ቅዳሜ 3 ኖቬምበር 2012

ይቅርታ!


 ‹‹ዘመኑ እ.ኢ.አ 1972 ዓ.ም ነው፡፡ ረጅሙ ሌሊት አልፎ አዲሱ ቀን ሰኔ 8 ሊነጋጋ ቀርበዋል፡፡ ሽምቅ ተዋጊዎች በሰሜን ቬትናም ግዛት ውስጥ እየተሽሎከለኩ እልህ አስጨራሽ ውጊያቸውን ተያይዘውታል፡፡
        በዚያን ቀን ሰኔ 8 1972 ዓ.ም ጠዋት በነዛ መንደሮች ላይ ከሰማይ ያናባል ቦንብ መዐት ወረደባቸው ፡፡ እነርሱም እንደ ሚፍለቀለቅ እሳተ ጎመራ ሆነው መንቀልቀል ጀመሩ፡፡ በምንም አይነት መንገድ ከዚህ እሳተ ጎመራ ውስጥ ማንም ማውጣት እንደማይቻለው ቢታወቅም ታምእራዊ በሆነ መንገድ በቁጥር አምስት የሚሆኑ ሕፃናቶች ከሚንቀሳቀሰው እሳት ውስጥ አምልጠው እየሮጡ ሲወጡ ታዩ፤ ከእነርሱም መካከል አንዷ ትራንግ ባንግ ከሚባለው መንደር አምልጣ የወጣች የዘጠኝ ዓመቷ ሕፃን ፋን ቲህ ኪምፋክ ነበረች፡፡ ኪም ፋክ ቦንቡ ጀርባዋን እና ክንዶቿን ጎድቷት ስለነበረ እና የለበሰችውን ልብስ በእሳት ተቀጣጥሎ ስለነበር፤ ልብሷን አውልቃ እራቁቷን ለመሮጥ ተገደደች፡፡
        በዚህ አሳዛኝ ሁኔታ ውስጥ ጦርነቱን ይዘግቡ የነበረው የአሶሴቲድ ፕሬስ ጋዜጠኛ ካሜራውን አነጣጥሮ እየተቃጠለች እራቁቷን የምትሮጠው ኪምን በመቅረጽ ምስሉ ቀርጾ አስቀራት፡፡ ኪም ወደ ጋዜጠኛው እና በሱ ዙሪያ ወዳሉት ወታደሮች ስትደርስ ‹‹ተቃጠልኩ! ተቃጠልኩ! ‹‹Nong qua, Nong qua,”    ‘too hot, too hot” እያለች ታለቅስ ነበር፡፡
        … ጋዜጠኛው ከምንና አብረዋት የተረፉትን ህፃናት ሳይጎን ወደ ሚባል ከተማ ወስዶ በሆስፒታል ውስጥ እርዳት እንዲሰጣቸው አደረገ፡፡ ኪም ብዙ የቦንብ ፍንጥርጣሪ በሰውነቷ ውስጥ ስለገባ በሆስፒታል ውስጥ ባደረገቸው የ14 ወር ቆይታ 17 ጊዜ ወደ ቀዶ ጥገና ተደርጎላታል፡፡ ደስ የሚለው ነገር ኪም ከዚህ ሁሉ ስቃይ እና መከራ በኋላ ድና ወደ ኅብረተሰቡ ተቀላቅላለች፡፡
        ዶ /ር ኪም ፉክ አሁን በካናዳ አገር እርሷ የተባበሩት መንግስታት የሰላም መልክተኛ ናት›› ትልቅም የሕጻናት መረጃ ማዕከል በስሟ ከፍታለች፡፡ የሁለት ልጆችም እናት ናት፡፡
        …. ጆን ፕሎሚር ፤ ኪም ካናዳ እንዳለች ሰማ ፈልጎም አገኛት›› ብዙ ሕዝብ በተሰበሰበበት በኪም ፊት ተንበርክኮ እዲህ አላት ‹‹ኪም ፉክ ያንን ሁሉ ጥፋት እንዲሆን ትዕዛዙን የሰጠሁት እኔ ነኝ›› በሰራሁት ነገር ተጸጽቻለሁ! ከመሞቴ በፊት አንቺን አግኝቼ ይቅርታ ልጠይቅሽ እመኝ ነበር፡፡ ስላገኘሁሽ እና ይቅርታ ልጠይቅሽ ስለቻልኩ በጣም ደስ ይለኛል፡፡ ኪም ይቅር ትይኛለሽ?...››      ኪም ህፃን ናት፤ ደግሞም ሰላማዊ ሰውናት፤ በተራንግ ባንግ መንደር ላይ የናፖል ቦንብ ሲጣል ብዙ ሰላማዊ ሰዎች በተገኙበት ተቃጥለው አልቀዋል፡፡ ኪም ወገኖቿን ሁሉ አጥታለች፤ የአደጋው ጠባሳ ዛሬም በገላዋ ላይ ይታያል፤ በሞት እና በሕይወት መካከል ሆና እርቃኗን ለዓለም ሁሉ ታይታለች ፡፡ በእውነት ኪም ጆን ፖሎሜርን ይቅር ትለው ይሆን?
        … ኪም በ1996 ዓ.ም በቬትናም ጦርነት መታሰቢያ ቀን ላይ እንዲህ ብላ ተናግራ ነበር፡፡ ‹‹ያለፈውን አንድ ጊዜ የሆነውን ነገር መለወጥ አንችልም! ነገር ግን እያንዳንዳችን ለወደፊቱ ሰላማዊነት ተባብረን ልንሰራ እንችላለን!!!››
እናም ኪም በፊቷ የተንበረከከውን ጆን ፕሎሜርን ብድግ አርጋ በማቀፍ እንባዋ በዓይኖቿ እየፈሰሱ ‹‹ይቅር ብዬሃለሁ!›› አለችው፡፡ ይህ ይቅርታ በዓለም ላይ በጦርነት ለተደረጉ በደሎች ሁሉ የተበደሉት ህዝቦች ይቅርታ ሆኖ ተመዘገበ ፡፡
‹‹ወንድምህ ቢበድልህ ገሥጸው÷ቢጸጸትም ይቅር በለው፡፡›› ሉቃስ 17፡3
       ይህን እውነተኛ ታሪክ ምንጭ ሆኖ ያገኘሁት መንገድ ላይ ትራንስፖርት እየጠበኩ ባለሁበት ሰዓት እንደነበር ከጋበዙኝ አንድ የእምነት ተቋም በራሪ ወረቀት ላይ ነው፡፡
        ‹‹ይቅርታ›› ለአለም ህዝብ ወሳኝ ጥልን ድል የምናደርግበት በእጅ የማይዳሰስ በዓይን የማይታይ መሳሪያ ነው፡፡ ታላቁ መጽሐፍ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲሁም ሌሎች መጽሐፎች ታላላቅ ሰዎች፣ ሙሁራን፣ የአገር ሽማግሌዎች፣የሃይማኖት መምህራን ዘወትር በጽሑፋቸውም ይሁን በትምህርታቸው የሚያነሱት አብሮ ርዕሰ ጉዳይ ነው፡፡ ዛሬም ፀሐፊው ማንሳት የፈለገው ስለዚሁ ዓብይ ጉዳይ ይቅርታ ነው፡፡
        ቅዱስ ጴጥሮስ ስለ ይቅርታ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሥለ ይቅርታ ሲጠይቀው እንዲህ ብሎት ነበር፡፡ ‹‹…..ጌታ ሆይ ወንድሜ ቢበድለኝ ስንት ጊዜ ልተውለት? እስከ ሰባት ጊዜን? አለው፡፡ ኢየሱስ እንዲህ አለው፡- አስከ ሰባት ጊዜ ሰበት እንጂ እስከ ሰባት ጊዜ አልልህም፡፡›› ይህ ቃል የሚያስመለክተን ከይቅርታ አስፈላጊነት ባሻገር ምን ያህል ጊዜ ይቅር ልንል እና ይቅርታ መጠየቅ እንዳለብን ነው፡፡
        ይህንን መሰረት በማድረግ ነው መሰለኝ የቀድሞው የኢትዮጵያ ቴሌኮሙኒኬሽን ኮርፖሬሽን የዛሬ ‹ኢትዮ ቴሌኮም? (እኔም ይቅርታ የአማርኛ ቃል ሥላልሠጡት አንድም መጠቀም ስላልፈለጉ የሥልጣኔ፤ የዕድገት ምልክት መሆኑ ነው መሰለን የእንግሊዘኛውም የተጠቀሙት እንዳለ ተጠቅሜአለሁ) መስሪያ ቤት መቼ እንደሚስተካከል የማይታወቀው የኔትወርኩን ችግር ‹‹¸ይቅርታ የደወሉላቸው ደንበኛ አሁን ማግኘት አይችሉም…..››፤ ‹‹sorry the network is busy …….››፤‹‹ይቅርታ ይቅርታ….›› ተጠቃሚውን ህብረተሰብ ያሰለች ትልቁ የቴሌኮም ችግር ነው ነገር ግን ሊቀርፈው ያልቻለው ከአሥር ዓመት በላይ ተሸክመነው የዘለቅነው ችግር ነው ምንም እንኳን መጽሐፍ በጥሬ ለ490 ያህል ጊዜ ሥህቱቱን ይቅር ማለት ቢገባንም የቴሌኮም ሥህተት በዛ፣ ይቅርታውም የምህረት ልመና ሳይሆን ማደንቆሪያ ከሆነ ሰነባበተ ምክንያቱም በሰላምና በጤና አጠገብዎ ያለውን ደንበኛ ‹‹ይቅርታ ›› ደንበኛዎን ሊያገኟቸው አይችሉም››፣ ይቅርታ መስመሮቹ ሁሉ ተይዘዋል፡፡›› ‹‹ይቅርታ ደንበኛው ከአገልግሎት መስጫ ክልል ውጭ ናቸው›› ወዘተ… ይባላሉ፡፡ እሺ እንደ መጽሐፉ ይህ ወዳጃችን ብቸኛው አገር በቀል ድርጅታችን በደለን ይቅርታ ጠየቀን መቼ ነው ተስተካክሎ ችግሩን አስወግዶ ‹ይቅርታ› መጠየቁን የሚያቆመው? ለነገሩ በኮምፒውተር የተቀረጸው (የተቀዳው) የድምጽ መልዕክት ለማደናገር (ለማደናቆር) ‹ይቅርታ› ትበል እንጂ ተቋሙ ለስራው ሥህተት ለበደለው በለድ የኢትዮጵያ ህዝብ ይቅርታ ጠይቆ አያውቅም፡፡
የበደሉትን ይቅርታ መጠየቅ፣ የቀሙትን መልስ ምህረት ማግኘት ትልቁ የኢትዮጵያን ሐብት ነበር፡፡ ዛሬ ግን ይቅርታ መጠየቅም ሆነ ይቅር ማለት ፋሽን ያለፈበት፣ ኋላቀር አስተሳሰብ እየሆነ ከመጣ ሰነባበተ፡፡ መምህራኑ ሃይማኖት፣ ሳይቀሩ ይቅር መባባልን፣ ምዕመናንን ይቅርታ መጠየቅ እንደ ውርደት እየቆጠሩት መጥተዋል፡፡ ቤተ እምነቶችንም የሚያስተምሩት የማያደርጉ መምህራን ማፍራት ከጀመረች ሰነባበተች ምዕመኑም ‹‹ይቅርታ አድርግልኝና….›› እያለ እያስፈቀደ ማስቀየም ጀምሯል፡፡ ‹‹ይቅርታ ይበለን እንጂ…›› እያለ ማማትንም የተቀደሰ ሥራ አድርጎታል ፡፡
ይቅርታ ያሥተማሩ ይቅርታንም በተግባር የተገበሩ በሥውር የበደሉትን በአደባባይ በአብራክ ህሊና ተንበርክከው ይቅርታ የጠየቁና አርአያ የሆኑ አልታጡም፡፡ አንዱ ጀግና ደፍሮ በአደባባይ ይቅርታ ሲጠይቅ ያጥፋም አያጥፋም ብዙዎችን ምሳሌ በመሆን አስተምሯል ብዙዎች ግን አንዱን ይቅርታ አልጠየቁም ዲ.ዳንኤል ክብረትን ምናልባት በደል አልተገኘባቸው ይሆናል፡፡ እርሱ ግን በአፈ መንፈስ ቅዱስ ይቅር መባል ይገባዋል፡፡ ይቅርታ ጠይቋልም ይቅርታንም አስተምሯልም፡፡ ኢትዮጵያዊው ጆን ፕሎሜር ያለጥፋት ወይም ጥቂት ጥፋት ትልቁን ይቅርታ የጠየቀ ትንሿ እርሾ ብዙውን ሊጥ ታቦካዋለችና፡፡
        በምድራችን በኢትዮጵያ ብዙዎች የጥቃት ሰለባ የሆነ በአካለ መጠን ጨቅላ የሆኑ በጦርነት የእሳት እራት የሆኑ ነበሩ፡፡ ሃማሴናውያን የት/ት ቤት ተማሪዎች፡፡
        በረሃብ አለንጋ ተገርፈው የረገፈ አሉ በ1977 ዓ.ም የኢትዮጵያ ድርቅ በበሽታ የሚሰቃዩና ህክምና በማጣት የሚረግፉና በጨቅላነታቸው የሚቀጠፉ ህጻናት ቁጥር የትዬለሌ ነው፡፡
        ወላጆቻቸውን በወባ፣ በቲቢ፣ በH.I.V. ኤድስ ያጡ የህፃናት ቁጥር ቤት ይቁጠረው……ወዘተ፡፡ ለዚህ ጥፋት፣ መነሻነት በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ የሰው እጅ አለበት፤ ታዲያ የትኛው ጀግና የይቅርታ መምህር ይሆን ‹‹…. ያንን ሁሉ ጥፋት እንዲሆን ትዕዛዙን የሠጠሁት እኔ ነኝ፡፡ በሰራሁት ነገር ተጸጽቻለሁ! …. ይቅርታ!›› በማለት ትውልድን ይቅርታ የሚጠይቅ? በህፃናት ሥም የሚመጣውን እርዳታ (ገንዘብ፣ እህል፣ መድሐኒት፣ ቁሳቁስ፣ ወዘተ…) ለሌላ ጉዳይ ወይም ለራሳቸው ጥቅም የሚያውሉ የመንግስትና የዓለም አቀፍ የእርዳታ ድርጅቶች ባለሥልጣናት የሆኑ?የሐይማኖት ትምህርት በማስተማር በዓለም ላይ ሰላምን በማምጣት የላቀ ሚናቸው መጫወት ሲገባቸው በዘረኝነትና በፖለቲካ ክፉ ሥራ ተጠምደው የህፃናቱን ለቅሶና ዋይታ፣ ህመምና ሥቃይ ወደ ጎን የተው የሃይማኖት መምህራንና መሪዎች ይሆኑ? በሥልጣን ጥማት የተነሳ የሥልጣን ዘመኔ ይራዘምልኝ፣ ሆዴ ይሙላ ደረቴ ይቅላ እያሉ እርስ በርስ ባለመስማማት ጦርነትን በህጻናት ላይ ሳይቀር የሚያውጁ ሰይፍ የሚመዙ ቦንብ የሚያፈነዱ መርዝ የሚረጩ የመንግስት ባለሥልጣናትና ጋሻ ጀግሬ(አጫፋሪዎች) ይሆኑ? ትርፉን በማሳደድ በቃኝን ባለማወቅና ያለኝ ይበቃኛል በጥቂቱ አትርፌ ህዝቤን ልጥቀም የሚል አስተሳሰብ በማጣት በየዕለቱ በህፃናት ምግብ፣ አልባሳት፣ የህክምና መድኃኒት…….ወዘተ ላይ ከፍተኛ ጭማሪን በመጨመር ሥቃያቸውን የሚያረዝሙት፣ ህመማቸውንና ጣራቸውን የሚያበዙት፣ ጩኸታቸውን፣ ለቅሶአቸውን፣ የድረሱልኝ ድምጻቸውን ….የመሥሚያ ጊዜ ያጡት ነጋዴዎች(መላው ህብረተሰብ) ይሆኑን? እንጃ ፣ የትኛው ወገን የእነ ኪምን ለቅሶ፣ ዋይታ፣ ሰቆቃ፣ ህመም፣ አልፎ ተርፎም ሞት በመስማትና በማየት ግፍ መዋል በቃኝ ያጠፋሁት ጥፋትና እልቂት፣በቃኝ እስከ ዛሬ ለነበረው ነገር ሁሉ ተጠያቂ እኔ ነኝ፣ …. ይቅርታ የሚለው የቱ ይሆን???
        ህፃናት እንዳ ኪም በጣሊያን ጦርነት፣ በግራኝ መሐመድና በዮዲት ጉዲት ጦርነት፣ አያት ቅድመ አያቶቻቸውን፣ በደርግና በወያኔ(ኢህአዴግ) ጦርነት፣ በኢህአዴግና በሻቢያ(በኢትዮጵ ኤርትራ) ጦርነት አባቶቻቸውን አጥተዋል ዛሬ በራሳቸው ዘመን ላይ በመሆን እነርሱን ለማጥፋት የጥፋት ኃይል እጁን ከጠብ መንጃ አፈሙዝ ላይ በማንሳት ህይወታቻቸውን ይታደጋቸው ጥፋትን ሳይሆን ምህረትን የሚያውጅ የፕሮፓጋንዳ ሥራን(አሉታዊ የሆነውን) በመሥራት ብቻ የተጠመደው ሰላምን በመስበክ ‹‹ተቃጠልን!››፣ ‹‹ተራብን››፣ ‹‹ታመምን››፣ ‹ወላጅ አልባ ሆነን››፣ ‹‹የሙቀት መጠን ጨመረብን››፣ ‹‹ንፁህ አየር አጣን፣››፣ ወዘተ የሚሉትን ጨቅላ ህጻና ወደ አስፈላጊውን ስፍራ ሊወሰዱ የተሰናዱ ጋዜጠኞች አገራችን ያሥፈልጋታል የሃሰት ሰይፋቸውን ጥለው እውነት የሚያወራ ብዕራቸው ሊጨብጡ ስለሰላም ስለ አንድነት ስለ እርቅ ሊዘምሩና ሊያሸበሽቡ ይገባል፤ ለባለሥልጣናትና ለባለጊዜዎች ማራገብ ይቅር፡፡ የጥፋት ኃይሎችን ገበና ያጋልጡ፡፡ በመምከርና በማስተማር ለህብረተሰቡም በማሳወቅ ከመንገዳቸው ይመልሱ፡፡
        በቤተ እምነቶች ካህናት፣ አስመላኪዎች፣ ሼኮች… ሥራቸውን በእውነት ላይ የተመረኮዘ ትውልድን የሚታደግ ለባለጊዜዎች የሚያደላ እና ህጻናት በተለያየ አቅጣጫ (በርሃብ፣ በብሽታ፣ በጦርነት፣ ወላጆቻቸውን በግፍ በማጣት፣ በዓለም ሙቅት ጨመር ምክንያት ሲጨነቁ …እና ሌሎች ህይወታቸውን የሚቀጥፉ እድገታቸውን የሚያጨናግፉ ነገሮች በመመልከት ተጠቂ ሲሆኑ ዝም ብሎ ከማየትና ዝምታን ከመምረጥ ለህጻናቱ ወግኖ መሟገት ለዚህ ዓለም የሚበጀውን ሰለምን መስበክ፣ ‹‹ኃጢአት መጥፎ ነገርን ብቻ ማድረግ ሳይሆን በጎ ነገር ማድረግ ሲችሉ አለማድረግም ኃጢአት ነውና፡፡››
        በህጻናት ዕልቂት ምክንያትነ ከተለያዩ አላማት ግብረሰናይ ድርጅቶች በልግስና ሥም የሚመጡትን እርዳታዎች (መድኃኒቶች፣ ገንዘቦች…. ወዘተ) ለግል ጥቅማቸው፣ ላልተፈለገ ምግባሮች (ለጦር መሳሪያ መግዣ፣ ለወታደሮች ማደራጃ ለቢሮ ህንጻ፣ ግንባታ ለባለሥልጣን የመኪና መግዣ የቢሮ ቄሳቁሶች (ቋሚ አላቂ እቃዎች) ፣ የተለያየ ክፍሎች ሥራ ማስፈጸሚያ በጀት) ማዋል ትልቅ በህጻናቶች ላይ የሚደርስ በደል ነው፡፡ ደረጃውን የጠበቀ የህጻናቶችና የወላድ እናቶች ማዋለጃና መንከባከቢያ ሆስፒታሎችን በማስፋፋት የእናቶችንና የህጻናትን ሞት መቀነስ ሲገባ የተያዘውን በጀት በባዶ ሜዳ በማስታወቂያ (ለትላልቅ ቢል ቦርዶች፣ማሰሪያ፣ለቴለቭዥንና ሬዲዮ ድራማዎች ማስታወቂያ እስፖንሰር ለተለያዩ ስብሰባዎችና ሥልጠናዎች ቲሸርትና ኮፍያ፣ ውኃና ኩኪሲ፣ ሻይ፣ ቡና ላይ…) ከማባከን ቀጥታ ከሞት የሚድኑበትን ተጠቃሚ የሚሆኑበትን ሥራ ቢሰሩ የተሻለ ብዙ ኪሞችን በሕይወት በማትረፍ፣ የነገ ትውልድ ተረካቢ ዜጎችን መፍጠር ይቻላል፡፡ የዛሬ ህጻናት የነገ ተስፋ ሰጪ ታሪክ ቀያሪ (ዶክተሮች፣ መምህራኖች፣ሰላም አስከባሪ ኃይሎች፣ ኢንጂነሮች፣ አርቲስቶች፣ ፓይለቶች፣ ሳይንሲስቶች፣ የፖለቲካ ሰዎች፣ የሀገር መሪዎች፣ በዓለም ላይ እርቀ ሰላም የሚያመጡ ብዙ ኒልሰን ማንዴላዎች፣ አብርሃም ሊንከንን ÷ወዘተ…) ማፍራት ይቻላል፡፡ ህጻናትን ልናደርግላቸው ከሚገቡት ጥቅሞቻቸው ባሻገር እያደረግንባቸው ጥቂቶችን እናቁም (ጉልበታቸውን ብዝበዛ፣ አስገድዶ መድፈር፣ ለሥዳትና ለጉዳና ተዳዳሪነት መዳረግ፣ ለልመና ማሰማራት….)
        የህጻናት አዕምሮን ባዶ ወረቀት አንድ ነውና መልካም ነገር እንቅረፅባቸው ዛሬ ያስፈርንባቸው ትንሽ መልካም ነገር የነገ የትውልድ ትልቅ ተስፋ ይሆናል፡፡ የዛሬ በደላችን ነገ ይቅርታ ያገኛልና፡፡ ዛሬ ጦርነት፣ ስደት፣ ርሃብ፣ ፍቅር ማጣት፣ ድኅነት፣በሽታ፣ ድርቅ… ያኩራመታት ዓላማችን ነገ በነዚህ አዲስ ተስፋ ስንቀው በሚመጡ ጨቅላ ህጻናት እንድታገግም፣ የተኳረፍን እንድንታረቅባት፣ የተከፋፈልን አንድ እንድንሆንባት፣ በጎን በቋንቋ በብሔር በቀለም በፖለቲካ፣ በሃይማኖት ተከፋፍለን የተበታተንነው አንድ ህዝብ አንድ አገር እንድንሆንባት በነዚህ አዲስ ትውልድ አዲስ ዓለም ለመፍጠር የተበላሸ ታሪክ፣ ውሸትን፣ ጠማማ፣ የፖለቲካ አካሄድንና አመራርን፣ ሥራ የተለየው ዲሞክራሲን፣ አናውርሳቸው የእኛን መጥፎ ገጽታ እንዲወርሱ አናድርጋቸው፡፡ በአዲስ የህጻናት አዕምሮ ሰላም፣ ፍቅር፣ እኩልነት፣ አንድነት፣ መከባበርን፣ መተሳሰብን፣ ከግል ጥቅም የጋራ ጥቅምን፣ የአገርን ጥቅም እንፃፍባቸው፡፡
        ‹‹ያለፈውን አንድ ጊዜ የሆነውን ነገር መለወጥ አንችልም ነገር ግን እያንዳንዳችን ለወደፊቱ ሰላማዊነት ተባብረን ልንሰራ እንችላለን!›› ኪም የተናገረቸው ነበር በቬትናም ጦርነት መታሰቢያ ቀን ላይ ዛሬም ኢትዮጵያውያን አፍሪካዊያን የዓለም ህጻናት ያለፉትን አሰቃቂ ጦርነቶችና ጥቂቶች በማሰብ ‹‹ያለፈውን መለወጥ አንችልም፤ለወደፊቱ ሰላማዊነት ተባብረን እንስራ›› ይላሉና፡፡ ደግሞ ጨለማ ሥራችንን በቀለም ከማስዋብ ይልቅ ከትናንት ጥፋታችን ተመልሰን እውነተኛ ሥራ እንስራ ስህተትና ጥፋትን መማሪያ እንጂ ታሪካችን አናድርግ እርቀ ሰላም እንፍጠር ይቅር እንባባል፡፡ይቅርታ!

ሐሙስ 1 ኖቬምበር 2012

የኢየሩሳሌም የመንፈስ ተጓዥ



                                                 ስምዖን ጌታን ታቅፎ



ክፍል ፪
ባለፈዉ ክፍል አንድ ላይ ረድኤተ እግዚአብሔርን አጋዥ በማድረግ ጀምረን ስለ አዉግስጦስ ቄሳር አመጣጥና ንግስና ተመልክተን  አዉግስጦስ ህዝቡ እንዲቆጠር ለምን እንዳደረገ አንስተን ነበር ያቆምነዉ፤ እነሆ እግዚአብሔር ለዚህ አብቅቶን ክፍል ሁለትን እንዲህ ይዘን መጥተናል ይከታተሉን። ያስጀመረን በሰላም ያስፈጽመን!

ክፍል ፪ እንዲህ ይቀጥላል፡ ማስተዋሉን ይስጠን!
ዩሴፍ፡- ሽማግሌዎች ወገን ስለነበር /ስለተወለደ/ ስሙን ብልዮስ ቄሳር ብለዉታል።ብልዮስ ቄሳር ጋስዮስ ቄሳርን ጋስዮስ ቄሳር አዉግስጦስ ቄሳርን ይወልዳል፤የአዉግስጦስ ቄሳር አመጣጥ እንግዲህ  ይህንን ይመስል ነበር።አነጋገሱ ደግሞ ህዝቡ በሀገራቸው አንድ ኃይለኛ ጠላት ተነስቶ አስቸገራቸዉ አጥፋልንና  እናነግስሀለን አሉት፡፡ እርሱም ኃያል ስለነበር በኃይሉ ተማምኖ ከአነገሣችሁኝ እሺ  በእጄ ብሎ አጥፍቶላቸዋል፡፡  እነርሱም ቃል  እንደገቡለት አንግሰውታል፡፡በቃ…..
-ታዲያ አውግስጦስ ቄሳር ሕዝቡ እንዲቆጠር ያደረገው ለምንድነው?
ዩሴፍ፡- ከእርሱ በፊት የሶሪያ አገረ ገዥ የነበረው ቄርኒዎስ አስቆጥሮ ነበርና እርሱም በሮም ውስጥ ሊያስቆጥር ችሏል፡፡  እኛም ለመቆጠር በቅተናል፡፡
-ወደዚህ ቆጠራ ስትሄድ አብራህ ማሪያም የምትባል እጮኛህ እንደነበረች ይነግራል ፡፡  ይህ አንዴት ነው?
ዩሴፍ/-   አዎ/ እጮኛዋ/ጠባቂዋ/ የነበርኩት እኔ ስለነበርኩ የማይካድ ነው፡፡  አብራኝ በቆጠራውም ላይ ከዚያም በኋላ ልጇን ወልዳ ከዚያም ደገሞ ስተሰደድ አብራኝ ነበረች፡፡ እንዲያውም እነሰሎሜ የዓይን እማኞች ናቸው፡፡ እዚያው ሣለን ነበር ምጧ መጥቶባት ልትወልድ የደረሰችው፡፡
-እሺ አባታችን እንግዲህ እስካሁን የጥያቄያችንን መንደርደሪያ ወይም የታሪኩን የስር መሰረት ነበር ስታጫውተን የነበረው አሁን ደግሞ ወደ ዋናው ጉዳያችን እንመለስና ያንን የስደት ጉዞ እንዴት ነበር ያሣላፍከው? ብትብራራልን፡፡
ዩሴፍ፡- እንግዲህ ስለጉዞ ብዙ  ካልኩህ እኔንም አንተንም ደስ ባለን ነበር፣ በቃላት መግለጹ ግን በዓይን እነዳዩት  እና እንደተሣተፉበት አይሆንም፡፡ለማንኛውም ግን፡- (ቅዱስ ዮሴፍ እጅግ በሃዘን ተዋጠ) ጉዞው በጣም ግራ የሚገባ ነበር፡፡  ሳላስበው ድንገት ነበር ማሪያምን ይዤ እንድጓዝ በመልዐኩ በኩል ትዕዛዝ የተላለፈልኝ እንኳን ላልተወሰነ ወራት የሚጓዙት አስፈሪ ጉዞ/ስደት/ይቅርና የመጓዝ /የመሰደድ/ አቅም አልነበረኝም፡፡  ነገር ግን እንደፈራሁት ሳይሆን አብሮን የነበረው ኤልሻዳይ /ሁሉን ቻይ/ ህጻን ብዙ ተአምራትን እያደረገ ስንጓዝ በኋላም ተወልዶ ካደገና ብዙ ተአምራትን እያደረገ ሲያበረታታንና ሲያጽናናን ደሰታ እየተሰማን ነበር የተጓዝነው፡፡
-ቅዱስ ዩሴፍ ስለጉዟቸው ከነገረን ወዲያ ቅድስት ሰሎሜንም አግኝተን  ቅድስት ሰሎሜ መቸስ ከስደቱ ከነበሩት መካከል ሴት አንቺ ብቻ ነበርሽ ህፃኑ ሲወለድ እናቱ አንደ ሴቶች ልማድ የሚያስጨንቅ ምጥ ነበረባት? ብለን ለጠየቅናት እንዲህ  ብላን ነበር፡-
ሰሎሜ፡- በእርግጥ ሴቶች ህፃኖቻቸውን ሲወልዱ/ ሲገላገሉ/ በጣም የሚያስጨንቅ መዉለድን የሚያስጠላ ምጥ ያጋጥማቸዋል፡፡ ይህ የሴቶች ልዩ ስጦታ/ባህሪ/ነው፡፡ በማርያም ግን እንኳን የሚያስጨንቅ ምጥ ይቅርና የሚያረጋጋ እና የሚያሰደስት ምጥ እንኳን ቢኖር (ፈገግ እያለች)አላጋጣማትም::ዩሐንስ በራዕዩ ስለእመቤታችን በራዕይ 12፣1-17 በምሣሌ ስለእመቤታችን የጻፈውና “በምጥ ተይዛ ስትወልድ ጮኸች...” ማለቱ በሌሎች የሴቶች ልማድ ማናገሩ ነው እንጂ በእመቤታችን ይህ ሁሉ የለባትም፡፡
ምክንያቱም በማህፀኗ የተጸነሰው አምላክ ወልደአምላክ አስጨንቆ በምጥ፣ በጣር፣ በጋር የሚወለድ ሣይሆን ምጥን ጣርን ጋርን የሚያስወግድ: የድንግልና በሯን ሳይከፍት/ክብረንጽህናዋን/ ሳይጓድል እንደገባ  ሳይከፈት የሚወጣ ነው፡፡
ነቢዩ ህዝቅኤል እና ኢሣይያስ ያሉትን አልሰማህም እንዴ ህዝቅኤል “...ይህ በር ተዘግቶ ይኖራል እንጂ አይከፈትም…” ያለው በር እኮ ማህፀኗን /ድንግልናዋን/ ነው፣ ታዲያ ሣይከፍት ገብቶ ሣይከፍት ከወጣ ምጥ ከምን ይምጣ? ህዝቅኤል 44፣1
ደግሞም ምጥ በእርግማን ምክንያት የመጣ ነው፡፡ ሔዋንን “በፀነስሽ ጊዜ ጭንቅሽን አበዛዋልሁ፡ በጭንቅ ትወልጃለሽ፣” ዘፍጥረት 3፣16 ተብላ ነበር፡፡እመቤታችን ግን የአዳም ኃጢያት በዘር ያልተላለፈባት ከመርገመ ሥጋ ከመርገመ ነፍስ ነጻ የሆነች ንፅህት: ቅድስት ናት ስለዚህ ምጥ የሚባል ነገር አላያትም፡፡
-ቅድስት ሰሎሜ አንቺስ እንደ ሴትነትሽ መጠን መቸስ ብዙ መከራን ከህፃኑ እናት ጋር በስደቱ ወቅት ተቀብለሻል የፀሐዩ ዋዕይ የሌሊቱ ቁር ረሀብና ጥሙ ቀላል  አልነበረም፡፡  ታዲያ ይህ ሁሉ እንዴት አደረገሽ?
ሰሎሜ፡- ያልከዉ ከእዉነት ያልረቀ ሀቅ ቢሆንም እንደስጋችን ድካምና እንደ ሴትነቴ ቢሆን የማይቻል ነበር፤ነገር ግን ስደታችን ኃያልና ኃይልን ከሚሰጠዉ ጋር ስለነበር ስደታችን ምንም አልተሰማኝም።
-ጥያቄ እያበዛሁብሽ ከስደቱ ይልቅ እኔ ሳላደክምሽ አልቀረሁም ፤ ለመሆኑ ስደቱን ጨርሳችሁ ከግብጽ ስትደርሱ የተሰማሽ ምንነበር?
ሰሎሜ፡- መጀመርያ ስደትን ስለማላዉቀዉ ገና ስጀምር ወይም ስንሰናደድ ፍርሃት ነበረብኝ፤ ነገር ግን አብሮን የነበረዉ የኢሳይያስ ህጻን አይዟችሁ እያለ የሚያጽናናን ስለነበር ፍርሃት ድካም ሰቆቃዉ ተወግዶ ብርታት ለማግኘት ችያለሁ። ስንመለስ ያለዉን ደስታ እንዴት እንደነበር በምን አይነት ቃላት እንደምገልጽልህ ግራ ይገባኛል። የደስታ ምንጩ ጋር ቁጭ ብዬ እንዲህ ነበር ብዬ እንዴት ልንገርህ? አንደኛ የመከራዉ መገባደድ ያስደስተኛል፡ በሁለተኛ ደረጃ ራሱ ህጻኑ ልጅ ሆኖ ሳለ በዚያ እድሜ ድንቅ ድንቅ ተኣምራትን ሲሰራ ያስደስተኛል። ከሁሉም በላይ ለማዳን ብለን ይዘነዉ የተሰደድነዉ ህጻኑ ራሱም ተርፎ እኛንም አትርፎ ለዚያች ሰዓት ነፍሳችንን ይዘን ወደ አገራችን መመለሳችን አስደስቶኛል። በአጠቃላይ የተሰማኝ ደስታ ነበር።  
ለመሆኑ ቅድስት ሰሎሜ አሁን ካልሽዉ መሃል ሕጻኑ የሰራዉ ተኣምራት እንዳስደሰተሽ ተናግረሽ ነበር የገለጽስሽልን፤ እስኪ በስደታችሁ ላይ ካጋጠሙሽ ተኣምራት መካከል ጥቂቱን ብትገልጪልን?
ሰሎሜ፡-ተኣምሩ ብዙ ነበር፤ቢሆንም ዋናዋናዉን ማስታወሻም ያለዉን አንዳንዱን እነግራችኋለሁ፡-ይኀዉም ጌታ በቤተልሔም በተወለደ ጊዜ ቤተልሔም በእሳት ቅጽር ታጠረች፡ አጋንንት እናያለን ብለዉ ቢመጡ መላዕክት በሐጸ እሳት እየነደፉ የማያስቀርቧቸዉ ሆኑ ሄደዉ ላለቃቸዉ ለዲያብሎስ ነገሩት እስቲ ተሸክማችሁ ዉሰዱኝ አላቸዉ፤ በኪሩቤል አምሳል እርሱም አራት ጸወርት አበጅቷልና ተሸክመዉ ይዘዉት ቢመጡ የማይሆንለት ሆነ። ከዚህ በኋላ ከሄሮድስ  ላከበት የእኔን ሥልጣን መንግሥት የሚቀማ ንጉሥ ተወልዷልና እርሱን ግደል (እንግደል) ብሎ ላከበት፤ እርሱም እነደምን ላድርግ ብሎ የምክር ቃል ይልክበታል፡- ለዚህማ ምን ቸገረህ ዓመት ተመንፈቅ ሁለት ዓመት የሆናቸዉን ሕጻናት ልብስናቀለብ እሰጣለሁና ሰብስቡልኝ ብለህ አዋጅ ንገር አለዉ፤ እነዳዘዘዉ አደረገ። በዚህን ጊዜ መልዐኩ ዮሴፍን ተነስ ሕጻኑንና እናቱን ይዘህ ሂድ ብሎታል። ከዚህ በኋላ ያላቸዉ ልጆቻቸዉን የሌላቸዉ ቀለብ እንቀበልበታለን እያሉ ልጅ እየተዋሱ ሂደዋል።እንደዚህ አድርገዉ 14ሺ ከ4 ሕጻናት አስፈጅቷል።ነገርግን ሕጻኑን/ጌታን/ ሊያገኙት አልቻሉም። ከዚያ በኋላ ግብጽ ወረደ ብለዉ ነገሩት፡አራት አለቃ ከነጭፍራዉ ሸልሞ ይህ የዕለት ሽልማታችሁ ነዉ፡ይዛችሁትያመጣችሁልኝ እንደሆነ ሙሉ ሽልማት እሸልማችኋለሁ ብሎ ሰደዳቸዉ።እነዮሴፍ ሲሄዱ ከጊጋር ቤት ሰንብተን ሄደናል፣ዮሳ የተባለዉም የዮሴፍ ልጅ ታሞ ከጊጋር ቤት ቀርቶ ነበርና የጊጋር ሰዎች አራት አለቃ ከነጭፍራዉ ይዛችሁ አምጡልኝ ብሎ ሰደደ ሲሉ ሰምቶ ከዚያ ተነስቶ ሲሄድ ሰይጣን ከመንገድ ቆይቶ ወዴት ትሄዳለህ? አለዉ፡፡ እነዚያማ ቀድመዉህ ሄደዋል ይህን ጊዜማ ገድለዋቸዉ ይሆናል፡ ተመለስ እንጂ ምን ያደክምሃል? አለዉ። አሁንም ሞተዉም እንደሆነ እቀብራቸዋለሁ ያሉም እንደሆነ እነግራቸዋለሁ ብሎ ኃይል ተሰጥቶት ፈጥኖ ደረሰባቸዉ። ዮሴፍና ማርያም ደክመዉ ወድቀዉ ጌታ አካሉ ቢወዛ እያጠብኩት ሳለሁ አግኝቶኝ እናንተ!ከዚህ በጤናችሁ አላችሁ? በዚህ ሕጻን ምክንያት አሁን በገሊላ በክንዷ ልጅ የታቀፈች ሴት አለችን? አለ። በዚህ ጊዜ ማርያም ደንግጣ ልጇን ከእኔ ተቀብላ የቀን ሐሩር የሌት ቁር የተቀበልኩብህ ከሞት ላላድንህ ነዉ? ብላ አለቀሰች።  
ልጇም ዩሳን አመጣጥህ ዋጋ የሚያሰጥ መልካም ነበር ነገር ግን እናቴን ስለአስደነገጥካት በምፅአት አስገብቼ ዋጋህን እስክሰጥህ ድረስ ይህችን ድንጋይ ተንተርስህ ተኛ ብሎት ከዚያ አርፋል፡፡ ከዚያ ተነስተን ስንሄድ ደርሰውብናል፡፡  ታላቅ ሾላ እንጨት ነበረች ሰውሪን ብንላት ከነአህያችንና ከነሰዎቻችን ተከፍታ ሰውራናለች እነርሱም አህያው ከውስጥ ሆኖ ቢያናፋ የአህያውን ጩኸት እየሰሙ ቦታው ጠፍቷቸው ሲዞሩ ሰንብተው አጥተውን ተመልሰዋል፡፡
ከዚያም ተነስተን እመቤታችን ከልመና ሔደች ሰይጣን የሰውን ልቦና እያፀናባት የሚዘክራት አጥታ ብትመለስ ሰብዓሰገል ያመጡላትን የወርቅ ጫማዉን ሌባ ወሰደባት ልመናም ሄጄ ላላገኝ የልጄን ጫማ አስወስድኩት ብላ ምርር ብላ አልቅሣለች በዚያን ጊዜ እንባዋ በል ፊት ላይ ፈሰሰ። ከዚህ በኋላ ጌታ ለቅሶዋን አይቶ ከድንጋይ ውሃ አፍልቆ አጠጥቶናል፡፡  አንድም ከዚያ ተነስተን ስንሄድ ከትዕማን ቤት ልመና ገብተን ስንለምን ትዕማን እመቤታችንን አይታ “ከወደየት መጥተሻል?” አለቻት እርሷም ከምድረ ይሁዳ አለቻት:“ደረቅ ኃይለኛ ብትሆኚ ይሆናል እንጂ እንዳንቺ ያለች ቆንጆ ከመጋረጃ  ትወጣለች?” አለቻት ዩሴፍም:- ለትዕማን “ለለማኝ ቢኖር ይዘከሩታል: ባይኖር ካለው ያድርስህ ይሉታል እንጂ እንደ ፍላፃ ልብ የሚወጋ ነገር ምን ያረግልሻል?” አላት፡፡  ኮቲባ የምትባል ወደል ባሪያ አለቻት ይህ የፍየል እረኛ እመቤቴን እንደምን ይናገራታል ብላ ደርቡን እያነዋወጠች ወርዳ እሱን በጥፊ መታው ጌታን ከእመቤታችን ነጥቃ ከምድር ጣለችዉ ጌታ ትዕግስት ልማዱ ነውና ዝም ብሏት ያለቅስ ጀመር  በዚህ ምርር ብላ አልቅሣለች ዕንባዋ በፊቱ ላይ ወርዷልና እንዲህ  አለ፡፡  እመቤታችን ልታነሣው ብትሔድ ዩሴፍ “ተዓምራቱን ይዩ አምላክነቱን  ይግለጽ ተይው አታንሽው” አላት፡፡
-       ትዕማንን ከነገረዶቿ ምድር ተከፍታዋጠቻት:
-       ቤተሰቦችዋም ጦጣ ዝንጀሮ እየሆኑ የገዛ ውሾቻቸው እያባረሯቸው ወጥተው ሄደዋል፡፡
-       ከጐረቤትም ጩኸት ሰምተው እንረዳለን ብለው ቢመጡ ግብር አበርነታቸውን አይቶ ከዚያው ደርሷቸዋል፡፡  ዩሴፍ  እንደአዛዥ እኔም እንደአበጋዝ ጌታ እንደ ንጉስ እመቤታችን እንደ ንግስት ሁነን ከቤቱ ገብተን መንፈቅ ተቀምጠናል፡፡
በመጨረሻም ከስደት ስንመለስ ከመንገድ ደክመን በረሃ ለበረሃ ስንጓዝ ፈያታዊ ዘየማንና ፈያታዊ ዘፀጋም የተባሉ ሁለት ወንበዴዎች አጋጥመውን በዚህን ግዜ  ሁላችንም ተደናግጠን ጌታን የተውልኝ መስሎኝ ልብሴን አውልቄ ሰጠኋቸው እነርሱም ስድስት ቀን ጠፍተንባቸው በሰባተኛው ቀን አግኝተውን ነበርና ምነው እስከ ዛሬ ታደክሙናላችሁ  አሁንስ እግዚአብሔር ከእጃችን ጣላችሁ አሉንና ሰብዓሰገል ያመጡለትን ስረወፅ ቀሚስ ያቺን  ወስደውብን  ከሄዱ በኋላ  እልፍ እንዳሉ ፈያታዊ ዘየማን እኒህ ሰዎች የቤተመንግስት ሰዎች ናቸው መሰለኝ አሳዘኑኝ እንመልስላቸው አለ፡፡  ነገር ግን የሚቀሙት በተራ ነበርና ተራዉ የፈያታዊ ዘፀጋም ስለነበር አይሆንም ብዙ ዋጋ ያወጣልኛል አለው ፈያታዋ ዘየማንም ከቤቴሌሔም  ጀምሮ እስከዚህ የቀማነው የአንተ ይሁን ይሄ የእኔ ይሁን ብሎ መልሶልናል፡፡
ጥጦስ ጌታን ከእኔ  ተቀብሎ ተሽክሞ ሰይፋን እየተመረኮዘ ሲሸኘን ተሰበረበት “ምነው ‘ወርቅ ላበደረ ጠጠር እህል ላበደረ አፈር’ እንዲሉ በጐ ብሠራ ሰይፌን ሠበርክብኝ” ብሎ አዘነ ጌታም “የተሰበረውን ሰይፍህን ከሰገባው አስገባው:” አለው እንዳለው ቢያደርግ ደህና ሆኖ አገኘው፡፡  እርሱም ደስ ብሎት “ይሄ ብላቴና ከደቂቅ ነቢያት ወገን ነው” አለ፡፡
ሌላው ደግሞ እንደ ኦሪት ስርዓት በስምንተኛው ቀን ወደቤተመቅደስ ይዘነው ሄደን ካህኑ ሊገርዘው ቢል ምላጩ ዉሃ ሆነ እንደገናም በገዛ ፈቃዱ ምላጭ ከሰውነቱ ላይ  ሳያርፍ ተገርዞ ታይቷል፡፡  እንግዲህ ካየኋቸው ተዓምራት መካከል ከብዙ በጥቂቱ ይህንን ይመስላል፡፡
-እኛም ከቅድስት ሰሎሜ ጋር ለሰፊ ስዓት አብረን ከተጫወትን በኋላ ወደ ቅዱስ ዩሴፍ ተመልሰን እንደዚህ ብለነው ነበር፡-በስደታችሁ ወቅት ወደ ኢትዮጵያ እንደሄዳችሁ ይነገራል መሄዳችሁ እዉነት ነው?

-ዩሴፍ፡- አዎ መሔዳችን እርግጥ ነው መሄዳችንም እኛ አውቀን ያደረግነው ነገር ብቻ ሣይሆን ትንቢቱም በነቢዩ ዕንባቆም ተተንብዩ ስለነበር ነው፡፡ ዕንባቆም 3፣3-7
“...እግዚአብሔር ከቴማን ቅዱስም ከፋራን ተራራ ይመጣል ክብሩ ሰማያትን ከድኖአል ምስጋናውም ምድርን ሞልቶአል፡፡  ፀዳሉም እንደ ብርሃን  ነው ጨረር ከእጁ ወጥቶአል  ኃይሉም በዚያ ተሰውሮአል፡፡  ቸነፈር በፊቱ  ይሄዳል የእሳት ነበልባል ከእግሩ ይወጣል፡፡……… የኢትዮጵያ ድንኳኞች ሲጨነቁ አየሁ የምድያም አገር መጋረጃዎች ተንቀጠቀጡ…”  ብሏልና በትንቢቱ መሰረት የፋራን ተራራ የተባለችን እመቤታችን ስትሆን ከፋራን ተራራ ይመጣል የተባለው ደግሞ የተወለደው ሕፃን/ኢየሱስ ክርስቶስ/ ነው፡፡  ድንኳን ደግሞ የሰደተኞች  ማረፊያ ነው፡፡ “…የኢትዮጵያ ድንኳኖች ሲጨነቁ አየሁ”የሚለው ዐረፍተ ነገር የእመቤታችን ስደት ወደኢትዩጵያም እንደምንሄድ የሚያመለክት ነበርና ስለዚህ ተጉዘናል፡፡
ለጊዜው ከቅዱስ ዩሴፍ ጋር ያለንን  ቃለመጠይቅ ማገባደጃ የመሰልንን ጥያቄ ለዚህ ትውልድ ካያችሁት ከምታውቁት የምታስትላልፋት ምን መልዕክት አላችሁ? ብለን ጠይቀናል፡፡  እነርሱም ከተመካከሩ በኋላ በዩሴፍ አማካይነት እንዲህ ብለውናል፡፡

ዩሴፍ፡- እኛ የምንለው ብዙ ነገር አለም የለምም ምክንያቱም ትውልዱብዙ ያውቃልና፡ አንድም በሌላ መልኩ ማወቅ ደግሞ የእግዚአብሔርን ማንነት ሊያሳውቀው እግዚአብሔር ከሚያድለው ክብር ስላላደረሰው እኛ የምንለው ይህ የተወለደው ሕፃን ፍፁም አምላክ ፍፁም ሰው መሆኑ ቀርቶ ሰው ብቻ ነው ብለው እናቱንም ወላዲተ ሰብዓ ብለው የሚረዱ ሰላሉ አምላክነቱን ለማረጋገጥ እንዲችሉ ከፅንሰቱ ጀምሮ እስከ ልደቱና ከዚያ በኋላ  ስላለው ፍፁም አምላክነቱ ኢሳይያስ ከ740 ዓመት በፊት ፅፎት የነበረው የትንቢት ቃል መመልክት መልካም ነው፡፡ ኢሳ7፣14 ማቴ፣1፣23 የተወለደው ሕፃን አማኑኤል የተባለው ቢወለድም አምላክ  በመሆኑ ስጋን ነስቶ ፍፁም ሰው መሆኑን ስለመገለጥ ነበር፡፡  ከዚህ ሌላ አሁንም በትንቢት… ሕፃን ተወልዶናልና…. ስሙም ድንቅ መካር ኃያል አምላክ የዘለዓለም አባት የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል፡፡ የሚል ቃል እናገኛለን፡፡  ኢሳ 9፣6 በቤተልሔም ዋሻ ሰብዓ ሰገል ወርቅ ዕጣን ከርቤ መብዐ አድርገው ያቀረቡላት እኛ  የሰገድንላት ከብቶቻችንም በትንፋሻቸው ያሟሟቁት ሕፃን ኢየሱሰ ክርስቶስ አምላክ ስለሆነ ስሙም ኃያል ተብሎ እንደሚጠራ ልንመክራቸው እንወዳለን፡፡

-       ከስደቱ እንዴት ነበር ልትመለሱ የቻላችሁት? ብለን ጥያቄ አቀረብንለት
-       ዩሴፍም፡- ተነስተህ ብላቴናውንና እናቱን ይዘህ ወደምድረ እስራኤል ተመለሰ የዚህን ብላቴና ነፍስ ለማጥፋት የሚሹት ሰዎች ጠፍተዋልና…  ብሎ መልዐኩ ስለነገረን ነዉ፡፡
-       እነዚህ የጠፉት እነማን ነበሩ?
-       ዩሴፍ፡- ዩሐንስ በፊጥሞ ደሴት ታስሮ በራዕይ ካየው ራዕይ 12፣1-6 የተጻፈውና ዩሐንስ ዘንዶው እያለ የሚጠራው አጋንንት ያደሩበት ሄሮድስ  ነው፡፡
-       መቸስ ይህንን ሁሉ ከመነጋገራችን በፊት የልደቱን ቀን ነበር ማወቅ ያለብን ለመሆኑ መቼ ነበር የተወለደው?
-       አስቀድሞ ትንቢት እንደተነገረለት ያ አምስት ቀን ተኩል ሲፈጸም ነዉ፤ በኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር /በ5500/ በአንድ ዓ.ዓ.  በዘመነ ማቴዎስ በታህሣሥ  29  ቀን ማክሰኞ ከሌሊቱ 10 ሰዓት ላይ ነበር፡፡
-       አስቀድመን በጉዞአችሁ ያደረገውን ተዓምራት ነግራችሁናል በዕለተ ልደቱ የተደረገውን ብትነግሩን? ስንላቸው እነርሱም፡--
-       1. የተወለደበት ሰዓት ሌሊት ሲሆን ብርሃን ከሰማይ ወርል ምክንያቱም መላዕክት ለእረኞች ሲናገሩ አይተዋል ሉቃስ2፣39
-       2.  የእግዚአብሔር መልአክ መጥቶ ለከብቶች ጠባቂዎች ክርስቶስ መድኀን ተወልዶላችኋል ብሎ አብስሮአቸዋል ሉቃስ 2፣10
-       3.  ብዙ መላዕክት ከሰማይ መጥተው አመስግነዋል ሉቃስ 2፣13-14
-       4.  የባቢሎንና የፋርስ ነገስታትም አንድ ላይ መልዓክ እየመራቸው ወደ ቤተልሔም መጥተው ህፃኑ ኢየሱስን አግኝተው ሰግደው ወርቅ ዕጣን ከርቤ ግብር አቅርበውለታል ማቴዎስ 2፣1-12 መዝሙር 71፣10 ብለው ነገሩንና እኛም ቀጥለን ወደ ቅዱስ ስምኦን እና ወደ እመቤታችን  ነበር የሄድነው፡፡
-       አባታችን ቅዱስ ስምኦን እንደሰማነው ከሆነ እና አንተም ከሥራችን ሰዓት ውጭ እንዳጫወትከን ይህ ያሁኑ ቁመናህ ጥንት ያልነበረና ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እንደሆነ ነበር የነገርከን ይህ እንዴት  እንደሆነ ብትነግረን?
ስምኦን፡- ታሪኩ ብዙ ነው እንደው ጥያቄያችሁን ለመመለስ ያህል በአንድ ወቅት የነቢያትን የትንቢት መጽሐፍ ለመተርጉም ተሰጥቶን ሣለ በመሐል ላይ አንድ ግራ የሚገባ ከአእምሮ በላይ የሆነ ነገር አጋጠመኝ፡፡
-ይቅርታ አድርግልንና በመሐል ገባንብህ ይህ ከአእምሮ  በላይ የሆነ ነገር ያልከውን ግልጽ ብታደርግልን?
ስምኦን፡- …ድንግል በድንግልና ትጸንሣለች.. ብሎ ኢሣይያስ የጻፈውን ነበር፡በእድሜዬ ድንግል ሴት ወልዳ አይቼም ሰምቼም ስለማላውቅ ግራ ተጋባሁ ድንግል የሚለውንም ብዕሲት /ሴት/ ብዬ ፃፍኩት በዚህን ግዜ እንቅልፍ ነገር አደረብኝና ተኛሁ ስንቃ ድንግል ተብሎ ተጽፎ አየሁት ለሶስት ግዜ እንደዚህ ካደረኩ በኋላ በሶስተኛው መልአክ ተገልጾ እንዲያውም ይህንን ነገር ሳታይ አትሞትም አለኝ፡፡ ለረጅም ዘመናት ቆይቼ /በጣም አርጅቼ/ ከአልጋ ላይ እንደ ትኋን ተጣብቄ ከተኛሁበት ሥፍራ ትንቢቱ ተፍጽሞ ሕፃኑ  በቤተልሔም በከብቶች በረት ተወልዶ በስምንተኛው ቀን ይዘውት ከኔ ዘንድ አመጡት፡፡ (የቅዱስ ስምዖን ፊት በጣም ያበራ ነበር ስለሁኔታዉ ሲያወራን)
§  ከዚያስ ይህ ድንቅ ነገር መፈጸሙን ስታይ ምን ተሰማህ: ምንስ አልክ?
ስምኦን፡-  ይህንን ድንቅ ነገር ስሰማ ደስታ ነበር የተሰማኝ በተለይ ግን ታቅፌው ሳበቃ ይንቀጠቀጥ የነበረው እጄ ሲፀና  የጐበጠው ወገቤ ሲቃና አንደትኋን ከአልጋ ተጣብቆ የነበረው ገላዬ ሲዝናና በጣም ነበር ደስታ የተሰማኝ ከዚያም በኋላ “አይኖቼ ማዳንህን አይተዋል በሰላም አሰናብተኝ”ብዬ ተማፀንኩት፡፡
በመቀጠልም እመቤታችንን  አነጋግርናት፡ ማርያም የታሪኩ ባለቤት እንደመሆ ብዙ የምናናግራት ነገር ነበር፡ ነገር ግን ለሌላ ጊዜ አቆይተነዋል፡፡ ላሁኑ ግን እንዲህ አልናት!
§  እመቤታች እኛ ሣናውቅ አንቺ አውቀሽ የማታደርጊልንና የማታስደርጊልን አንዳች ነገር የለም የልቦናችንን  ሃሣብ/ ጥያቄ/ ምንም እንኳን ብታዉቂ ከፊትሽ ከቆምን ዘንድ አባሐርያቆስ እንዳለሽ እኛም የምንለሽ አለን.. ድንግል ሆይ ርጉም በሆነ በሄሮድስ ዘመን ከእርሱ ጋር ካገር ወደ ሀገር ስተሸሺ ካንቺ ጋር መሰደዱን አሳስቢ፤ ድንግል ሆይ ከዓይኖችሽ በፈሰሰው እና በተወደደ ልጅሽ ፊት የወረደውን መሪሪ ዕንባ  አሳስቢ ድንግል ሆይ  ረሀቡንና ጥሙን ችግሩንና ኃዘኑን ከርሱ ጋር የደረሰብሽንም ጭንቅ ሁሉ አሳስቢ ...  ብለናት ነበር፡፡  እርሷም፡-
ማርያም፡- ልጄ ዳግም ለፍርድ ሲገለጽ በክብሩ  በመንግሥቱ  ያስባችሁ፡፡
                                                           አሜን! ይቆየን!

ጦማሩን ስለጎበኙ አመሰግናለሁ!

መልካም ነገርን ለሌሎች ማጋራት ባህላችን እናድርግ፤ ላልደረሰዉ በማጋራት ድርሻችንን እንወጣ፡፡

ትቶ እና ችሎ

  ትቶ እና ችሎ ብጹእ ወቅዱስ አቡነ መርቆርዮስ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ በደረሰ ረታ ብጹዕነታቸው ለሶስት አሥርት አመታት እኛ በማናውቀው እግዚአብሔር በሚያውቀው በብዙ መከራ በብዙ ፈተና ውስጥ ነው ያሳለፉት። ...