየሩሳሌም ከተማ ቆሻሻ ተከምሮበት ለብዙ ዘመናት ለረጅም ወራት ተደብቆ ኖሯል።

አውቀውም ይሁን ሳያውቁ ቆሻሻ ደፉበት፣ የቆሻሻውም ብዛት ተራራ ሰራበት።

በመስቀሉ ልቧ የተነካ ንግሥት (ንግሥት እሌኒ) ደመራ አስደምራ መስከረም አስራ ስድስት በእጣን ጢስ እየተመራች የተቀበረውን መሥቀል ከተቀበረበት ከምድር ልብ አወጣች።

በአጼ ዳዊት ዘመነ ንግሥና ታስቦ እርሳቸው አረፍተ ዘመን ሲገታቸው በአጼ ዘርኣያቆብ ዘመን ኢትዮጵያ የግማደ መስቀሉ ባለቤት ሆነች።

የትናንቷ ኢትዮጵያ፣ የትናንት ኢትዮጵያውያን፣ የትናንት እናቶች(ሴቶች)፣ የትናንት መሪዎች ይህን ተግባር ሲፈጽሙ የዛሬዎቹ ግን ከቤተክህነት እስከ ቤተመንግሥት ለዚህ ዘመን ለዚያውም ለዚህ አገር እና ትውልድ የማይመጥን ተግባር ይፈጽማሉ።

ሆሳእና "አሁን አድን" የሚል ስያሜን ይዛ አሁን ለክርስቲያኑ ፍትህ ነፍጋለች፣ ከተማዋ ከካህን ስያሜዋን ያገኘች ብትሆንም ካህን ገፊ ሆናለች፣ ከተማዋ ለምህረት ይሁን ለመአት እሳት ይዘንብባት እንደነበር የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው። ሆሳእና የጌታ መገለጥ የታየበት በአል ቢሆንም ኢትዮጵያዊቷ ሆሳእና ግን ከክቡሩ የሰው ልጅ የጥምቀት እና የመስቀል ደመራን ማክበሪያ ሥፍራ ለከብት ማቆሚያ ተሰጥቷል።
የእንስሳት ክብር ከሰው/ከክርስቲያን ክብር ልቋል።
ናዝሬት (አዳማ)፣ ደብረዘይት (ቢሾፉቱ)፣ ሞጆ፣ስልጤ፣ እና ሌሎች ክልልም እንዲሁ እየቀጠሉበት ነው። የቤተክርስቲያንን ጥላቻ የመንግሥትን ሥልጣን ተገን አድርጎ ግለሰቦች ጫና ሆነዋል። ይህ ጥላቻ ጅማ፣ ጅግጅጋ፣ ሻሸመኔ፣ ዝዋይ፣ አሩሲ፣ አሰላ፣ መተከል ወዘተ ላይ አብያተክርስቲያናት ተቃጥለዋል ክርስቲያኖች ተሰውተዋል፤ ሐብት ንብረቶች ወድመዋል። የመንግሥት ተሿሚዎች እንደገና መልሰው ክርስቲያኑን በመግለጫ አስፈራርተዋል። የጸጥታ አካላት ቆመው ባለበት ሥፍራ የተደራጁ ጽንፈኞች አካላዊ እና ስነልቡናዊ ጥቃት ሲፈጸሙ እያየን ነው። መንግሥት ጥቃቱን ከመከላከል ይልቅ ለአጥቂዎች ሽፋን እየሆነ ያለበት ሁኔታ ነው ያለው።

በአስሩም ክልሎች በሁለቱም የፌደራል ከተሞች በሁሉም ወረዳና ቀበሌ፣ በሁሉም የግልና የመንግሥት ተቋማት ብልሹ አሰራር እና አመራር፣ በግልና በመንግሥት የከፍተኛ የትምህርት ተቋማት፣ መስቀሉ ተቀብሯል። የመስቀሉ አዳኝነት፣ የመስቀሉ ሃይል፣ ተደብቋል። ቆሻሻው (ምንዝር፣ ሙስና፣ ጥላቻ፣ ዘረኝነት፣ አስገድዶ መድፈር፣ ግብረ ሰዶም፣ የበላነት መንፈስ፣ የተተኪነት መንፈስ፣) ተከምሮበታል። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን እነርሱም (በሽንገላም ቢሆን) እንደሚሉት እኛም እንደምናምነው ሁሉን አቻችላ እና እኩል አድርጋ ከማእዷ የምታጋራ አገርም እናትም ጭምር ናት።

ይህች ሥንዱ እመቤት ቤተክርስቲያን ጠላቶቿ ገነው፣ ገፊዎቿ በዝተው፣ አቅሟ ተዳክሞ፣ ሰፊ እጇ ሰልሎ (ዝሎ) ታይታለች። ቢሆንም የሲኦል ደጆች እንኳን አይችሏትም። ትናንትንም እንዲህ እያለፈች እዚህ ደርሳለች። እንደሌሎች በእርዳታ እና በበጀት ሌሎችን ለመጫን እና ለማጥቃት የበላይ ለመሆን ሌላ ተልእኮ ይዛ የምትንቀሳቀስ ተቋም አይደለችም።

ትናንት የኢየሱስ ክርስቶስን መስቀል በደመራ በእጣን ጢስ ከተቀበረበት ከቆሻሻው ሥር እንዳላገኘችና እንዳላወጣችው ዛሬ ኢትዮጵያን የተጫናትን መከራ፣ መገፋፋት፣ መከፋፈል፣ መገዳደል፣ ለማስወገድ ደመራውን ደምሮ ጢሱን አጢሶ መስቀሉን ለማክበር ከፍ ከፍ ለማድረግ የመንግሥት ባለሥልጣናት ብልሹ አሰራር እና ቆሻሻ ተግባር ለጊዜውም ቢሆን የመስቀልን በአል የአገራችን የደቡብ እና የኦሮሚያ ክልሎች እንቅፋት ሆነዋል።

በሁሉም አቅጣጫ ኦርቶዶክሳዊ የሆነ እንባውን የሚያነባበት፣ ዋይታና እሮሮ የሚያሰማበት፣ በአላቶቹን በአደባባይ ሳይሆን እንደ ዘመነ ሰማእታት ከምድር በታች እንዲያከብር የሚጠበቅበት እየሆነ መጥቷል።

የመስቀል በአል ያነጋግረን እንጂ የጥምቀተ ባህር ነገርም ከተነሳ እጅን በአፍ ላይ አስጭኖ የሚያስቆዝም ነው።

ለመፍትሔው ብዙ የወጣት ማህበራት፣ ማህበረ ካህናት፣ ቤተክህነት፣ ሲኖዶስ ይንቀሳቀሳል። ነገር ግን ችግሩን ሊቀርፉት አልቻሉም። በቤተክርስቲያን ላይ በሚደርሱ ጥቃቶች ሳቢያ ብዙ የሚደራጁ በአካልና በየሚድያው (ፌስቡክ፣ ቴሌግራም፣ ዩቲዩብ) የሚደራጁ ምእመናን ሞልተዋል፤ ይሁን እንጂ ከተሰባሰቡበት አላማ ውጭ የአክቲቭስቶችና የዩቲዩበሮች እንጀራ ከመሆን አልዘለሉም። ይህም የውስጥ ችግራችን የመስቀሉን ሃይል በማወቅም ይሁን ባለማወቅ የሚጣሉ የቆሻሻ አይነቶች ናቸው።

የመስቀሉን ክብር የሚገልጥ መሪ ኢትዮጵያ ያስፈልጋታል። መስቀሉ የአማንያን ብቻ ሳይሆን ላላመኑትም ይጠቅማል። ከመስቀሉ ጋር የተቀበረ ፍትሕ ለኦርቶዶክሳዊያን ብቻ ሳይሆን ለሌሎች በእምነት ለማይመስሉን ጩኸታቸው ለታፈነ የእምነት ተቋማትና ምእመናን ሁሉ ፍትህ ያሰጣል። ሽቅብ ወደላይ የሚሸኑትን ግፈኞች አደብ ያስገዛል ለመንግሥት እና የጸጥታ አካላት ሳይቀር የራስ ምታት የሆኑትን ሥርአት ያስይዛል።

በመሥቀል በአል ሥም አገሪቱ ላይ የሚፈጸሙ ሥርአት አልበኝነት የኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን ብቻ መስሎን እንደ ጠላት ተመልክተው ደስታም ተሰምቶዎት ከሆነ ተሳስተዋል።

ይህ የጽንፈኝነት አካሄድ ኢትዮጵያዊ መስሊሙን፣ ፕሮቴስታንቱን፣ ካቶሊኩን፣ የይሖዋ ምሥክሩን፣ ወንጌላውያንን፣ ዋቄፈታውን፣ ባሕሉን፣ ወጉን፣ ታሪክን ሁሉ አንድ በአንድ መንካቱ አይቀሬ ነው። ስለዚህ አብሮ መንቃት አብሮ ቆሻሻውን ቆፍሮ ተራራውን ንዶ መስቀሉን አውጥቶ፣ ክብሩን ገልጦ፣ በአሉን በጋራ ማክበር የተሻለ መፍትሔ ነው።

ሰፊዋን ኦርቶዶክስ ከናቁና ከነቀነቁ ወደሌላው የማይመጡበት ምንም ምክንያት የለም። እነዚህን ሰወች ሃይማኖተኛ አድርጎ ብቻ ማየት፣ የእምነቱ ጥላቻ ብቻ አድርጎ ማየት ትልቅ ስህተት ነው፤ የትኛውም ሃይማኖተኛ በምንም መለኪያ ይህንን የማድረግ ሞራል የለውምና። ይህ ተግባር አገርን የማፍረስ ተልእኮ እንጂ።

መንግሥትም ሆነ ሕዝብ ይህንን ችግር የአንድ ቤተክርስቲያን ጉዳይ ብቻ አድርጎ ማየት የለበትም። ምንአልባት ዛሬ ኦርቶዶክስ እና ሙስሊም በእምነቱ ምክንያት ተገድሏል ያልን እንደሆነ የትናንቱን የሌሎች ቤተእምነቶች መቃጠል እና የምእመናን ሞት አንዘንጋ። ነገም የተደገሰልን እልቂትና ውድመት ሊኖር ስለሚችል በአንድነት በመቆም አገርንና ሕዝብን ልንጠብቅ ይገባል።

ችግሩ ዘላቂ ባይሆንም መስቀሉ ከተቀበረበት እስኪወጣ ክልከላዎች እስኪነሱ ቆሻሻውን ከመድፋት ይልቅ ማንሳት ላይ እስካልተረባረብን ድረስ ይቀጥላል።

ስለዚህ አገርንና ቤተክርስቲያንን ለመታደግ መሰባሰባችንን አንተው። ቆሻሻ (ብልሹ አሰራርን፣ ሙስናን፣ ስልጣንን አላግባብ መጠቀምን፣ ዘረኝነትን፣ ተረኝነትን፣ የግል ጥቅም ማስቀደምን) መስቀሉ የተቀበረበት ቦታ መጣልን እናቁም እንዲህ እያደረግን የምንቀጥል ከሆነ የቤተክርስቲያንን እና የአገርን ትንሳኤ ቀን እናረዝመዋለንና።

ንግሥት እሌኒ መስቀሉን ከተቀበረበት ለማውጣት ወራት የፈጀባት ሕዝቡ የጣለው የቆሻሻ ክምር ብዛት ነው። እንዲሁ ለኢትዮጵያ ትንሳኤ መቅረብም ሆነ መራቅ ምክንያቱ እኛ በምናጠራቅመው አይነት እና የቆሻሻ ብዛት ስለሚወሰን ጥንቃቄ እናድርግ።

መስቀሉ የሚወጣበት የመዳን ቀን የሚቀርብበት የሰወች እኩልነት የሚረጋገጥበት ቀን እንዲቃረብ ተራራውን ለመናድ፣ መስቀሉን ለማክበር ቁፋሮውን እንቀላቀል።

በየሙያ መስካችን በየተሰማራንበት ተራራውን እንናድ፤ (ጥላቻ፣ መከፋፈል፣ መጠቃቀም፣ ወዘተ) ይወገድ። ያኔ የመስቀሉም የሆነ የኢትዮጵያ ክብር ይገለጣል። ብዙዎች ይፈወሳሉ። ይድናሉ። ጎባጣው አሰራር ይቀናል፣ ለምጻሙ ይነጻል፣ የሞተ ተስፋችን ይለመልማል፣ እውሩ አመራራችን ይስተካከላል። እንባችን ይታበሳል።

ሕዝብና መንግሥትም በሰላም እጅ ለእጅ ተያይዞ ለልማትና ለሰላም ይሰለፋል። ኢትዮጵያ አገራችን ቁጥር አንድ ታላላቅ አገሮች አንዷ ትሆናለች። ኢትዮጵያውያን የስደት መከራቸው ማብቂያ ያገኛል። አማንያን በሰላም አምልኮአቸውን ያከናውናሉ። ነጋዴ ነግዶ አርሶ አደር አርሶ አርብቶ አደር አርብቶ ሰርቶ አዳሪ ሰርቶ ያልፍለታል። አውርቶ አደር እና አባልቶ/አዋግቶ አደሮች ቦታ ያጣሉ። በነው ከስመው ይጠፋሉ።

መስቀል መከራ ቢሆንም ቅሉ እኒህን ሁሉ የማሸነፍ ሃይል ስላለው ሁሉን ድል አድርጎ በአሉን በሰላም የምናከብርበትን ዘመን ቅርብ ያድርግልን።

በፍጹም መንፈሳዊ ቅናት ፍትሕን እንፈልግ፣ በፍጹም ትሕትና መፍትሔ ለማግኘት እንምከር። ከንግሥት እሌኒ የምንማረው በትህትና ወደ አባቶች ለምክር መቅረብን፣ በመንፈሳዊ ቅናት ለአግልግሎት መሯሯጥን፣ ለአገር ከፍታ ከክብር ዝቅ ማለትን ነውና። ዝቅ ብለን አገርን ከፍ እናድርጋት።

ከአጥብያ ቤተክርስቲያን እስከ ቅዱስ ሲኖዶስ የሚጠበቅበትን ያድርግ እያደረገም ይገኛልና እኛም የበኩላችንን እንወጣ።

በጾም፣ በጸሎት፣ በምሕላ፣ በሱባኤ፣ በንሰሐ፣ እግዚአብሔርን ምላሽ ልንጠይቅ መንግሥትንም በመደራጀት በሥርአት እና ሕጉን ተከትሎ በመንፈሳዊ ሥነምግባር መብታችንን ልንጠይቅ ይገባል።

የጌታዬ የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል ሆይ የጥፋት ጭለማ ውጦናልና ወዴት አለህ? በሚያጠፉን ጠላቶቻችን ተከበናልና ወዴት አለህ? ገጸ ምሕረትህ ወደኛ ትመለስ።

መስቀል ለእኛ ለምናምን ሃይላችን ነው፣ መድኋኒታችን ነው፣ የክብራችን መገለጫ ነው።

እውነት እንዳይደበቅ አጋሩት።
ይቆየን።

በቴሌግሬም ገጽ ለመከታተል

@deressereta

ቅዳሜ 22 ኦገስት 2020

+ እግዚአብሔር እንዴት ይፈርዳል? +



+ እግዚአብሔር እንዴት ይፈርዳል? + 
(ጊዜ ወስደው ያንብቡት አያጥር ነገር ታሪክ ሆኖ ነው)
አንድ ግብፃዊ መነኩሴ ለገዳሙ መርጃ የእጃቸው ሥራ የሆኑትን ቅርጫቶች ሊሸጡ ወደ እስክንድርያ ለመጓዝ በጠዋት ተነሡ፡፡
በመንገድ ላይ ታዲያ ትልቅ የቀብር ሥነ ሥርዓት ለማድረግ የሚጓዝ ሕዝብ ገጠማቸው፡፡ ሟቹ ዝነኛ አረማዊ ገዢ ሲሆን በዘመነ ሰማዕታት በሺህ የሚቆጠሩ ክርስቲያኖችን የገደለ ሰው ነበር፡፡ አሁን ዕድሜ ጠግቦ ሞቶ ነው፡፡ ቀኑ ውብ ፀሐያማ ቀን ነበርና የሀገሩ ዜጎች በነቂስ ወጥተው ገዢያቸውን እየቀበሩ ነው፡፡
ይህንን ያዩት መነኩሴ ጉዳያቸውን ፈጽመው ወደ ገዳም ሲመለሱ አሳዛኝ ዜና ሰሙ፡፡ ለስድሳ ዓመታት በበረሃ በብሕትውና ቅጠልና የበረሃ ፍሬ ብቻ እየበላ የኖረ ባሕታዊ በዚያች ዕለት በጅብ ተበልቶ ሞቶ ነበር፡፡
መነኩሴው እጅግ ጥልቅ ኀዘን ውስጥ ሆነው እንዲህ ሲሉ አሰቡ ፦
‘በሺህ የሚቆጠሩ ክርስቲያኖችን የገደለው አረማዊ ሰው በታላቅ ክብር ታጅቦ ሲቀበር ሕይወቱን ሙሉ በጾምና በጸሎት ፈጣሪውን ያገለገለው ባሕታዊ በጅብ ተበልቶ የተዋረደ አሟሟት ሞተ፡፡ይህ እንዴት ዓይነት ፍርድ ነው? እግዚአብሔር ከመልካምነቱ ሁሉ ጋር ኢፍትሐዊ ነገሮች ሲሆኑ ዝም ብሎ ይፈቅዳል፡፡ በዚህ ምክንያት ብዙ ሰዎች የፈጣሪን መኖር ይጠራጠራሉ፡፡ እኔም ፍርዱን እንዲገልጽልኝ መጸለይ ይኖርብኛል’ አሉ፡፡
ከዚያች ቀን ጀምሮ መላልሰው ወደ ፈጣሪ ‘’ፍርድህን ግለጽልኝ’ ብለው ደጋግመው ጸለዩ፡፡ ብዙም ሳይቆይ እግዚአብሔር ፍርዱን እንዲህ ገለጠላቸው፡፡
ከሳምንታት በኋላ እንደተለመደው ወደ እስክንድርያ የሦስት ቀን ጉዞ ሊሔዱና ቅርጫታቸውን ሊሸጡ ተነሡ፡፡መንገዱን እንደጀመሩ ድንገት አንድ ወጣት መነኩሴ ወደ እርሳቸው ሲመጣ ተመለከቱ፡፡
‘’አባቴ ይባርኩኝ’
‘እግዚአብሔር ይባርክህ ልጄ’
‘አባቴ ወዴት ይሔዳሉ?’ አለ ወጣቱ መነኩሴ
‘ወደ እስክንድርያ ቅርጫቴን ልሸጥ እየሔድኩ ነው’ አሉት
‘ጥሩ አጋጣሚ ነው አባ እኔም ወደዛ እየሔድኩ ነው’ አለ በትሕትና
‘ጎሽ አብረን እንጓዛለና’ አሉ አባ፡፡ ወጣቱ መነኩሴ ከእጃቸው ሸክማቸውን ተቀበለ፡፡ ጥቂት እንደሔዱ እንዲህ አላቸው፡፡

የአዳል በግ

 

አንዱ ደወለልኝና የአገራችን ደቡባዊት ከተማ ስም ጠራልኝና እዛ ከተማ ውስጥ እና ዙርያዋ የሚገኙ ወጣቶች የአዳል በጎች ናቸው እንዴ? አለኝ።
እኔ እስከማውቀው የአዳል በግ ባለቤት/ባለበጉ ያልሆነ ከግልገልነት እስከ ሙክትነት እድሜው ዘወር ብሎ ያላየው ገዝቶ እየነዳ ወስዶ የሚያተርፍበት፣ የገዛ አርዶ አወራርዶ ነግዶ የሚያተርፍበት፣ ሌላው የደላው ደግሞ በልቶ ከርሱን የሚሞላበት ነው።
ሻጭም በርሱ ስሜት እየለካ በጉን ብሔርና ክልል ይሰጠዋል፤ ከበግነት ማንነት የአዳል በግነት መለያ ያላብሰዋል።የበጉን ሥጋና ቆዳ አዋዶ ይሸጠዋል።
ይሕንን የዋህ ሲጠሩት አቤት፣ ሲሸጡት ገዢን ተከትሎ የሚሄድ፣ ሲያርዱት ለምን ብሎ በማይጠይቅ በግ ለሰው የተመሰለው፤ ለዚያውም በክፉ ሰው ከሰውነት ልክ በወረደ ክብርን ጠርቶ ውርደትን በመረጠ ሰው አለማቀፋዊ ማንነቱን በውስን ሥፍራ በጠባብ መንደር በብሔር የተሸበበ ሰውን ይወክል ዘንድ የተገደደ በግ ነው። የአዳል በግ።
እነዚህ ሰወች ደግሞ ከሰውም ይልቅ ለአውሬነት የሚቀርቡ፣ አውሬያዊ ጸባይ ያላቸው። ሰውን ቁልቁል ዘቅዝቀው የሚሰቅሉ፣ ብሔርን መሰረት አድርገው ለይተው ገድለው አስክሬንን የሚያክል ነገር ያለ ባህላችንና እምነታችን መሬት ለመሬት የሚጎትቱ፣ እንደ አገር ድሃ እና ለማኝ አገር፣ እንደ ሕዝብ ለሰው ልጅ የሚገባውን የተመጣጠነ ምግብ መመገብ አይደለም በአግባቡ በልተን የማናድር፣ እንዲሁ ብሔርና ሐይማኖትን መሠረት በማድረግ ሐብት ንብረትን ለማውደም እንደ መንጋ የሚነዱ፣ መንግሥትን ያህል ተቋም በጥቅም በመገዛት ለዚያውም ለጠላት አገር መንግሥት ለመገልበጥ ላይ ታች የሚሉ የሰው እንክርዳዶች።
እነዚህ ናቸው በየዋሁ በግ የተመሰሉት፤ በአንድ በኩል እውነትም ሲታዩ በጎች ናቸው ለሚያርዳቸው የሚታዘዙ፣ ገድሎና ዘልዝሎ ሊበላቸው ከቋመጠ ጋር የሚውሉ። በሬ ካራጁ እንዲሉ። ክፋታቸው እንዳለ ሆኖ ያሳዝናሉ።
እንደ በግ ግር የሚሉ፣ የማያስቡ የማያስተውሉ፣ የሚጠቅማቸውን ለይተው የማያውቁ። ከትናንት ውድቀትና ስህተት የማይማሩ። አልፎ ተርፎ ከራሳቸውም ሥህተት ጭምር የማይማሩ።
ይህ ጓደኛዬ ስለነዚህ ወጣቶች ሲያወራልኝ በስሜት ነበር በውስጡ የሚንተከተከው ደም የቆዳውን ከለር እስኪቀይር ነበር ደሙ ፈልቶ በስሜት እያወራኝ ያለው።
እውነት ግን ምን ሆነናል?
ምንስ እየሆንን ነው?
ምንድን ነው የነካን?
እስከማውቀው ኢትዮጵያዊነት እንዲህ አልነበረም፤ እርግጥ ነው ጥንትም አንዳንድ አገርና ሕዝብን ለጥቅም ሲሉ አሳልፈው የሚሸጡ አሉ። ነበሩም በመጠን እና በይዘታቸው ግን ይሕን እንደማያክሉ የታሪክ ድርሳናት ይመሰክራሉ። "የአበሻ ጀብዱ" የሚለው መጽሐፍ ቋሚ ምሥክር ነውና።
ይህ ተግባር ጓደኛዬ በጠቀሳት አንዲት ከተማ የተወሰነ የተወገዘ ተግባር ብቻ አይደለም። ዋና ከተማችንን ጨምሮ እንጂ።
የወደሙ ሐብት ንብረቶች፣ የሞቱ ሰወች፣ የጎደለ አካል ከአንድ የጦርሜዳ ውሎ በላይ ነው። እንደ አገርም እንደ ሕዝብም በአለም መድረክ የተዋረድንበት። ገዳይም ሟችም እኛው ራሳችን ... የሆንበት አሳፋሪ ተግባር።
የሚላስ የሚቀመስ የሌለው መናጢ ድሃ ወጣት ንብረት ሲያወድም የሥራ ገበታው ሥራ አጥ ወገኖቹ ሰርተው ደመወዝ አግኝተው ቤተሰብ የሚያስተዳድሩበትን ሥፍራ ቋሚ እና ተንቀሳቃሽ ንብረት የሚያቃጥል።
በደጉም በክፉም ጊዜ ጸጥታ በማስፈን፣ ሰላማችን እንዳይደፈርስ ዘብ የሚቆሙ የጸጥታ አካላትን መግደል፣ አካል ማጉደል ያጎረሰ እጅ ነካሽነት ነው።
ለነዚህ አረመኔዎች የአዳል በግነት ምግባራቸውን የሚገልጥ የነውረኝነታቸው መገለጫ ሥም ሳይሆን የክብር ሥም ነው የሚሆነው። ለአዳል በጎች ደግሞ እንዲህ ጭካኔ በተሞላ ተግባር በሚሰማሩ ከሰውነት ክብር በወረዱ በመንጋ በሚያስቡ በመንደር በተወሰኑ ወጣቶች መመሰል ስድብ ነው።
ቀጣይ ትውልድ የማፍራት ተግባር ላይ ቤተሰብ ትልቅ ድርሻ እንዳለው እሙን ነው በመቀጠል የአካባቢው ማህበረሰብ የሐይማኖት አባቶች የአገር ሽማግሌዎች የትምህርት ቤት መምህራን ወዘተ እያለ ይቀጥላል። እስከ ማስታውሰው እነዚህ አካላት በኔ ማንነት ውስጥ ድርሻቸውን ስለምገነዘብ ለነዚህ አካላት ትልቅ ክብር ነበረኝ። እነርሱ በውስጤ ባሰረጿት የአንዲት ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያዊነት ውስጤ በፍቅር ብርሃን ይንቦገቦጋል የመንደርተኝነት ጨለማ አልዋጠኝም። "ኑ ቡና ጠጡ" የምትል የመልእክት ድምጽ ከወላጆቼ እንደሰማሁ በቀጫጭን እግሮቼ ብን ብዬ በርሬ ዘር፣ ቀለም፣ ሐይማኖት፣ ብሔር ሳልለይ ቡና ጠጡ ብዬ ከመጥራት ወዲያ መከፋፈልን ባላየሁበት ማህበረሰብ ውስጥ እንዴት ዛሬ በሐይማኖት፣ በብሔር ተከፋፍሎ ጸብ ግድያ ማፈናቀል ንብረት ማውደም ከየት መጣ?????
ማንስ በመካከላችን የሐሳብ እንክርዳድ ዘር ዘራ?
የሐይማኖት መምህራን በምሣሌ ሲያስተምሩ አንድ ገበሬ መሬቱን አርሶ አለስልሶ ስንዴ ዘራበት ሰብሉ ከቡቃያነት አልፎ ከፍ ማለት ሲጀምር እርሻውን ቢመለከት አረም ወርሮታል እንደልማዱ ቤተሰቡን ሰብስቦ የአከባቢውን ሰው ደቦ ጠርቶ የበቀለውን አረም አረመው። በመቀጠልም የዘራው ዘር አብቦ ካፈራ በኋላ ተመልሶ ቢመለከተው ንጹሕ የስንዴ እርሻ በእንክርዳድ ተወርሯል። የእምነት መምህራን ይህንን የስንዴ እርሻ በእንክርዳድ መወረር አመስጥረው ሲያስተምሩ "እንክርዳዱን" የዘራው ጠላት ሰይጣን እንደሆነ ያስተምራሉ።
በዚህ ትውልድ መካከልም የሰው ልጅ እንደ ሰው ሲፈጠር እንዲህ በመከፋፈል ሳይሆን ከአንድ አዳም እንደተገኘን አሁንም የእምነት ተቋማት የሥነ ፍጥረት ትምህርት አስተምህሮ ያስረዳናል። እንዲህ በመከፋፈል እንድንባላ እንድንጋጭ አንዱ ሌላኛውን እንዲያሳድድ ንብረት እንዲያወድም አገር እስከ ማፍረስ የሚያደርስ ግጭት እንዲፈጠር የሚያደርጉ ተግባራት ይከናወናሉ። ይህን እንዲሆን ማን አደረገ? ካልን ሁላችንም የምንገነዘበው የሰይጣንን ተግባር የሚተገብሩ በትውልድ መካከል የእንክርዳድ ዘርን የሚዘሩ አክቲቪስቶች፣ ፖለቲከኞች፣ "ከእውቀት ነጻ " ምሁራን ተብዬዎች፣ ሚዲያዎች ወዘተ ናቸው።
ችግሩን ማወቅ የመፍትሔው አጋማሽ ነው እንዲሉ ምሁራን ትውልዱ ራሱን እንዲህ በውስጣችን እንክርዳድ የሚዘሩትን ምን ማድረግ ይጠበቅበታል? መንግሥት? የእምነት አባቶች፣ የአገር ሽማግሌዎች፣ ወዘተ ምን ያድርጉ?
አስቀድመን እንደተናገርን በስንዴ እርሻ ውስጥ የበቀለውን የእንክርዳድ ዘር ገበሬው በመኸር ወቅት ስንዴውን ከእንክርዳዱ በጥበብ እንዲለይ በየደረጃው ያለን ስለ ሕዝባችን ሃላፊነት የሚሰማን ግለሰብ እና በተለያየ የመንግሥት ሃላፊነት በመውሰድ ሠላም የማስፈን፣ ጸጥታ የማስከበር፣ ሕግን የማስከበር ተግባር ላይ የተሰማሩ አካላት በጥበብና በማስተዋል እራሳችንንና ወገናችንን ከጠላት ዲያቢሎሳዉያን ልንጠብቅ እና ልንከላከል ይገባል።
ወደ መሬት ስናወርደው ሕብረተሰቡ የሚደርሰውን መረጃ ከማህበራዊ ሚዲያ፣ ከኤሌክትሮኒክ ሚዲያ፣ ከህትመት ሚዲያ፣ ወዘተ የምናገኛቸውን መረጃዎች ብስል ከጥሬ መለየት የሚጠቅመውን ከማይጠቅመው፣ እውነተኛውን ከሐሰተኛው መለየት ይጠበቅበታል።
ሕዝብን ከጥፋት አገርን ከመበታተን ሐብትና ንብረትን ከውድመት የሚታደጉ የጸጥታና የደህንነት አካላት አገርንና ሕዝብን ለመታደግ ያገኙትን ሳይንሳዊ ጥበብ ፖለቲከኞችን እና መሪዎችን ከመጠበቅ፣ ተፎካካሪዎችን መረጃ ከመጥለፍ እና ከማገት ተጠብቀው አገርን እና ሕዝብን ከጥፋት ለመታደግ የእለት ተለት አገር ውስጥ የሚሰራጩ መረጃዎችን በማሰስ በመተንተን ጥፋት ከመፈጠሩ ንብረት ከመውደሙ የሰው ህይወት ከማለፉ አስቀድሞ ሊያከሽፍ ጥፋተኛውንም በቁጥጥር ሥር ማዋልና ለሕግ ማቅረብ ይኖርበታል።
የሕግ አስፈጻሚ አካላት እና በተለያዩ ተግባራት ላይ የተሰማራው ባለስልጣን ህግን ከለላ በማድረግ ጥፋት ላይ የተሰማሩትን ፈቃድ ከመስጠት በዘለለ የየእለት ተግባራትን ትክክለኛነት መመዘን፣ እርምትና እርምጃ መውሰድ ይጠበቅባቸዋል። ይህንን ካልከወንን ጥፋቱ ቀላል አይሆንምና። እንደ ምሳሌ ብናነሳ በማህበረሰብ መካከል የመከፋፈል ቅስቀሳ የሚያደርጉ ሚዲያዎች አስቀድመው ሕጋዊ ከለላ ለማግኘት በሕጋዊ መልኩ ፈቃድ ወስደው ሥራ ጀምረዋል። ግብር ይከፍላሉ። ሕግ ባለበት አገር ውስጥ ሕጋዊ መስለው ይንቀሳቀሳሉ። ይህ ብቻ በቂ አይደለም። ብሮድካስት ባለስልጣን በየወቅቱ ሥራቸውን መፈተሽ፣ እርምት መውሰድ፣ እርምጃ መውሰድ፣ ወዘተ ይኖርበታል። ይህ ሳይሆን ሲቀር ግን የሚደረገው ሩጫ "ጅብ ከሄደ ውሻ ጮኸ" ይሆንብናል። እነርሱ የተቋቋሙበትን አላማ ካሳኩ በኋላ ማስጠንቀቅያ መሥጠት፣ ለመዝጋት መሯሯጥ በሕዝብ ላይ መዘባበት ይሆናል። ሌሎችም እንዲሁ ተጠቅሰው ተዘርዝረው የማያልቁ አስቀድመን አስበን በመከወን ከጥፋት ልንታደግ የሚገቡ ተግባራት አሉን።
ብዙውን ጊዜ እንደታዘብኩት ከሆነ አንድ ነገር ከሆነ በኋላ ህጉን ስንተች ስለ አገሪቱ ሕግ መላላት ስናወራ ይደመጣል። እንደ ኢትዮጵያ ከ98% በላይ ሐይማኖተኛ በሆነ ማህበረሰብ መካከል ስለ ምድራዊ ሕግ መጨቃጨቅ ለኔ ውሃ የማያነሳ ሀሳብ ነው ምክንያቱም እንደ ሐይማኖተኛነታችን እምነትን እንደተቀበለ እና እንደመንፈሳዊ ሰው ምድራዊ ሕግ ለሰው ልጅ ኢምንት ነውና። ምድራዊ ሕግ ስለ መደፈር ፍትሕ ከመስጠቱ በፊት መረጃና ማስረጃ ይሻል። መንፈሳዊ ሕግ ግን ስለ ዝሙት "ያየ የተመኘ አመነዘረ" ይላል። በእምነት ጥላ ሥር ላደገ ማህበረሰብ ሴትን ልጅ ለመድፈር አይነሳሳም። ሕጉ ላልቷል ሥጋት አይሆንበትም። ሕጉን ሳይሆን የሚያወግዘው ዝሙትን ነውና። ስለዚህ የእምነት ተቋማት እና የእምነት ተቋማት መምሕራን ትውልድን በመቅረጽ ላይ ድርሻና ግዴታ አለባቸው። እንዲህ ስንል ግን በእምነት ስም የሚነግዱትን ስመ አምላክ ነጋድያንን ልብ ልንል ይገባል። እነርሱም የትውልዱ ነቀርሳዎች ስለሆኑ።
እንግዲህ እንደ በግ እንዳንነዳ ምን እናድርግ?
በግ ላለመሆን ያለን ብቸኛ አማራጭ ሰው መሆን ነው።
ሰው ስንሆን:-
እንደ ሰው እናስባለን
እንደ ሰው እንኖራለን
ሰዋዊ እሳቤ ይኖረናል
እንተሳሰባለን
እንከባበራለን
በሐሳብ የበላይነት እናምናለን
የሰውን ክቡርነት እናምናለን
ለሕግ እንገዛለን
በጥቅም አንገዛም
አገርና ሕዝብን አንሸጥም
ሕዝብን ለፖለቲካ ፍጆታ አናባላም
ንብረት አናወድምም
አካል አናጎድልም
ሕይወት አንቀጥፍም።
ሰው ክቡር ሆኖ ሳለ አያስተውልም እንስሳትን መሰለ እንዲል እኛም ወደ ማስተዋል ተመልሰን እንደ ሰው እንኑር።
ደረሰ ረታ
ሐምሌ 7/2012

እንደ ሰው ልንኖር

 

የከሰል ጭስን አደገኝነት አውቆ ከሰልን የሚፈራ እና የሚጠላ ከመሸ በኋላ ከሰል አቀጣጥሎ ቤቱ አስገብቶ የሚቆልፍ ሰውና በዘር/ብሔር /በሃይማኖት ግጭት የሚመጣን እልቂት የሚጠላ ነገር ግን ጸቡን የሚያቀጣጥል ሰው ይመሳሰሉብኛል።
መቸስ ግጭት አንዴ ከተቀጣጠለ በኋላ አደጋ እንዳያደርስ የሚያደርግ ብልሃት እንደሌለው አገር ያወቀው ጸሃይ የሞቀው ነው።
አሳን መብላት በብልሃት እንዲሉ ማንኛውም ግጭት ዋስትና የለውምና ሁላችንም ከብሔራችን ሰውን አስቀድመን እንተዛዘን እንከባበር።
እዚህ ቤት ያለ እሳት እዛም ልብ እያልን ቢሆን መልካም ነው።
ዛሬን ለመኖር ትናንትን ምክንያት በማድረግ ከነገ መጨናገፍ ኋላቀርነት ነው።
ትናንት ጡት ተቆረጠ በሚል ትርክት ዛሬ እየቆረጡ ነገን ማበላሸት የትናንት ትርክት እውነት እንኳን ቢሆን በዚህ ዘመን እንዲህ አይነት ተግባር መከወን ከትናንቶቹ እጅግ አንሶ መገኘት ነው።
ትናንት በባሪያ ንግድ ዘመን አባቶቻችን ይህን ኋላቀርነት ለማስቀረት ብዙ ዋጋ እንዳልከፈሉ ዛሬ አለም በዘመነበት ሰአት እንዲህ እንደ ግመል ሽንት ወደ ኋላ መሄድ ነው። ድርጊታችንም ሰወች እንዲህ አድርጉ እያሉን እንደ ሮቦት ሳያገናዝቡ መነዳት ዘመናዊ ባርነት ነው።
እምቢኝ ብለን ወደ ኋላ ዘመን የሚያስጉዙንን ልናወግዛቸው የተልእኳቸው አስፈጻሚ ከመሆን በመቆጠብ አገራችንን በልማት እና በሰላም ማስከበሩ ጎን ልንቆም እንደ ፍጥረታችን እንደ ሰው ልንኖር ይገባል።
ደረሰ ረታ
ሐምሌ 29/2012

ጦማሩን ስለጎበኙ አመሰግናለሁ!

መልካም ነገርን ለሌሎች ማጋራት ባህላችን እናድርግ፤ ላልደረሰዉ በማጋራት ድርሻችንን እንወጣ፡፡

ትቶ እና ችሎ

  ትቶ እና ችሎ ብጹእ ወቅዱስ አቡነ መርቆርዮስ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ በደረሰ ረታ ብጹዕነታቸው ለሶስት አሥርት አመታት እኛ በማናውቀው እግዚአብሔር በሚያውቀው በብዙ መከራ በብዙ ፈተና ውስጥ ነው ያሳለፉት። ...