ሐሙስ 1 ኖቬምበር 2012

የኢየሩሳሌም የመንፈስ ተጓዥ



                                                 ስምዖን ጌታን ታቅፎ



ክፍል ፪
ባለፈዉ ክፍል አንድ ላይ ረድኤተ እግዚአብሔርን አጋዥ በማድረግ ጀምረን ስለ አዉግስጦስ ቄሳር አመጣጥና ንግስና ተመልክተን  አዉግስጦስ ህዝቡ እንዲቆጠር ለምን እንዳደረገ አንስተን ነበር ያቆምነዉ፤ እነሆ እግዚአብሔር ለዚህ አብቅቶን ክፍል ሁለትን እንዲህ ይዘን መጥተናል ይከታተሉን። ያስጀመረን በሰላም ያስፈጽመን!

ክፍል ፪ እንዲህ ይቀጥላል፡ ማስተዋሉን ይስጠን!
ዩሴፍ፡- ሽማግሌዎች ወገን ስለነበር /ስለተወለደ/ ስሙን ብልዮስ ቄሳር ብለዉታል።ብልዮስ ቄሳር ጋስዮስ ቄሳርን ጋስዮስ ቄሳር አዉግስጦስ ቄሳርን ይወልዳል፤የአዉግስጦስ ቄሳር አመጣጥ እንግዲህ  ይህንን ይመስል ነበር።አነጋገሱ ደግሞ ህዝቡ በሀገራቸው አንድ ኃይለኛ ጠላት ተነስቶ አስቸገራቸዉ አጥፋልንና  እናነግስሀለን አሉት፡፡ እርሱም ኃያል ስለነበር በኃይሉ ተማምኖ ከአነገሣችሁኝ እሺ  በእጄ ብሎ አጥፍቶላቸዋል፡፡  እነርሱም ቃል  እንደገቡለት አንግሰውታል፡፡በቃ…..
-ታዲያ አውግስጦስ ቄሳር ሕዝቡ እንዲቆጠር ያደረገው ለምንድነው?
ዩሴፍ፡- ከእርሱ በፊት የሶሪያ አገረ ገዥ የነበረው ቄርኒዎስ አስቆጥሮ ነበርና እርሱም በሮም ውስጥ ሊያስቆጥር ችሏል፡፡  እኛም ለመቆጠር በቅተናል፡፡
-ወደዚህ ቆጠራ ስትሄድ አብራህ ማሪያም የምትባል እጮኛህ እንደነበረች ይነግራል ፡፡  ይህ አንዴት ነው?
ዩሴፍ/-   አዎ/ እጮኛዋ/ጠባቂዋ/ የነበርኩት እኔ ስለነበርኩ የማይካድ ነው፡፡  አብራኝ በቆጠራውም ላይ ከዚያም በኋላ ልጇን ወልዳ ከዚያም ደገሞ ስተሰደድ አብራኝ ነበረች፡፡ እንዲያውም እነሰሎሜ የዓይን እማኞች ናቸው፡፡ እዚያው ሣለን ነበር ምጧ መጥቶባት ልትወልድ የደረሰችው፡፡
-እሺ አባታችን እንግዲህ እስካሁን የጥያቄያችንን መንደርደሪያ ወይም የታሪኩን የስር መሰረት ነበር ስታጫውተን የነበረው አሁን ደግሞ ወደ ዋናው ጉዳያችን እንመለስና ያንን የስደት ጉዞ እንዴት ነበር ያሣላፍከው? ብትብራራልን፡፡
ዩሴፍ፡- እንግዲህ ስለጉዞ ብዙ  ካልኩህ እኔንም አንተንም ደስ ባለን ነበር፣ በቃላት መግለጹ ግን በዓይን እነዳዩት  እና እንደተሣተፉበት አይሆንም፡፡ለማንኛውም ግን፡- (ቅዱስ ዮሴፍ እጅግ በሃዘን ተዋጠ) ጉዞው በጣም ግራ የሚገባ ነበር፡፡  ሳላስበው ድንገት ነበር ማሪያምን ይዤ እንድጓዝ በመልዐኩ በኩል ትዕዛዝ የተላለፈልኝ እንኳን ላልተወሰነ ወራት የሚጓዙት አስፈሪ ጉዞ/ስደት/ይቅርና የመጓዝ /የመሰደድ/ አቅም አልነበረኝም፡፡  ነገር ግን እንደፈራሁት ሳይሆን አብሮን የነበረው ኤልሻዳይ /ሁሉን ቻይ/ ህጻን ብዙ ተአምራትን እያደረገ ስንጓዝ በኋላም ተወልዶ ካደገና ብዙ ተአምራትን እያደረገ ሲያበረታታንና ሲያጽናናን ደሰታ እየተሰማን ነበር የተጓዝነው፡፡
-ቅዱስ ዩሴፍ ስለጉዟቸው ከነገረን ወዲያ ቅድስት ሰሎሜንም አግኝተን  ቅድስት ሰሎሜ መቸስ ከስደቱ ከነበሩት መካከል ሴት አንቺ ብቻ ነበርሽ ህፃኑ ሲወለድ እናቱ አንደ ሴቶች ልማድ የሚያስጨንቅ ምጥ ነበረባት? ብለን ለጠየቅናት እንዲህ  ብላን ነበር፡-
ሰሎሜ፡- በእርግጥ ሴቶች ህፃኖቻቸውን ሲወልዱ/ ሲገላገሉ/ በጣም የሚያስጨንቅ መዉለድን የሚያስጠላ ምጥ ያጋጥማቸዋል፡፡ ይህ የሴቶች ልዩ ስጦታ/ባህሪ/ነው፡፡ በማርያም ግን እንኳን የሚያስጨንቅ ምጥ ይቅርና የሚያረጋጋ እና የሚያሰደስት ምጥ እንኳን ቢኖር (ፈገግ እያለች)አላጋጣማትም::ዩሐንስ በራዕዩ ስለእመቤታችን በራዕይ 12፣1-17 በምሣሌ ስለእመቤታችን የጻፈውና “በምጥ ተይዛ ስትወልድ ጮኸች...” ማለቱ በሌሎች የሴቶች ልማድ ማናገሩ ነው እንጂ በእመቤታችን ይህ ሁሉ የለባትም፡፡
ምክንያቱም በማህፀኗ የተጸነሰው አምላክ ወልደአምላክ አስጨንቆ በምጥ፣ በጣር፣ በጋር የሚወለድ ሣይሆን ምጥን ጣርን ጋርን የሚያስወግድ: የድንግልና በሯን ሳይከፍት/ክብረንጽህናዋን/ ሳይጓድል እንደገባ  ሳይከፈት የሚወጣ ነው፡፡
ነቢዩ ህዝቅኤል እና ኢሣይያስ ያሉትን አልሰማህም እንዴ ህዝቅኤል “...ይህ በር ተዘግቶ ይኖራል እንጂ አይከፈትም…” ያለው በር እኮ ማህፀኗን /ድንግልናዋን/ ነው፣ ታዲያ ሣይከፍት ገብቶ ሣይከፍት ከወጣ ምጥ ከምን ይምጣ? ህዝቅኤል 44፣1
ደግሞም ምጥ በእርግማን ምክንያት የመጣ ነው፡፡ ሔዋንን “በፀነስሽ ጊዜ ጭንቅሽን አበዛዋልሁ፡ በጭንቅ ትወልጃለሽ፣” ዘፍጥረት 3፣16 ተብላ ነበር፡፡እመቤታችን ግን የአዳም ኃጢያት በዘር ያልተላለፈባት ከመርገመ ሥጋ ከመርገመ ነፍስ ነጻ የሆነች ንፅህት: ቅድስት ናት ስለዚህ ምጥ የሚባል ነገር አላያትም፡፡
-ቅድስት ሰሎሜ አንቺስ እንደ ሴትነትሽ መጠን መቸስ ብዙ መከራን ከህፃኑ እናት ጋር በስደቱ ወቅት ተቀብለሻል የፀሐዩ ዋዕይ የሌሊቱ ቁር ረሀብና ጥሙ ቀላል  አልነበረም፡፡  ታዲያ ይህ ሁሉ እንዴት አደረገሽ?
ሰሎሜ፡- ያልከዉ ከእዉነት ያልረቀ ሀቅ ቢሆንም እንደስጋችን ድካምና እንደ ሴትነቴ ቢሆን የማይቻል ነበር፤ነገር ግን ስደታችን ኃያልና ኃይልን ከሚሰጠዉ ጋር ስለነበር ስደታችን ምንም አልተሰማኝም።
-ጥያቄ እያበዛሁብሽ ከስደቱ ይልቅ እኔ ሳላደክምሽ አልቀረሁም ፤ ለመሆኑ ስደቱን ጨርሳችሁ ከግብጽ ስትደርሱ የተሰማሽ ምንነበር?
ሰሎሜ፡- መጀመርያ ስደትን ስለማላዉቀዉ ገና ስጀምር ወይም ስንሰናደድ ፍርሃት ነበረብኝ፤ ነገር ግን አብሮን የነበረዉ የኢሳይያስ ህጻን አይዟችሁ እያለ የሚያጽናናን ስለነበር ፍርሃት ድካም ሰቆቃዉ ተወግዶ ብርታት ለማግኘት ችያለሁ። ስንመለስ ያለዉን ደስታ እንዴት እንደነበር በምን አይነት ቃላት እንደምገልጽልህ ግራ ይገባኛል። የደስታ ምንጩ ጋር ቁጭ ብዬ እንዲህ ነበር ብዬ እንዴት ልንገርህ? አንደኛ የመከራዉ መገባደድ ያስደስተኛል፡ በሁለተኛ ደረጃ ራሱ ህጻኑ ልጅ ሆኖ ሳለ በዚያ እድሜ ድንቅ ድንቅ ተኣምራትን ሲሰራ ያስደስተኛል። ከሁሉም በላይ ለማዳን ብለን ይዘነዉ የተሰደድነዉ ህጻኑ ራሱም ተርፎ እኛንም አትርፎ ለዚያች ሰዓት ነፍሳችንን ይዘን ወደ አገራችን መመለሳችን አስደስቶኛል። በአጠቃላይ የተሰማኝ ደስታ ነበር።  
ለመሆኑ ቅድስት ሰሎሜ አሁን ካልሽዉ መሃል ሕጻኑ የሰራዉ ተኣምራት እንዳስደሰተሽ ተናግረሽ ነበር የገለጽስሽልን፤ እስኪ በስደታችሁ ላይ ካጋጠሙሽ ተኣምራት መካከል ጥቂቱን ብትገልጪልን?
ሰሎሜ፡-ተኣምሩ ብዙ ነበር፤ቢሆንም ዋናዋናዉን ማስታወሻም ያለዉን አንዳንዱን እነግራችኋለሁ፡-ይኀዉም ጌታ በቤተልሔም በተወለደ ጊዜ ቤተልሔም በእሳት ቅጽር ታጠረች፡ አጋንንት እናያለን ብለዉ ቢመጡ መላዕክት በሐጸ እሳት እየነደፉ የማያስቀርቧቸዉ ሆኑ ሄደዉ ላለቃቸዉ ለዲያብሎስ ነገሩት እስቲ ተሸክማችሁ ዉሰዱኝ አላቸዉ፤ በኪሩቤል አምሳል እርሱም አራት ጸወርት አበጅቷልና ተሸክመዉ ይዘዉት ቢመጡ የማይሆንለት ሆነ። ከዚህ በኋላ ከሄሮድስ  ላከበት የእኔን ሥልጣን መንግሥት የሚቀማ ንጉሥ ተወልዷልና እርሱን ግደል (እንግደል) ብሎ ላከበት፤ እርሱም እነደምን ላድርግ ብሎ የምክር ቃል ይልክበታል፡- ለዚህማ ምን ቸገረህ ዓመት ተመንፈቅ ሁለት ዓመት የሆናቸዉን ሕጻናት ልብስናቀለብ እሰጣለሁና ሰብስቡልኝ ብለህ አዋጅ ንገር አለዉ፤ እነዳዘዘዉ አደረገ። በዚህን ጊዜ መልዐኩ ዮሴፍን ተነስ ሕጻኑንና እናቱን ይዘህ ሂድ ብሎታል። ከዚህ በኋላ ያላቸዉ ልጆቻቸዉን የሌላቸዉ ቀለብ እንቀበልበታለን እያሉ ልጅ እየተዋሱ ሂደዋል።እንደዚህ አድርገዉ 14ሺ ከ4 ሕጻናት አስፈጅቷል።ነገርግን ሕጻኑን/ጌታን/ ሊያገኙት አልቻሉም። ከዚያ በኋላ ግብጽ ወረደ ብለዉ ነገሩት፡አራት አለቃ ከነጭፍራዉ ሸልሞ ይህ የዕለት ሽልማታችሁ ነዉ፡ይዛችሁትያመጣችሁልኝ እንደሆነ ሙሉ ሽልማት እሸልማችኋለሁ ብሎ ሰደዳቸዉ።እነዮሴፍ ሲሄዱ ከጊጋር ቤት ሰንብተን ሄደናል፣ዮሳ የተባለዉም የዮሴፍ ልጅ ታሞ ከጊጋር ቤት ቀርቶ ነበርና የጊጋር ሰዎች አራት አለቃ ከነጭፍራዉ ይዛችሁ አምጡልኝ ብሎ ሰደደ ሲሉ ሰምቶ ከዚያ ተነስቶ ሲሄድ ሰይጣን ከመንገድ ቆይቶ ወዴት ትሄዳለህ? አለዉ፡፡ እነዚያማ ቀድመዉህ ሄደዋል ይህን ጊዜማ ገድለዋቸዉ ይሆናል፡ ተመለስ እንጂ ምን ያደክምሃል? አለዉ። አሁንም ሞተዉም እንደሆነ እቀብራቸዋለሁ ያሉም እንደሆነ እነግራቸዋለሁ ብሎ ኃይል ተሰጥቶት ፈጥኖ ደረሰባቸዉ። ዮሴፍና ማርያም ደክመዉ ወድቀዉ ጌታ አካሉ ቢወዛ እያጠብኩት ሳለሁ አግኝቶኝ እናንተ!ከዚህ በጤናችሁ አላችሁ? በዚህ ሕጻን ምክንያት አሁን በገሊላ በክንዷ ልጅ የታቀፈች ሴት አለችን? አለ። በዚህ ጊዜ ማርያም ደንግጣ ልጇን ከእኔ ተቀብላ የቀን ሐሩር የሌት ቁር የተቀበልኩብህ ከሞት ላላድንህ ነዉ? ብላ አለቀሰች።  
ልጇም ዩሳን አመጣጥህ ዋጋ የሚያሰጥ መልካም ነበር ነገር ግን እናቴን ስለአስደነገጥካት በምፅአት አስገብቼ ዋጋህን እስክሰጥህ ድረስ ይህችን ድንጋይ ተንተርስህ ተኛ ብሎት ከዚያ አርፋል፡፡ ከዚያ ተነስተን ስንሄድ ደርሰውብናል፡፡  ታላቅ ሾላ እንጨት ነበረች ሰውሪን ብንላት ከነአህያችንና ከነሰዎቻችን ተከፍታ ሰውራናለች እነርሱም አህያው ከውስጥ ሆኖ ቢያናፋ የአህያውን ጩኸት እየሰሙ ቦታው ጠፍቷቸው ሲዞሩ ሰንብተው አጥተውን ተመልሰዋል፡፡
ከዚያም ተነስተን እመቤታችን ከልመና ሔደች ሰይጣን የሰውን ልቦና እያፀናባት የሚዘክራት አጥታ ብትመለስ ሰብዓሰገል ያመጡላትን የወርቅ ጫማዉን ሌባ ወሰደባት ልመናም ሄጄ ላላገኝ የልጄን ጫማ አስወስድኩት ብላ ምርር ብላ አልቅሣለች በዚያን ጊዜ እንባዋ በል ፊት ላይ ፈሰሰ። ከዚህ በኋላ ጌታ ለቅሶዋን አይቶ ከድንጋይ ውሃ አፍልቆ አጠጥቶናል፡፡  አንድም ከዚያ ተነስተን ስንሄድ ከትዕማን ቤት ልመና ገብተን ስንለምን ትዕማን እመቤታችንን አይታ “ከወደየት መጥተሻል?” አለቻት እርሷም ከምድረ ይሁዳ አለቻት:“ደረቅ ኃይለኛ ብትሆኚ ይሆናል እንጂ እንዳንቺ ያለች ቆንጆ ከመጋረጃ  ትወጣለች?” አለቻት ዩሴፍም:- ለትዕማን “ለለማኝ ቢኖር ይዘከሩታል: ባይኖር ካለው ያድርስህ ይሉታል እንጂ እንደ ፍላፃ ልብ የሚወጋ ነገር ምን ያረግልሻል?” አላት፡፡  ኮቲባ የምትባል ወደል ባሪያ አለቻት ይህ የፍየል እረኛ እመቤቴን እንደምን ይናገራታል ብላ ደርቡን እያነዋወጠች ወርዳ እሱን በጥፊ መታው ጌታን ከእመቤታችን ነጥቃ ከምድር ጣለችዉ ጌታ ትዕግስት ልማዱ ነውና ዝም ብሏት ያለቅስ ጀመር  በዚህ ምርር ብላ አልቅሣለች ዕንባዋ በፊቱ ላይ ወርዷልና እንዲህ  አለ፡፡  እመቤታችን ልታነሣው ብትሔድ ዩሴፍ “ተዓምራቱን ይዩ አምላክነቱን  ይግለጽ ተይው አታንሽው” አላት፡፡
-       ትዕማንን ከነገረዶቿ ምድር ተከፍታዋጠቻት:
-       ቤተሰቦችዋም ጦጣ ዝንጀሮ እየሆኑ የገዛ ውሾቻቸው እያባረሯቸው ወጥተው ሄደዋል፡፡
-       ከጐረቤትም ጩኸት ሰምተው እንረዳለን ብለው ቢመጡ ግብር አበርነታቸውን አይቶ ከዚያው ደርሷቸዋል፡፡  ዩሴፍ  እንደአዛዥ እኔም እንደአበጋዝ ጌታ እንደ ንጉስ እመቤታችን እንደ ንግስት ሁነን ከቤቱ ገብተን መንፈቅ ተቀምጠናል፡፡
በመጨረሻም ከስደት ስንመለስ ከመንገድ ደክመን በረሃ ለበረሃ ስንጓዝ ፈያታዊ ዘየማንና ፈያታዊ ዘፀጋም የተባሉ ሁለት ወንበዴዎች አጋጥመውን በዚህን ግዜ  ሁላችንም ተደናግጠን ጌታን የተውልኝ መስሎኝ ልብሴን አውልቄ ሰጠኋቸው እነርሱም ስድስት ቀን ጠፍተንባቸው በሰባተኛው ቀን አግኝተውን ነበርና ምነው እስከ ዛሬ ታደክሙናላችሁ  አሁንስ እግዚአብሔር ከእጃችን ጣላችሁ አሉንና ሰብዓሰገል ያመጡለትን ስረወፅ ቀሚስ ያቺን  ወስደውብን  ከሄዱ በኋላ  እልፍ እንዳሉ ፈያታዊ ዘየማን እኒህ ሰዎች የቤተመንግስት ሰዎች ናቸው መሰለኝ አሳዘኑኝ እንመልስላቸው አለ፡፡  ነገር ግን የሚቀሙት በተራ ነበርና ተራዉ የፈያታዊ ዘፀጋም ስለነበር አይሆንም ብዙ ዋጋ ያወጣልኛል አለው ፈያታዋ ዘየማንም ከቤቴሌሔም  ጀምሮ እስከዚህ የቀማነው የአንተ ይሁን ይሄ የእኔ ይሁን ብሎ መልሶልናል፡፡
ጥጦስ ጌታን ከእኔ  ተቀብሎ ተሽክሞ ሰይፋን እየተመረኮዘ ሲሸኘን ተሰበረበት “ምነው ‘ወርቅ ላበደረ ጠጠር እህል ላበደረ አፈር’ እንዲሉ በጐ ብሠራ ሰይፌን ሠበርክብኝ” ብሎ አዘነ ጌታም “የተሰበረውን ሰይፍህን ከሰገባው አስገባው:” አለው እንዳለው ቢያደርግ ደህና ሆኖ አገኘው፡፡  እርሱም ደስ ብሎት “ይሄ ብላቴና ከደቂቅ ነቢያት ወገን ነው” አለ፡፡
ሌላው ደግሞ እንደ ኦሪት ስርዓት በስምንተኛው ቀን ወደቤተመቅደስ ይዘነው ሄደን ካህኑ ሊገርዘው ቢል ምላጩ ዉሃ ሆነ እንደገናም በገዛ ፈቃዱ ምላጭ ከሰውነቱ ላይ  ሳያርፍ ተገርዞ ታይቷል፡፡  እንግዲህ ካየኋቸው ተዓምራት መካከል ከብዙ በጥቂቱ ይህንን ይመስላል፡፡
-እኛም ከቅድስት ሰሎሜ ጋር ለሰፊ ስዓት አብረን ከተጫወትን በኋላ ወደ ቅዱስ ዩሴፍ ተመልሰን እንደዚህ ብለነው ነበር፡-በስደታችሁ ወቅት ወደ ኢትዮጵያ እንደሄዳችሁ ይነገራል መሄዳችሁ እዉነት ነው?

-ዩሴፍ፡- አዎ መሔዳችን እርግጥ ነው መሄዳችንም እኛ አውቀን ያደረግነው ነገር ብቻ ሣይሆን ትንቢቱም በነቢዩ ዕንባቆም ተተንብዩ ስለነበር ነው፡፡ ዕንባቆም 3፣3-7
“...እግዚአብሔር ከቴማን ቅዱስም ከፋራን ተራራ ይመጣል ክብሩ ሰማያትን ከድኖአል ምስጋናውም ምድርን ሞልቶአል፡፡  ፀዳሉም እንደ ብርሃን  ነው ጨረር ከእጁ ወጥቶአል  ኃይሉም በዚያ ተሰውሮአል፡፡  ቸነፈር በፊቱ  ይሄዳል የእሳት ነበልባል ከእግሩ ይወጣል፡፡……… የኢትዮጵያ ድንኳኞች ሲጨነቁ አየሁ የምድያም አገር መጋረጃዎች ተንቀጠቀጡ…”  ብሏልና በትንቢቱ መሰረት የፋራን ተራራ የተባለችን እመቤታችን ስትሆን ከፋራን ተራራ ይመጣል የተባለው ደግሞ የተወለደው ሕፃን/ኢየሱስ ክርስቶስ/ ነው፡፡  ድንኳን ደግሞ የሰደተኞች  ማረፊያ ነው፡፡ “…የኢትዮጵያ ድንኳኖች ሲጨነቁ አየሁ”የሚለው ዐረፍተ ነገር የእመቤታችን ስደት ወደኢትዩጵያም እንደምንሄድ የሚያመለክት ነበርና ስለዚህ ተጉዘናል፡፡
ለጊዜው ከቅዱስ ዩሴፍ ጋር ያለንን  ቃለመጠይቅ ማገባደጃ የመሰልንን ጥያቄ ለዚህ ትውልድ ካያችሁት ከምታውቁት የምታስትላልፋት ምን መልዕክት አላችሁ? ብለን ጠይቀናል፡፡  እነርሱም ከተመካከሩ በኋላ በዩሴፍ አማካይነት እንዲህ ብለውናል፡፡

ዩሴፍ፡- እኛ የምንለው ብዙ ነገር አለም የለምም ምክንያቱም ትውልዱብዙ ያውቃልና፡ አንድም በሌላ መልኩ ማወቅ ደግሞ የእግዚአብሔርን ማንነት ሊያሳውቀው እግዚአብሔር ከሚያድለው ክብር ስላላደረሰው እኛ የምንለው ይህ የተወለደው ሕፃን ፍፁም አምላክ ፍፁም ሰው መሆኑ ቀርቶ ሰው ብቻ ነው ብለው እናቱንም ወላዲተ ሰብዓ ብለው የሚረዱ ሰላሉ አምላክነቱን ለማረጋገጥ እንዲችሉ ከፅንሰቱ ጀምሮ እስከ ልደቱና ከዚያ በኋላ  ስላለው ፍፁም አምላክነቱ ኢሳይያስ ከ740 ዓመት በፊት ፅፎት የነበረው የትንቢት ቃል መመልክት መልካም ነው፡፡ ኢሳ7፣14 ማቴ፣1፣23 የተወለደው ሕፃን አማኑኤል የተባለው ቢወለድም አምላክ  በመሆኑ ስጋን ነስቶ ፍፁም ሰው መሆኑን ስለመገለጥ ነበር፡፡  ከዚህ ሌላ አሁንም በትንቢት… ሕፃን ተወልዶናልና…. ስሙም ድንቅ መካር ኃያል አምላክ የዘለዓለም አባት የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል፡፡ የሚል ቃል እናገኛለን፡፡  ኢሳ 9፣6 በቤተልሔም ዋሻ ሰብዓ ሰገል ወርቅ ዕጣን ከርቤ መብዐ አድርገው ያቀረቡላት እኛ  የሰገድንላት ከብቶቻችንም በትንፋሻቸው ያሟሟቁት ሕፃን ኢየሱሰ ክርስቶስ አምላክ ስለሆነ ስሙም ኃያል ተብሎ እንደሚጠራ ልንመክራቸው እንወዳለን፡፡

-       ከስደቱ እንዴት ነበር ልትመለሱ የቻላችሁት? ብለን ጥያቄ አቀረብንለት
-       ዩሴፍም፡- ተነስተህ ብላቴናውንና እናቱን ይዘህ ወደምድረ እስራኤል ተመለሰ የዚህን ብላቴና ነፍስ ለማጥፋት የሚሹት ሰዎች ጠፍተዋልና…  ብሎ መልዐኩ ስለነገረን ነዉ፡፡
-       እነዚህ የጠፉት እነማን ነበሩ?
-       ዩሴፍ፡- ዩሐንስ በፊጥሞ ደሴት ታስሮ በራዕይ ካየው ራዕይ 12፣1-6 የተጻፈውና ዩሐንስ ዘንዶው እያለ የሚጠራው አጋንንት ያደሩበት ሄሮድስ  ነው፡፡
-       መቸስ ይህንን ሁሉ ከመነጋገራችን በፊት የልደቱን ቀን ነበር ማወቅ ያለብን ለመሆኑ መቼ ነበር የተወለደው?
-       አስቀድሞ ትንቢት እንደተነገረለት ያ አምስት ቀን ተኩል ሲፈጸም ነዉ፤ በኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር /በ5500/ በአንድ ዓ.ዓ.  በዘመነ ማቴዎስ በታህሣሥ  29  ቀን ማክሰኞ ከሌሊቱ 10 ሰዓት ላይ ነበር፡፡
-       አስቀድመን በጉዞአችሁ ያደረገውን ተዓምራት ነግራችሁናል በዕለተ ልደቱ የተደረገውን ብትነግሩን? ስንላቸው እነርሱም፡--
-       1. የተወለደበት ሰዓት ሌሊት ሲሆን ብርሃን ከሰማይ ወርል ምክንያቱም መላዕክት ለእረኞች ሲናገሩ አይተዋል ሉቃስ2፣39
-       2.  የእግዚአብሔር መልአክ መጥቶ ለከብቶች ጠባቂዎች ክርስቶስ መድኀን ተወልዶላችኋል ብሎ አብስሮአቸዋል ሉቃስ 2፣10
-       3.  ብዙ መላዕክት ከሰማይ መጥተው አመስግነዋል ሉቃስ 2፣13-14
-       4.  የባቢሎንና የፋርስ ነገስታትም አንድ ላይ መልዓክ እየመራቸው ወደ ቤተልሔም መጥተው ህፃኑ ኢየሱስን አግኝተው ሰግደው ወርቅ ዕጣን ከርቤ ግብር አቅርበውለታል ማቴዎስ 2፣1-12 መዝሙር 71፣10 ብለው ነገሩንና እኛም ቀጥለን ወደ ቅዱስ ስምኦን እና ወደ እመቤታችን  ነበር የሄድነው፡፡
-       አባታችን ቅዱስ ስምኦን እንደሰማነው ከሆነ እና አንተም ከሥራችን ሰዓት ውጭ እንዳጫወትከን ይህ ያሁኑ ቁመናህ ጥንት ያልነበረና ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እንደሆነ ነበር የነገርከን ይህ እንዴት  እንደሆነ ብትነግረን?
ስምኦን፡- ታሪኩ ብዙ ነው እንደው ጥያቄያችሁን ለመመለስ ያህል በአንድ ወቅት የነቢያትን የትንቢት መጽሐፍ ለመተርጉም ተሰጥቶን ሣለ በመሐል ላይ አንድ ግራ የሚገባ ከአእምሮ በላይ የሆነ ነገር አጋጠመኝ፡፡
-ይቅርታ አድርግልንና በመሐል ገባንብህ ይህ ከአእምሮ  በላይ የሆነ ነገር ያልከውን ግልጽ ብታደርግልን?
ስምኦን፡- …ድንግል በድንግልና ትጸንሣለች.. ብሎ ኢሣይያስ የጻፈውን ነበር፡በእድሜዬ ድንግል ሴት ወልዳ አይቼም ሰምቼም ስለማላውቅ ግራ ተጋባሁ ድንግል የሚለውንም ብዕሲት /ሴት/ ብዬ ፃፍኩት በዚህን ግዜ እንቅልፍ ነገር አደረብኝና ተኛሁ ስንቃ ድንግል ተብሎ ተጽፎ አየሁት ለሶስት ግዜ እንደዚህ ካደረኩ በኋላ በሶስተኛው መልአክ ተገልጾ እንዲያውም ይህንን ነገር ሳታይ አትሞትም አለኝ፡፡ ለረጅም ዘመናት ቆይቼ /በጣም አርጅቼ/ ከአልጋ ላይ እንደ ትኋን ተጣብቄ ከተኛሁበት ሥፍራ ትንቢቱ ተፍጽሞ ሕፃኑ  በቤተልሔም በከብቶች በረት ተወልዶ በስምንተኛው ቀን ይዘውት ከኔ ዘንድ አመጡት፡፡ (የቅዱስ ስምዖን ፊት በጣም ያበራ ነበር ስለሁኔታዉ ሲያወራን)
§  ከዚያስ ይህ ድንቅ ነገር መፈጸሙን ስታይ ምን ተሰማህ: ምንስ አልክ?
ስምኦን፡-  ይህንን ድንቅ ነገር ስሰማ ደስታ ነበር የተሰማኝ በተለይ ግን ታቅፌው ሳበቃ ይንቀጠቀጥ የነበረው እጄ ሲፀና  የጐበጠው ወገቤ ሲቃና አንደትኋን ከአልጋ ተጣብቆ የነበረው ገላዬ ሲዝናና በጣም ነበር ደስታ የተሰማኝ ከዚያም በኋላ “አይኖቼ ማዳንህን አይተዋል በሰላም አሰናብተኝ”ብዬ ተማፀንኩት፡፡
በመቀጠልም እመቤታችንን  አነጋግርናት፡ ማርያም የታሪኩ ባለቤት እንደመሆ ብዙ የምናናግራት ነገር ነበር፡ ነገር ግን ለሌላ ጊዜ አቆይተነዋል፡፡ ላሁኑ ግን እንዲህ አልናት!
§  እመቤታች እኛ ሣናውቅ አንቺ አውቀሽ የማታደርጊልንና የማታስደርጊልን አንዳች ነገር የለም የልቦናችንን  ሃሣብ/ ጥያቄ/ ምንም እንኳን ብታዉቂ ከፊትሽ ከቆምን ዘንድ አባሐርያቆስ እንዳለሽ እኛም የምንለሽ አለን.. ድንግል ሆይ ርጉም በሆነ በሄሮድስ ዘመን ከእርሱ ጋር ካገር ወደ ሀገር ስተሸሺ ካንቺ ጋር መሰደዱን አሳስቢ፤ ድንግል ሆይ ከዓይኖችሽ በፈሰሰው እና በተወደደ ልጅሽ ፊት የወረደውን መሪሪ ዕንባ  አሳስቢ ድንግል ሆይ  ረሀቡንና ጥሙን ችግሩንና ኃዘኑን ከርሱ ጋር የደረሰብሽንም ጭንቅ ሁሉ አሳስቢ ...  ብለናት ነበር፡፡  እርሷም፡-
ማርያም፡- ልጄ ዳግም ለፍርድ ሲገለጽ በክብሩ  በመንግሥቱ  ያስባችሁ፡፡
                                                           አሜን! ይቆየን!

ማክሰኞ 23 ኦክቶበር 2012

የኢየሩሳሌም የመንፈስ ተጓዥ




የኢየሩሳሌም የመንፈስ ተጓዥ


…እነሆ ለሕዝብ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ደስታ
የምሥራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ ዛሬ በዳዊት ከተማ
መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ የሆነ መርገመ ሥጋ መርገመ
ነፍስ የሌለበት በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስ የሚያድል የዓለም
መድኃኒት የሚሆን የባህርይ አምላክ ክርስቶስ በዳዊት ከተማ
በዳዊት ባህርይ ተወልዶላችኋላና..
                                                                                                                                             አዘጋጅ ፡-ደረሰ ረታ
ዘመነ ጽጌ
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስትያን ስርአትና ደምብ መሠረት በየዓመቱ ከመስከረም 26 እስከ ኅዳር 6 ቀን ድረስ ወቅቱ ዘመነ ጽጌ ወይም ወርሐ ጽጌ  የሚባል ሲሆን፡ ይህ ወቅት በቤተክርስትያን ስርዐት መሰረት በየሳምንቱ ቅዳሜ ምሽት በዝማሬና በምስጋና ሊቃዉንተ ቤተክርስትያን እግዚአብሔርን እና እመቤታችንን ሲያመሰግኑ ያነጋሉ። ሊቃዉንቱ ምስጋና የዘወትር ስራቸዉ ቢሆንም ቅሉ ይህንን ወቅት ደግሞ በተለየ ሁኔታ ማኀሌተ ጽጌ በሚባለዉ ዜማ እመቤታችንን ሲያመሰግኑ ያድራሉ፤ የሊቃዉንቱ በረከት ይደርብንና እኛም በማብዛት ሳይሆን በማሳነስ፣ በማስረዘም ሳይሆን በማሳጠር እንዲህ በማለት እናመሰግናታለን።   

ድንግል ሆይ ለምስጋና በሚመች ቃላትና አንደበት አይደለም የማመሰግንሽ በረከሰ አንደበቴ ነዉ እንጂ፣ መላዕክት ዘወትር የሚያመሰግኑሽ ቅዱሣንም እንዲሁ በመራድና በመንቀጥቀጥ ያለማሰለስ የሚያመሰግኑሽ የእኔ ምስጋና እንደምን ያንስ ይሆን? ማርያም ሆይ ያንን በረሃ በጽምና በረሃብ ስለኔ  ሐጥያትና በደል ማቋረጥ ሳያንስሽ ማዘንሽ? በዚያ በበረሃ ለተንከራተቱት በበረሃዉ ሙቀት ለተቃጠሉት እግሮችሽ፣ ባዘንሽ ጊዜ ላነቡት አይኖችሽ፣ የበረሃዉ ግለት በፈጠረዉ ጽም የተነሳ ለደረቁት ከንፈሮችሽና ጎሮሮዎችሽ፣ ክብር ምስጋና ይገባቸዋልና አመሰግንሻለሁ።
  ድንግል ሆይ በደሌ ከአዳምና ሔዋን በደል እጅጉን ልቋልና፡ ነፍሴም ጎስቁላለችና የእናት ልመና ፊት አያስመልስ አንገት አያስቀልስምና ለበደሌ አሳስቢ!
ይህንን ወቅት አስመልክቶ መጠነኛ ዝግጅት እነሆ!!!!
                     በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ
አሜን
የኢየሩሳሌም የመንፈስ ተጓዥ
ክፍል ፩
    

-->
ማናችሁ ?ምንድናችሁስ? ስራችሁስ ምንድን ነው? ብትሉ፤ የሰው ልጆች ፍጥረት የመጀመሪያ የአዳም የልጅ ልጅ የሆን  የስላሴ አርአያ እና አምሣያ በስተምሥራቅ አፍሪካ ከምትገኝ ከኢትዮጵያ የፈለስን ስንሆን፣ስራችን ታሪክ ፀሐፊነት ነዉ፡፡
ታዲያ እኔና የስራ ባለደረባዬ ለስራችን የሚያገለግሉንን መሣሪያዎች አንግተን የበረሀውን ንዳድ ታግሰን ከፊታችን ደረቱን አስጥቶ የሚጠብቀንን የተያያዘ ዳገት ስንወጣ የዘመኑ ቴክኖሎጂ ያላየውንና የፎቅ መውጫ መውረጃ/ሊፍት/ሳያስፈልገን ቁልቁለቱን ስንወርድ ከርመን የእግራችን አሻራ እስኪጠፋ  በመጓዝ በዚያን ጊዜ ዘመን ተቆጥሮለት ትንቢት ተነግሮለት ስለተወለደው ህጻን  የመወለዱን ዜና ለመዘገብ እንዲሁም ፈርኦን ሊገለዉ ያሳድደዉ ስለነበር ወደ ግብጽ ስለተሰደደዉ ስለዚሁ ህጻን ለማወቅ በመንፈስ ወደ ኢየሩሳሌም ተጉዘናል። ኢሣይያስ አማኑኤል ብሎ ከ740 ዓመት በፊት በትንቢት የተናገረለት ዩሴፍም በትንቢቱ መሰረት በተወለደ በስምንተኛው ቀን ኢየሱስ ብሎ  ስለሰየመው ድንቅ ነገር ለመጻፍ ከስፍራችን ይህ ምሥጢር ወደተፈጸመበት እና ወደሚያቁት ሰዎች አመራን፡፡
ታሪኩንም በደንብ ግልጽ ሆኖልን እንድናውቀው ትንቢት የተናገሩለትንም አንዳንድ የእድሜ ባለፀጋ በሕይወት ስለምናገኛቸው ከልደቱ ጀምረን ያለውን ለማወቅ የዳዊት ከተማ ወደሆነች በያዕቆብ ዘመን ኤፍራታ እየተባለች   ወደምትጠራዋ ከአየሩሳሌም ወደ ደቡብ   ዘጠኝ (9) ኪሎ ሜትር ርቃ ወደምትገኝ ቤተልሔም ተጓዝን፡፡
-ቤተልሔም ማለት የስሟትርጓሜ የእንጀራ ቤት ማለት ነው፡፡
የታሪኩን ሙሉ መረጃ ለማግኘት ያነጋገር ነው የባለታሪኩን እናት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያምን፣ ጠባቂዋ/እጮኛዋ/ የነበረውን የዕድሜ ባለፀጋ የሆነው ቅዱስ ዩሴፍን፣ በተተነበየለት ትንቢት መሰረት እስከዚያን ዕለት እና ከዚያም በኋላ የቆየውንና በጣም አርጅቶ ሳለ ህጻኑን ሲታቀፍ እርጅናው የታደሰለትን ስምኦንን የልደቱን ሁኔታ ለማየት በሰዓቱ ከሩቅ ምስራቅ መጥተው የነበሩ ሰብዓ ሰገልን እና እረኞችን እንዲሁም  የአካባቢዎች ሰዎች ነበር፡፡
ለመጀመሪያ ጊዜ ግን ያመራነውናጥያቄያችንን ያነሣነው ለሰብዓ ሰገል እና ለእረኞች ነበር፡፡  ከሁሉም በፊት የምናምንበትን ፈጣሪ ስራችንን እንዲባርክ በጸሎት በመጠየቅ ነበር፡-
ቅድመ ዓለም የነበርክ ዛሬም ያለህ ዓለምንም አሣልፈህ ለዘለዓለም የምትኖር ያለትናንት ቀዳማዊ ያለነገ ደሀራዊ የምትባል ጥንታዊ እና ቀዳማዊ የሆንክ በባህሪ ሞት በመንግሥትህ ሽረት የሌለብህ የሠራዊት ጌታ  እግዚአብሔር  አምላክ  ሆይ ራስህን ዝቅ በማድረግ በቤተልሔም በከብቶች በረት ውስጥ ከእናትህ ከድንግል ማርያም የተወለድህ ክብር ምስጋና ይድረስህ፡፡
በመቀጠልም የአምላክነቱ ድንቅሥራ ተደርጎላቸሁ በቦታው በመገኘት እና ታላቅ ምሥጢሩን ለማየት የታደላችሁ ቅድስት ሰሎሜ እና ቅዱስ ዩሴፍ እንዴት አላችሁ?እናንተስ በአካባቢው ሰዎች ዘንድ ተንቆ የነበረን ስራ በመስራት በእረኝነት ላይ ያላችሁ የሀገረ ገሊላ እረኞች ዛሬን እንዴት ደረሣችሁ? ሠላምታችንን እንዲህ ከጀመርን በሁላ ጥያቄያችንን የቀጠልነው እንዲህ በማለት ነበር፡፡
ከሩቅ ምሥራቅ ኮከብ መርቷችሁ ለአምላካችሁ እጅ መንሻን ለማቅረብ ወደጌታ ዘንድ የቀረባችሁ ሰብዓሰገል ከመንገዱ ብዛት የተነሣ ካልደከማችሁ አንዲት ጥያቄን ልጠይቃችሁ?
ዘጋቢው፡-ለመሆኑ ጌታ እንደሚወለድ እንዴት አወቃችሁ?
ከቦታችሁስ ስትነሱ ብዛታችሁ ስንት ነበር? ይህ መንፈሳዊ ጉዞአችሁሰ ስንት ቀን ፈጀባችሁ? እናንተስ በመላእክት አብሣሪነት መወለዱን ያወቃችሁ እና በእልልታና በዝማሬ ጌታችሁን ያመሰገናችሁ የሀገረ ገሊላ አረኞች፡ መወለዱን ሥትሰሙ ምን ያህል ደነገጣችሁ፤ በእውነቱ መወለዱን አይታችሁ ሥተመለሱስ የቱን ያህል ተደሰታችሁ?
ሰብዓሰገል፡- የጌታን መወለድ ያወቅነው ነበዩ ሚኪያስ በትንቢት ተናገሮ ስለነበረ በዚያ ምክንያት እና ጊዜውም መድረሱን በአባታቻን ጃንደራሽ ትምህርት አማካይነት ኮከቡን በማየት ነበር፡፡ ከቦታችንም ስንነሣ ከየነገዳችን ከካም ነገድ ሶስት እልፍ፡ ከሴም ነገድ ሶስት፡ እልፍ ከያፌት ነገድ ሶስት፡ እልፍ በአጠቃላይ ዘጠኝ እልፍ በመሆን ነበር፡፡
ጉዞአችንም ኮከቡን በምስራቅ እያየን በኮከብ እየተመራን ሄሮድስ በተንኮል እንደነገረን ሣይሆን በህልም መልዐኩ እንደነገረን በሌላ ጐዳና በመሄድ ነበር የደረስነው፤ ወዴት ነው? እያልን እንዳልመጣን አገኘነው እያልን ተመለሰን፣ ንጉስ አይሁድ ብለን እንዳልሄድን አምላክ መሆኑን አምነን/አውቀን/ተመለስን፣ ስንሄድ ድፍን ሁለት ዓመት ሙሉ እንዳልፈጀብን በ40 ቀናችን ሀገራችን ተመልሰን ገባን፡፡
እረኞች፡-  መወለድ የሚለው ቃል ምንም አያስደነግጥም ትንሽ ግራ የሚገባው እና የማያስደነግጠው ምንም እንኳን ትንቢት ተነግሮለት ዘመን ተቆጥሮለት ሱባዔ ተገብቶለት የተወለደ ቢሆንም የሰዎችን ልጆች ለመውለድም ሆነ ለመወለድ የሚያበቃ አምላክ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ ለዚያውም በከብቶች በረት መወለዱ ነበር ያሰደነገጠንና ግራ ያጋባን፡፡
መወለዱን አይተን ደስታውን እየተካፍለን ስንመለስ የተሰማን ደስታ ልክና መጠን የለውም ይህን ይመስላል፣ ይህን ያክላል አይባልም፡፡ አንልምም፡፡
---የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ ወዴት ነው ? እያላችሁ ስትመጡና ንጉስ ሄሮድስ ግቢ ስትደርሱ ንጉስ ሆኖ ሣለ ሌላ ንጉስ ወዴት ተወለደ ብላችሁ በመጠየቃችሁ አልፈራችሁም?
ሰብዓሰገል፡-ንጉስ ሲባል እንኳን ሠራዊቱን አልፎ ድርጊቱንና አስፈሪውን ፊቱን ታይቶ ይቅርና ስሙ ራሱ ሲጠራ በጣም ያስፈራል፡፡  ከዚያም ባሻገር ንጉስ እራሱን ሌላ እርሱን የሚተካ ከስልጣን የሚያወርደው ንጉስ የታለ ብሎ መጠየቅ ያስፈራል፡፡ ነገር ግን ነብዩ ኢሳይያስ እንደሚለው ኃያልነቱ በግፍ ተገዝተን ችግር ተደራርቦብን የኑሮ ጫና ወገባቸውን ያጐበጠውን የግፍ አገዛዝ የመረረንን ያስወግድልናል፣ ያቃናልናል፣ ከበታቹም ቀኝ አዝማች እና ግራ አዝማች ብሎ ይሾመናል፣ የቅርብ ወዳጆቹም የመንግስቱ አማካሪዎችም ያደርገናል ብለን አስበን ስለነበር የወደፊት ደስታችን/ተስፋ/የዚያን ሰዓቱን ፍራቻችንን አስወግዶልን ስለነበር አልፈራንም፡፡
-ሁለት ዓመት ሙሉ ተጉዛችሁ ቤተልሔም ዋሻ ስትደርሱ ምን ተሰማችሁ?
ሰብዓሰገል፡- መቸስ የእግር ጉዞ ስትጓዝ ምን ያህል አድካሚ እንደሆነ ልነግርህ አልችልም፤ እንኳን እኛ ህፃኑን ለማግኘት የተጓዝነው ቀርቶ እናንተ ይህንን ጥያቄ ለእኛ ለማቅረብ የፈለጋችሁትን ፍለጋ ብዙ እንዳደከማችሁ አይታችኋል፡፡  እኛ እንግዲህ ስንጓዝ አንድ ነገር ማለትም የምናገኘውን ንጉስ /አምላክ/ ተስፋ አድርገን ስለነበረ ተስፋው ያበረታን ነበር በተጨማሪም ይመራን የነበረው መልዐክ ስለሚያጽናናን አንዳች ፍራቻ የለብንም ። በጉዞአችን ያጋጠሙን ገጠመኞች ደስታ ስለነበሩ ከደስታው በቀር ሌላ የምናስታውሰው አንዳችም የለም፡፡እንግዲህ የተሰማን ደሰታ ብርታት ነበር፡፡
--አስቀድመን ጥያቄውን እንደጀመርንላቸሁ በቂውን መልስ ማግኘት የምንችለው ከእናንተ መሆኑንና በዕለቱም እንደነበራችሁ ተነግሮናል ይህ እንዴት ነበር?
እረኞች፡-የዚህን ታሪክ መፈጸም ልጆች ስለነበርን ከሰዎች ጋራ ስለማንገናኝ እንዲሁም ሁልጊዜ ውሉአችን ከከብት ጋር ስለነበር ምንም የምናውቀው ነገር የለም ነበር። ነገር ግን ድንገት ከብቶች እያገድን ሳለን ከሰዎች ወገን ያልነበረ ነጭ ልብስ የለበሰው መጣ፤ ወደኛ ዘንድም የሚያበራው ብርሃን እየቀረበን ሲመጣ ከታላቅ ምስጢርነቱም በተጨማሪ ልጅነትም ስለነበር ከመደናገጣችን የተነሳ ያቺን ዕለት ረገምን የተፈጠርንባትን ቀን እንደ ዕለተ ሞታችን አየናት መሬት ተስንጥቃ ብትዉጠን ተመኘን። መቸስ የዚያን ዕለት ፍራቻና ደስታ ምን ቃላት ይገልጸዋል እጅግ ፈራን እጅግም ደስ አለን፡፡
---ምን ደስ የሚያስኝና የሚያስፈራ ነገር አያችሁ?
እረኞች፡-እኛ እረኞች ስለሆንና በሰዎች ሁሉ ዘንድ የተናቅን ስንሆን ይህን ከሰው ወገን ያልሆነ ነገር ማየት እጅግ ያስፈራን ነበር (መልዐክ ማየታችን)፡፡  ምክንያቱም ለማጥፋትም ለመራዳትም ይመጣሉና፡፡
--ይህ ወደ እናንተ የመጣው ነጭ ልብስ የለበሰ መልዐክ ምን አላችሁ?
እረኞች፡- ይህ ግርማ ሞገሱ የሚያስፈራ መልዐክ ወደኛ ሲመጣ እንዲህ የሚል ቃል ነበር የተናገረን… …  እነሆ ለሕዝቡ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ደስታ የምስራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ ፤ ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ የሆነ መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስ የሌለበት፤ በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስ የሚያድል፣ የዓለም መድኃኒት የሚሆን የባህረይ አምላክ ክርስቶስ በዳዊት ከተማ በዳዊት ባህርይ ተወልዶላችኋልና  አለን፡፡  ለመልዐከ  ፍርሃት አርቆ መናገር ልማድ ነውና አትፍሩ አለን። ይህ ቃል ነበር በተለይ በጣም ደስ እንዲለን ያደረገው፡፡  ያው እኛም ስለተደናገጥን  ለተወሰነ ሰዓት በመካከላችን ዝምታ ሰፈነ ድንገት እንደመጣ ድንገት በአፋጣኝ ሁኔታ ተለይቶን ሣይሄድ መጠየቅ ያለብንን ጥያቄ አቀረብን ጥያቄውም እርሱ መሆኑን በምን ዓይነት ምልክት ማወቅ ይቻላል? የሚል ነበር እርሱም ለጥያቄያችን መልስ እንዲህ ሲል ነገረን … “….ሕፃን ተጠቅልሎ በግርግም ተኝቶ ታገኙታላችሁ” ብሎን ወደ መጣበት ሄደ፡፡ እኛም እርስ በርስ መልዐኩ የገለጠልንን ይህን የሆነውን ነገር ለማየት ወደቤተልሔም እንሂድ በመባባል ጉዞአችንን ወደ ቤተልሔም ቀጠልን፡፡
-ለመሆኑ ወደዚህ ወደተባለው ሥፍራ ሥትጓዙ ሁላችሁም ተስማምታችሁ ነው የሄዳችሁት? ምንም ችግርስ የለም ነበር?
እረኞች፡- መቸስ አንድ ነገር ሲታቀድ እንከን አያጣውም ገና ከመጀመሪያው ጀምሮ ፍርሀት  በውስጣችን ነግሶ፤  በመሐል ላይም አለመግባባት ተፈጥሮ ስለነበር ግማሾቻችን እንሂድ ስንል ግማሹ አይ አንሄድም ምን እንደሆነ አውቀን ነው የምንሄደው? መሽቶብናል፣ ስንቅም ጨርሰናል፣ አንሄድም የሚል አለ። ከፊሉ ደግሞ ይህ አሁን ተገልጾ የተሰወረው ያኔ አዳምን “… እኔ የብርሃን መልዐክ ነኝ” ብሎ ይዞ ከወጣ በኋላ ደም እንደ ጅረት እስኪፈሳቸዉ ድረስ የወገራቸው ሰይጣን ቢሆንስ ብሎ ያመነታ ነበር፡፡
--መጠርጠር መልካም ነው፡- ታዲያ በጨረሻ ምን ላይ ደረሳችሁ?
እረኞች፡-በመጨረሻ ሰዓት እግዚአብሔር የወደደውን እና የፈቀደውን ነውና የሚያደርገው ሁላችንም የምስጢሩ /የደስታው/ ተካፋይ ሆንን፡፡
-ወደእዚሀ ስፍራ ስትደርሱ ማንን አገኛችሁ?
እረኞች፡-  ይህንን ስፍራ ከዚህ ቀደም ምንም እንኳን ብናውቅም በዚህን ዕለት ግን በጣም ለየት ያለ ነበር፡፡  ቦታዋ እንኳን እጅግ ከብራለች ጸጋንም ተጐናጽፈለች፣ከዚህ ቀደም የምናዉቃት መንደር አትመስልም። በዚህ የተከበረ ስፍራ በሐመልማለ ሲና የምትመሰለዋን ምራገ ጸሎት የሆነች የህፃኑን እናት ማርያምንና ዩሴፍን ህፃኑን በግርግም/ በከብቶች በረት/ ተኝተው አገኘነው፡፡
----እንኳን እናንተ ተአምረኛውን ያገኛችሁ እኛ እናንተን ስናገኛ በጣም ደስታ ተሰምቶናል፡፡  እናንተስ ምን ተስምቷችሁ ነበር ምንስ አላችሁ?
እረኞች፡- መቸስ በልቦናችን የተሰማንን ደስታ ለመግለጽ  ቃላት አይገኝለትም ብቻ ባጭሩ ወደር የማይገኝለት ደስታ ተሰምቶናል፡፡ እንደደረሰንም በህፃኑ ፊት ፍግም ብለን ከሰገድን በኋላ ስለእርሱ የተነገረን ነገር ነገርናቸው ከመላዕክትም ጋራ አመሰገንነው፡፡
-እዚያ ስትደርሱ ምንም ችግር አላጋጠማችሁም ነበር?
እረኞች፡- አጋጥሞን ነበር አንድ ሀሩር የሚባል ሰው ህፃኑ የተወለደበትን ቦታ ላሳያችሁ ብሎ በልቡ ተንኮል አስቦ ወደሌላ ስፍራ ሊወስደን ቢል መላዕክት አንገቱን ቆርጠው ጥለዉት እኛም አንገቱን  ቅሌ/ገና/ ተጫውተንበታል፡፡
-እረኝነት ብዙ ሰዎች እነደተራ ይቆጥሩታል፡፡ እናንተስ እረኝነተችሁን እንዴት ትመለከቱታላችሁ?
-   እረኞች፡-  ሁሉም ነገር ክብደትና ቅለት የሚሰጠው እንደተመልካቹ እና እንደነገርየው ዓይነት ነው፡፡ እኛም ምስጢሩን ስንመለከት የዓለም ጠባቂ/እረኛ/ የሆነው የኢየሱስ ክርስቶስ ምሣሌ መሆን ማለት በጣም ትልቅ ክብር ነው፡፡  ስለዚህ ይህ ክብር ለእኛ በፍጹም የሚገባ አልነበረም፡፡  ታናናሾችን ከፍ የሚያደርግ አምላክ ግን ሁሉን አደረገ፡፡
-ለጊዜው ከእረኞች ጋር ያለንን ጥያቄ  በዚህ አቋርጠን አብረው ወደነበሩት ሰብዓሰገል ጥያቄአችንን እንዲህ በማለት ሰነዘርን፡-
እንግዲህ ባለፈው ስንነጋገር ከሩቅ ምስራቅ ለህፃኑ  ልትሰግዱ የመጣችሁት በነቢዩ ሚክያስ ትንቢት መሰረት እንደሆነና ስትመጡም ወደ ንጉስ ሄሮድስ ዘንድ እንደደረሣችሁ ነበር የነገራችሁን መንገዱም ሁለት ዓመት መፍጀቱን ነገራችሁናል፡፡ ለመሆኑ  ወደ እዚህ  ስፍራ  ስትመጡ ሁለት ዓመት በመጓዝ ከዚያ ደረሳችሁ ንጉስ ሄሮድስ ፈት ስትቀርቡ ህፃኑ ወዴት እንዳለ ሲነግራችሁ ያላችሁ ነገር ነበር?

ሰብዓሰገል፡-   ንጉስ ሄሮድስ ጋርም ስንደርስ ህፃኑን አገኝታችሁ ሰግዳችሁ ስትመለሱ መጥታችሁ ለእኔም ወዴት እንዳለ ንገሩኝና ሄጄ እሰግድለታለሁ ብሎ ነበር፡፡  እኛ ግን ስንመለስ በዚያ አልተመለስንም፡፡
ንጉሥ ሄሮድስ እኔም እንድሰግድለት መጥታችሁ ንገሩኝ  ሲላችሁ ለምን ነበር ያልነገራችሁት  ለምንስ በሌላ መንገድ ሄዳችሁ?
-ሰብዓሰገል፡-  “ሄጄ እስግድለታለሁ” የሚለው ቃል ደባን ያዘለ ቃል ነበረና፤ሊሰግድለት ሣይሆን ሊገለው ነበር ተመልሣችሁ ንገሩኝ ያለው ለዛብለን ነዉ። አንድም መልዐኩ በመጣችሁበት በኩል አትሂዱ ስላለን ነበር በዚያ ያልተመለሰነውና በሌላ መንገድ የሄድነው።
-ይመራችሁ የነበረው ኮከብ ሁለቱንም ዓመት ያበራ ነበር እንዴ?
ሰብዓሰገል፡-መንደር ሲገባ ከሰው ሥንገናኝ ይሰወራል፡፡  በረሀ በረሀውን ስንጓዝ ግን አቅጣጫውን ይመራን  ነበር፡፡
- ከዚህ ቀደም አመጣጣችሁ ከወዴት ነው ስንላችሁ ከሩቅ ምስራቅ እንደመጣችሁ ነበር የገለጻችሁት ከሩቅ ምስራቅ ስትሉ ከየት ከየት አካባቢ ነበር?
-ሰብዓሰገል፡- ከብዙ ቦታ ቢሆንም ልብ አምላክ ዳዊት በትንቢቱ፡- “በፊትም ኢትዮጵያ ይስግዳሉ ጠላቶቹም አፈር ይልሣሉ” መዝሙር 71፣9 የሚል ስላለ ከኢትዮጵያም የመጣን ነበርን፤



-->
-ሰብዓሰገልንም በዚሁ መልኩ ጥያቄአችንን ካቀረብንላቸው በኋላ በቀጣዩ ደግሞ በስደቱ ላይ አብረው ወደነበሩት አምርተን ቅዱስ ዩሴፍን ቀዳሚ ተጠያቂ አድርገናል፡፡  በዘመኑ ወደነበረው ቆጠራ ሄዶ ስለነበር ለምን እንደሄደ  ላነሳንለት ጥያቄ እርሱም እንዲህ ሲል መልሶልናል፡፡
..ዩሴፍ፡- ለቆጠራ የሄድኩት ሰው ሁሉ ይቆጠር ዘንድ ለ41 ዘመናት በሮም የነበረ አገረ ገዥ አውግስጦስ ቄሳር ባወጣው ትእዛዝ መሰረት ለመቆጠር ነዉ፡፡
--ለ41 ዘመን በሮም ላይ አገረ ገዥ የነበረው የአውግስጦስ ቄሳር ማን ነዉ እንደሆነ ብትነግረን?
ዩሴፍ፡- አባቶቻችን ፡ውሃ ከጥሩ ነገር ከስሩ ይላሉ እኔም ታሪኩን ከስር መሰረቱ ልንገራችሁ ድሮ ያኔ የሮም ንጉስ  ከአንድ ጐልማሣ ሚስት ዘንድ ያለፈቃድዋ ደረሰባት/ደፈራት/ ባልዋን  ከልብ የምታፈቅር ሴት ነበረችና ያለፈቃድዋ ሌላ ወንድ ስለደረሰባት ታንቃ ሞተች፡፡ ወንድሞቿ እህታችን የሞተችው በእርሱ ምክንያት ነው ብለው ከቤተ ጣዖት ገብቶ ሲወጣ አንቀው ገደሉት፣ ኋላም ሕዝቡ እርሱም እርሷም የሞቱት አንድ ሰው ኃጢያት ሲሰራ ዝም ስላልን አይደለምን? ብለው ነገር የሚወስኑላቸው 120 ሽማግሌዎች ሾመዋል፡፡ ከ120 ሽማግሌ የአንዱ ሽማግሌ ሚስት ጸንሣ ሳለች በምትወልድበት ግዜ ሞተች ገንዘን እንቀብራለን ሲሉ ጽንሱ በማህጠኗ ተንቀሣቀሰ፣ ሕያውን ከምውት ጋር እንቀብራለን? ብለው ሆዷን ቀደው አወጡት አደገ ኃያልና ምሁር ሆነ፡፡  በስተመጨረሻም ሁሉንም አጥፍቶ ለንግስና በቅቷል ታሪኩ እንዲህ ነበር፤ተረዳችሁ?
- አመጣጡን ና አነጋገሱን እንዴት እንደነበር ግልጽ ብታደርግልን?
ዩሴፍ፡- ሽማግሌዎች ወገን ስለነበር /ስለተወለደ/ ስሙን ብልዮስ ቄሳር ብለዉታል።ብልዮስ ቄሳር ጋስዮስ ቄሳርን ጋስዮስ ቄሳር አዉግስጦስ ቄሳርን ይወልዳል፤የአዉግስጦስ ቄሳር አመጣጥ እንግዲህ  ይህንን ይመስል ነበር።አነጋገሱ ደግሞ ህዝቡ በሀገራቸው አንድ ኃይለኛ ጠላት ተነስቶ አስቸገራቸዉ አጥፋልንና  እናነግስሀለን አሉት፡፡ እርሱም ኃያል ስለነበር በኃይሉ ተማምኖ ከአነገሣችሁኝ እሺ  በእጄ ብሎ አጥፍቶላቸዋል፡፡  እነርሱም ቃል  እንደገቡለት አንግሰውታል፡፡በቃ…..
-ታድያ አዉግስጦስ ቄሳር ህዝቡ እንዲቆጠር ያደረገዉ ለምንድን?
ይህንን እና ሌሎችን ቀሪ ምሥጢር በክፍል ሁለት እንዳስሳለን፤ በመንፈስ አብራችሁን ስለተጓዛችሁ እያመሰገንን ለክፍል ሁለት ያበቃን ዘንድ ጸልዩ። መልካም የጽጌ ዘመን ይሁንልን፣ ይቆየን።

ጦማሩን ስለጎበኙ አመሰግናለሁ!

መልካም ነገርን ለሌሎች ማጋራት ባህላችን እናድርግ፤ ላልደረሰዉ በማጋራት ድርሻችንን እንወጣ፡፡

ትቶ እና ችሎ

  ትቶ እና ችሎ ብጹእ ወቅዱስ አቡነ መርቆርዮስ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ በደረሰ ረታ ብጹዕነታቸው ለሶስት አሥርት አመታት እኛ በማናውቀው እግዚአብሔር በሚያውቀው በብዙ መከራ በብዙ ፈተና ውስጥ ነው ያሳለፉት። ...