ሐሙስ 28 ጁላይ 2022

ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያዊነት

 አንዳንዴ ስለ ኢትዮጵያ ፣ ኢትዮጵያዊነት ፣ ስለ ክርስትና ፣ ስለ እስልምና እና ሌሎችም ማሰብ ይከብዳል። ፖለቲካውንማ ተውት የእረኞች ጨዋታ አድርገውታል፤ እረኞችስ ቀን ተጫውተው ማታ ሲበተኑ ነገ በሌላ ጨወታ እና ቅኝት ነው የሚመለሱትና።


ግራ የገባው አንዲት አገር ኢትዮጵያን ይዞ በየመንደር ለዚያውም ለመንደሩ አንዳች ፋይዳ በሌለው ጉዳይ መከፋፈሉ፣ ሁሉም ነፍሱን አስይዞ የሚወራረድባት የመኖሩ ምክንያት እምነት ይኖረውና ከየእምነቱ አስተምህሮ ውጪ ሲጓዝ ከማየት የበለጠ ግራ የገባ ነገር የለም።(ለኔ)


አሁን በሰሞኑ በውስጥ ብዙ መልእክቶች ከየእምነቱ ሰዎች ይደርሱኛል። (ለመረጃ ይሁን ሊያናግሩኝ እንደሆነ እንጃ) እኔ ግን ኢትዮጵያ ከመቶ አመት በፊት ስለነበረችበት ሁኔታ የተጻፉ ታሪኮችን፣ ግለ ታሪኮችን በማንበብ ላይ ነበርኩ። (የዛሬውን ያህል ቅጥ ያጣ ነገር አላነበብኩም) አልፎ አልፎ እንዲህ የከረፋ ታሪክም ባይሆን የሽፍቶችን ታሪክ ለማየት ችያለሁ። ( እምነትን ሽፋን እና ተገን አድርገው የሚንቀሳቀሱ የዛሬዎቹ ወሮበላዎች ግን የትናንቱን ሽፍቶች ያስንቃሉ)


ኢትዮጵያኮ ከጣልያን ወረራ ቀደም ብሎ እና ከዚያ ኋላ አውራጃ ከአውራጃ የሚያገናኝ የረባ መንገድ አልነበራትም፤ ቅርብ ጊዜ ድረስ አብዛኛው የገጠር ከተሞቻችን የጤና ተቋም አልነበራቸውም። በሽተኞች እና ነፍሰጡሮች ለሕክምና በቃሬዛ ነበር የሚጓጓዙት።(ከምኔው ለጥፋት ደረስን ሆስፒታል፣ ትምህርት ቤቶች፣ የመንግስት ተቋማት፣ ባንኮችን እና ሌሎች የግል ተቋማትን ለማፍረስ ፈጠንን?)


በእኔ አረዳድ ከሆነ ልሳሳትም እችላለሁ ባለኝ መረጃ ንጹህ ውሃ መጠጣት የስላጣኔ እና የእድገት ምልክት በሆነባት አገር እየኖርን እንዴት ብለን የሌለንን እናጠፋለን? መንገድ፣ ሆስፒታል፣ ዮኒቨርስቲ ወዘተ የስኬት መለኪያ በሆነበት አገር እንደ ቅርስ ልንንከባከበው ሲገባ እንዴት በአስርት አመታት የገነባነውን በሰአታት ለማፍረስ እንነሳለን? እንዴትስ ነው ሙስሊሞች/ ክርስቲያኖች ይህን አደረጉት ታስብላለህ?


ታድያ እንደዚህ አይነት አገር ውስጥ የሚኖር ሕዝብ፣ ሐይማኖተኛ አገር ከማፍረስ ይልቅ መገንባት አይሻለውም ነበረ። (አገር እና ሕዝብ ሲኖር ነውና ሁሉም ነገር የሚኖረው)


ብዙ ጊዜ የሚጠቀስ ነገር ልጥቀስላችሁ ከአገር ወጥተን ባህር ስንሻገር ፓስፖርት ነው የምናሳየው ፓስፖርታችን ላይ ኢትዮጵያዊ መሆናችን እንጂ ሌላ ነገራችን አይጠቀስም። እውቅናችንም ሆነ እውቅና መነፈጋችን በአገራችን ላይ የተመረኮዘ ነው። ነገር ግን የኔ እምነት የበላይ ካልሆነ፣ እንደ ሰም አቅልጦ እንደ ገል ቀጥቅጦ ካልገዛ ይህቺ አገር አገር አትሆንም የሚል ትምክህት አለብን። (የት ልንደርስ ነው?)


ይህን አስተምህሮ ነቢዩ መሐመድም ሆኑ ኢየሱስ ክርስቶስ አላስተማሩትም። መቸስ ከሁለቱ አስተምሮ ውጪ የሆነ ጥቂት ነው። ለእስልምናው ቤተክርስቲያን ወይም ቸርች አቃጥሎ ጥቅሙ ምንድንነው ከፊቱ ያለው ታሪክ ምንም ይሁን ምንም። ለክርስቲያኑ ቀኝህን ለመታ ግራህን ስጥ የሚል ወንጌል እየሰበከ እና እየተሰበከ ሙስሊሙን ማሳደድ ከምን ከየት የመጣ ነው?


አንድ ተንቀሳቃሽ ምስል ከሰአታት በፊት ደረሰኝ ሙሲሊሞችን እንደማይወክል ጠንካራ እምነት አለኝ። ለፖለቲካ ትርፍ የሚባሉትንም አይወክልም የፖለቲካ ዲሲፕሊን አይደለምና። ከአንድ ደቂቃ በታች ነው በግርድፉ እንዲህ ይላል[ "ቤተክርስቲያንን አታቃጥሉ ቤተክርስቲያንን ለምን ታቃጥላላችሁ? ቤተክርስቲያንን አትንኩት ባለበት ይሁን እነርሱን ካጠፋን በኋላ ቤተክርስቲያኑ ወደ መስጊድነት እንቀይረዋለን። አላህን እያመሰገነ ቅዱስ ገብርኤል ወደ መስኪድነት እንደተቀየረ ይናገራል"] እኔ እስከማውቀው እስልምና አስተምሮ ካልሆነ በቀር በግድ አያሰልምም። 


ብዙ ነገር ማለት ቢቻል እንኳን ብዙ የሚከለክሉኝ ሥነምግባሮች እና አስተምህሮዎች ስላሉኝ ብዘለው እመርጣለሁ። ስለ ራሴ ጉዳይ እንደ እግር እሳት ሲያንገበግበኝ ስለ ወንድሞቼም እንዲሁ ይገደኛልና። 


ክርስቲያን እንደመሆኔ መጠን አስር የምገዛለት ህጎች አሉኝ አምስቱ ስለ እግዚአብሔር ፍቅር ሲሆን አምስቱ ስለ ወንድም ፍቅር ነው። ስለዚህ እግዚአብሔርን የምወደውን ያህል የሰውን ልጅ (ከእምነቱ፣ ብሔሩ እና የፖለቲካ አመለካከቱ ጨምሮ) የመውደድ ግዴታ አለብኝ።


ለአንድ ክርስቲያንም ይሁን ሙስሊም እንዴት ቤተክርስቲያን፣ ቸርች እና መስኪድ እንደሚገነባ በደንብ ያውቀዋልና አንዳቸውንም ለማቃጠል፣ ለማፍረስ ይቅርና አንዲት ጠጠር ለማንሳት አይዳዳውም።


አንዳንድ የአለም ክፍሎች ላይ አብያተክርስቲያናት ወደ ሙዚየም እና መስጊድነት እንደተቀየሩ አውቃለሁ። ነገር ግን ይህ ተግባር የኢትዮጵያውያን መገለጫ አይደለም። ይሁን ከተባለ ብዙ ዋጋ ያስከፍላል ይኽ መዘንጋት የለበትም። (አንዱ ከሰሞኑ የተነሳውን ግርግር ታሳቢ አድርጎ ስለሚከተለው ጥፋት ሲናገር ለነበረው ምላሽ ሲሰጥ "ማንም ውሃ እና ቅጠል ይዞ አይወጣም " ሲል ሰማሁ። እውነት ነው ድንበር ሲታለፍ ሁሉም እሳት ጎርሶ እሳት ይተፋልና ዳፋው ከባድ ነው።) ከዚህ ማንም አያተርፍም።


አንድ ወደሚያደርገን አገራችን ጉዳይ ስንመጣ አገር ፈርሳ የት ሆነን ልናመልክ ነው? እምነት የላኩልን ሰዎች እንደሆነ እምነት ይልኩልን እንደሆነ እንጂ አገር ስትፈርስ አንዳችንንም አይቀበሉንም። ይህን አንዘንጋ። አጥፊዎችም ስለ ጥፋታችን ዶላር ይከፍሉን እንደሆነ እንጂ አገር ቆርሰው አይሰጡንም። ይህ የሚጠፋን አይመስለኝም።


አንዳንድ የዋሆች የሚሆነው ሁሉ ለፖለቲካ ትርፍ እንቅስቃሴ ብቻ የሆነ ብቻ ይመስላቸዋል። አትሳሳቱ አይደለም ባይባልም  ብቻውን ግን አይደለም። ሁለቱ ቤተ እምነቶች መቸም በእምነት ደረጃ አይጋጩም። የቤተእምነቱ ሰወች እንደሚያራምዱት ተለጣፊ ዓላማ ግን ላይጋጩ የሚችሉበት ሁኔታ የለም አይባልም። እኛ ግን ዓላማችንን እና ሚናችንን እንለይ ሐይማኖተኛ ነን ካልን የእምነት አስተምሮውን እንከተል፣ ፖለቲከኞች ነን ካልን እምነቱን እና ፖለቲካውን አንቀላቅል።


ወጣቶች ትልቅ የሆነ የአገርም ሆነ የሐይማኖት አደራ አለባችሁ። በአስተውሎት ተንቀሳቀሱ እንጂ እንደ መንጋ አትነዱ። እምነትንም ሆነ አገርን ተገን አድርገው የሚዘውሩን ጊዜያቸውን እንደ ሸንኮራ ምጥጥ ስላደረጉት ነውና እኛ ግን ጊዜያችንን ልንሰዋላቸው ዓላማቸውን ልናስፈጽም አይገባም።


በየእምነት ተቋማቱ ያላችሁ ወጣቶች፣ አስተማሪዎች፣ አባቶች አስቀድማችሁ የእምነቱ አስተምሮ ምን ይላል? ብላችሁ ጠንቅቃችሁ እወቁ። አንዳንዴ የራስን እምነት የሚያስተምር ግልብ 'መምህር' ከማዳመጥ የሰከነ አስተዋይ የሌላ ቤተእምነት መምህር መስማት ያስመኛል።


አንዳንዱ አስተምህሮው የማይለውን ሲደሰኩር ወጣቱ እውነት እየመሰለው ይከተዋል። ለ"መስዋዕትነት" ይሯሯጣል።


ስለመስዋዕትነት ሌላ ጊዜ የምናወራው ነገር ቢሆንም ቅሉ አሁን ላይ በየትኛውም ቤተእምነት በተነሳ ግርግር እየተነሳን የምንማገደው መስዋዕትነት እንዳልሆነ አስረግጬ እናገራለሁ። መስዋዕትነት ስለሚያምኑት ነገር ዋጋ መክፈል ነው።እኛ በቤተእምነታችን አጥር ሥር ስናልፍ ስናገድም ኖረን አንዳች የእምነት ምልክት በሕይወታችን ሳይኖር እንደ እሳት እራት ግርግር ውስጥ ገብተን የሞትን እንደሆነ እንደሁ መስዋዕት የሚለው ስም ሲለጠፍልን ስሙን እናገኝ እንደሆነ እንጂ ክብሩን አናገኝም።

እንደ ወንድምነቴ የምመክረው መጀመሪያ በመስኪዱ፣ በቤተክርስቲያን ፣ በቸርች ተገኝተህ ተማር ሕይወቱን ኑረው ከዚያ በኋላ በእምነትህ የሚመጣውን ተቀበል ከዚያም መስዋዕት ሁኑ፤ ጽድቅም ሆኖ ይቆጠርልሃል። አለበለዚያ ግን ደምህ ደመከልብ ነው የሚሆነው።


ሁላችንም አገራችንን ዘብ እንቁምላት የየቤተእምነቶቻችንን ጉዳይ አንገት መድፊያ አንሁን።


ለክርስቲያኖች አንድ መልዕክት ማስተላለፍ እፈልጋለሁ። አትስረቅ፣ አትግደል፣ አታመንዝር፣ ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ፣ በሐሰት አትመስክር የሚለውን ቀዳሚ ሕግ ጠብቅ።


ይኽን ካደረክ የማንም ሐብት ንብረት አይዘረፍም፣ የሰውልጅ ሕይወቱ እንዲሁ በከንቱ አይቀጠፍም፣ የሴትልጅ ክብር በየመንገዱ አይገሰስም/አትደፈርም፣ ለወንድምህም ወዳጁ እንጂ ጠላቱ አትሆንም፣ ስለእውነት እንጂ ስለቡድንህ ፍርድ አይዛባምና።


እንዲህ ስላልሆነ በዘመናችን መኪኖቻችን በስንት ቁልፍ እና ቴክኖሎጂ ጭምር ተጠብቀው ይሰረቃሉ፣ እህቶቻችን በነጻነት አይንቀሳቀሱም አልፎ ተርፎም ይደፈራሉ፣ በየእምነት ቤቶች በተፈጠረ ችግር ሰዎች ይገደላሉ፣ አካል ይጎላል፣ ንብረት ይወድማል፣ የመንጋ ፍርድ ይፈረዳል። 99% አማኝ ያለባት አገር ነች ተብላ የምትታማ አገር አለችን።ለዚህ አፍራለሁ።


ዶክተር አለማየሁ ዋሴ በአጭር ቃል የተናገሩት ምርጥ ገላጭ አባባል አለ። በግርድፉ መልዕክቱ እንዲህ ይላል "እኛ ኢትዮጵያውያን እንደሰው በዚህምድር ላይ ያልሰራነው በደል የለም። ሰይጣን እንኳን የሚቀናብን ነን። በቀሪው ዕድምያችን ያልሰራነው ነገር ቢኖር መልካም ነገር ብቻ ነው።


ይኼ ነው እንግዲህ ኢትዮጵያዊነት ... ቀሪው ዕድሜያችን የክፋት ሳይሆን የመልካምነት ነው። ለዚያውም በቂ የሆነ ዕድሜ የለንም። ከበቃን ቀሪ ዘመናችንን በአንድነት መልካም ነገር እንስራ።


ለጠቢብ አንዲት ቃል ትበቃዋለችና ጠቢባን ሁኑ።

"መጀመሪያ እንድትሸነፍ የሚያደርጉህን ምክንያትህን አሸንፍ"

 ጀግናችን አበበ ቢቂላ በባዶ እግሩ ሮጦ ጀግንነትን ከመቀዳጀቱ በፊት 35ኪሎ ሜትር እንደሮጠ ሆዱን አመመው፤ ይኽም ሕመም ሩጫውን እንዲያቋርጥ ሊያደርገው ከጫፍ የደረሰውን ውሳኔ እንዲቀይር ያደረገው ከላይ የጠቀስኩት የአለቃው ምክር ነበረ። 


የድል ምልክታችን አበበም ወደ ልቡ ተመልሶ ሕመሙን ችላ አለው። ሩጫውን ቀጠል፤ ዛሬ የምንኮራበትን ድል አስመዘገበ። አበበን ለድል ያበቃው በዓለም አደባባይ የኢትዮጵያን ሰንደቅ እንዲውለበለብ ያስቻለው ሕመሙን ማሸነፉ ነው። 


እኛም እንዳናሸንፍ የሚያደርጉን፣ የሚያዋርዱን፣ ከክብር ዝቅ የሚያደርጉን፣ መለያየት ላይ እንድናተኩር የሚያደርጉን፣ ዘረኞች እንድንሆን፣ ለኔ ብቻ እንድንል ያደረጉን ሕመሞች አሉብን። 


ድል ለመቀዳጀት፣ በዓለም አደባባይ አንደኞች እንድንሆን፣ ከፈለግን መጀመሪያ እንድንሸነፍ የሚያደርጉንን ምክንያቶች እናሸንፍ። 


መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል " ጥቃቅኑን ቀበሮዎች አጥምዳችሁ ያዙ" እንዚህ ቀበሮዎች ጥቃቅን መሆናቸው ሳይሆን የሚያጠፉት ሰፊ የወይን እርሻ ነው ግምት ሊሰጠው የሚገባው። በዘመናችንም ችላ የምንላቸው ጥቃቅን የመሰሉን ለዓመታት አዕምሯችን ላይ የተሰሩ ነገሮች ዛሬ ላይ ለእርስ በርስ ጦርነት፣ ለስደት፣ ለሞት፣ ለጥላቻ፣ ለዘር እልቂት እየዳረገን ይገኛል። 


እንድንሸነፍ ከሚያደርጉን ነገሮች መካከል አንዱ ዘረኝነት ነው፤ ለማሸነፍ ከፈለግን መጀመሪያ ዘረኝነትን የተጠናወተው ማንነታችንን ማሸነፍ ይኖርብናል። 


ሌላው ጥላቻ ነው "ወንድሙን የሚጠላ ነፍሰ ገዳይ ነው" እንዲል መጽሐፍ ጥላቻ የዕድገት/የአሸናፊነት ጸር ነው። ስለዚህ መጀመሪያ ጥላቻን እናሸንፍ። ከዚያ ወደቀደመ ክብራችን እንመለሳለን። አለበለዚያ የሶስት ሺ ዘመን ታሪካችንን እናበላሻለን። 


ሁሌም አሸናፊ ትሆን ዘንድ የሚያሸንፍህን አሸንፍ።

መልካም ጊዜ

ደረሰ ረታ 


እንኳን ደስ አለን

 በኢትዮጵያ ምድር ላይ ያጣነዉን ደስታ ዳግም እንድንጋራ ላደረጋችሁን ድንቅ አትሌቶቻችን እና የአትሌቲክስ ፌዴሬሽን እናመሰግናችኋለን፡፡

 

መላዉ የኢትዮጵያ ሕዝብ ሆይ እንኳን ደስ አለን፡፡ 





እሑድ 8 ኦገስት 2021

ሞት በጥር ነሐሴ መቃብር

 "ሞት በጥር ነሐሴ መቃብር"

በደረሰ ረታ


እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም አባቷ ኢያቄም እናቷ ሐና በመባል የሚጠሩ ሲሆን የተጸነሰችሁ እንዲሁ በሐጢያት ሳይሆን " ብዙ ተባዙ ምድርንም ምሉዋት" በተባለው አምላካዊ ሕግ እንጂ። ኦሪት ዘፍጥረት 1፥28

ኦ ድንግል አኮ በፍትወት ደነሰ ዘተፀነስኪ ድንግል ሆይ " ዘርዕ ዘይወፅእ እምስካበ ተአዳዌ ሕግ ይከውን ለቅጥቃጤ ወለሐሳር" ለሐሳር ለመከራ የተጸነስሽ አይደለሽም።

አላ በሩካቤ ዘበሕግ እምሐና ወኢያቄም ተወለድኪ፤ ከሐና ከኢያቄም ሕጋዊ በሆነ ሩካቤ ተወለድሽ እንጂ።

የእመቤታችን ቅድመ አያቶች (በጥሪቃ እና ቴክታ ) ባለጸጎች ነበሩ። ልጅ ግን አልነበራቸውም።

ሕልም አይተው እንደ ህልሙ መሰረት ቴክታ ጸነሰች፤ ሄእማንን ወለደች።

ሄኤሜን ዴርዴን፣ ዴርዴ ቶናህን፣ ቶናህ ሲካርን፣ ሲካር ሄርሜላን፣ ሄርሜላ ሐናን ወለደች።

ሐናም ለአቅመ ሔዋን ስትደርስ ነገዱ ከይሁዳ የሆነ ኢዩአቄምን አገባች። እርሷም እንደ አያቶቿ መካን ሆነች።

ሐና ልጅ ስላልነበራት እጅግ ታዝን ነበረ አንገቷንም ደፋች። ከዕለታት በአንደኛው ቀን ከቤተ እግዚአብሔር ሄዳ እጅ ነሳች። ስትመለስ ርግቦች ሲጫወቱ አይታ ፈጣሪዋን " ሁሉን ሁለት ሁለት አድርገህ ፈጥረሃል ሐና ባሪያህን ግን ድንጋይ አድርገህ ፈጥረሃታል። " በማለት አምርራ አለቀሰች።

ሐናና ኢያቄም ከቤተ እግዚአብሔር ሱባኤ ገብተው የሰው መሳቂያ መሳለቂያ እንዳይሆኑ ዕድሜ ዘመናቸውንም አንገታቸውን ደፍተውም እንዳይኖሩ ተማጸኑ፣ ወንድ ልጅ ቢወልዱ ለቤተ እግዚአብሔር አገልጋይ እንደሚሆን ሴት ልጅ ቢወልዱ መሶበ ወርቅ ሰፍታ፣ ሐር ፈትላ ትኖራለች ብለው ስለት ተሳሉ።

ወዲያው ነሐሴ ሰባት ሐና የዓለሙን መድኅን የወለደችውን ማርያምን ጸነሰች። እመቤታችንም ገና በእናቷ ማኅጸን ሳለች ብዙ ተአምራትን ታደርግ ጀመር። ይህን የሰሙ አይሁድ በምቀኝነት ተነሱባቸው። በድንጋይ ወግረው በእሳት ፈጅተው ሊገድሏቸው መከሩባቸው። የእግዚአብሔር መልአክም በማህጸን ካለችው የዓለም መድኃኒት እንደሚወለድ ያውቅ ነበረና ወደ ሊባኖስ ተራራ ሂዱ ብሏቸው በዚያ እያሉ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተወለደች።

የእመቤታችን መጸነስ እንደ እንግዳ ደራሽ እንደ ውሃ ፈሳሽ የነበረ ነገር ሳይሆን በአባቶች ትንቢት ሲነገር የኖረ ነበር። እመቤታችንም በተወለደች ዕለት ብርሃን ወርዷል፤ተድላ ደስታ ሆኗል።

የእመቤታችን አስተዳደግ ልቡናቸውን እንዳደነደኑ የዕብራውያን ሴቶች ልጆች እንዳደጉት በቧልት በጨዋታ በዋዛና በፈዛዛ አልነበረም። በንጽሕና በቅድስና ሆና በቤተመቅደስ አድጋለች እንጂ። ምድራዊ ኅብስትን፣ ምድራዊ መጠጥን ተመግባ ጠጥታ አይደለም። ሰማያዊ ኅብስትን ተመግባ ከሰማየ ሰማያት የተቀዳ ሰማያዊ መጠጥን ጠጥታ አደገች እንጂ።

በእናት በአባቷ ቤት ሶስት ዓመት ከኖረች በኋላ የስለት ልጅ ናትና ሦስት አመት ሲሆናት አፏ እህል ሳይለምድ ልቧ ሰው ሳይወድ በቃላቸው መሰረት ወስደው ቤተመቅደስ ለካህኑ ዘካሪያስ ሰጡት በቤተመቅደስ ትኖር ዘንድ ቤተመቅደስ አስገቧት፣ በቤተመቅደስ ቅዱስ ሩፋኤል ኅብስት ሰማያዊ ፅዋዕ ሰማያዊ እየመገባት አስራ ሁለት ዓመት ኖራለች።

ዕድሜዋ አስራ አምስት አመት ሆኗታልና ጎልማሳ ስለሆነች አይሁድ ካህኑ ዘካርያስ ከቤተመቅደስ እንዲያስወጣት ዘበዘቡት እርሱም ለእግዚአብሔር አመለከተ። የአከባቢው ሰው ይጠብቋት ዘንድ እጣ ቢያወጡ በዮሴፍ ወጣበት፣ እምቢ ቢል ርግብ በራሱ ላይ መጥታ አረፈችበት፣ ዕጣ ቢጣጣሉም ደግሞ በዮሴፍ ወጥቶበታል። ምስክርነት በሶስት ይጸናል እንዲሉ እመቤታችንን የመጠበቁ ነገር በዮሴፍ ጸናበት። ሕዝቡም " በዚህም ቢሉ በዚህ እመቤታችን ላንተ ደርሳለችና ግብር ገብተን እንደሰጠንህ ግብር ገብተን እስክንቀበልህ ድረስ ይዘሃት ሂድ" አሉት። ሳይወድ በግድ ይዟት ሄደ። ዮሴፍ እመቤታችንን ወደ ቤቱ ይዟት ከሄደ በኋላ ወደ ዓለም ኑሮ አልተመለሰም። በንጽሕና በቅድስና ሲጠብቃት ኖረ።

አዳም ከበደለ ጊዜ ጀምሮ በአብ ሕሊና ስትታሰብ ኖራለችና እግዚአብሔር አብ ንጽሕና ቅድስናሽን ባየ ጊዜ አብሳሪውን  ብርሃናዊ መልአክ ቅዱስ ገብርኤልን ወደርሷ ላከው እርሱም እንዲህ አላት። " መንፈስ ቅዱስ ይመጽእ ላእሌኪ፤ ወኃይለ ልዑል ይጼልለኪ፤ ውእቱሰ ንጹሕ እምነ ሠለስቱ ግብራት ዘወእቶሙ ዘርዕ ወሩካቤ ወሰስሎተ ድንግልና እለ ሥሩዓን በእጓለ መሕያው ወእሙራን ቦሙ። ..." መንፈስ ቅዱስ ያድርብሻል፤ ኃይለ ልዑል ወልድም ከሦስቱ ግብራት ይከለክልሻል። አካላዊ ቃል ከአባቱ እሪና ሳይለይ ካንቺ ተዋሐደ።ከምልአቱ ሳይወሰን ፀነስሽው። አካላዊ ቃል ካንቺ ከሥጋሽ ሥጋ ከነፍስሽ ነፍስ ነስቶ ሰው ሆነ።

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በዐርባ ዘጠነኛው ዓመተ ምሕረት በዘመነ ሉቃስ ጥር ሃያ አንድ ቀን በስልሳ አራት አመቷ ዐረፋለች።

ሐዋርያት አስከሬኗን ባጎበር አድርገው ወደ ጌቴሴማኒ ሊቀብሯት ይዘዋት ሲሄዱ አይሁድ ለምቀኝነት አያርፉምና አስክሬኗን በእሳት አቃጥለን እናጥፋት ብለው ተማከሩ።

ታውፋንያ የተባለው ኃይለኛ ሰው ፈጥኖ መጥቶ የአልጋውን ሸንኮር ያዘው መልአከ እግዚአብሔርም በረቂቅ ሰይፍ ሁለት እጆቹን ቆረጠው። ነገር ግን ቅዱስ ጴጥሮስ በጸሎቱ ሁለት እጁን ቀጥሎለታል።

ሐዋርያት በዚህ ተደናግጠው ቢበተኑ ወንጌላዊው ዮሐንስ ከመልአክ ጋር አስክሬኗን በገነት ዕፀ ሕይወት ሥር አስቀምጠዋታል።

ቅዱስ ዮሐንስ ተመልሶ መጥቶ ሐዋርያትን አይዟችሁ እመቤታችን በገነት በዕፀ ሕይወት ሥር ናት ብሎ አጽናናቸው።

ሐዋርያት ቶማስ ዐይቶ እኛ ሳናይ ልንቀር ነውን? ብለው በነሐሴ መባቻ በዕለተ ሰኞ ሱባዔ ገብተዋል። ሁለተኛውን ሱባዔ እንደጨረሱ በአሥራ አራተኛው ቀን መልዐኩ የእመቤታችንን አስክሬን ሰጥቷቸው ዕለቱን ቀብረዋታል።

በሶስተኛው ቀን ማክሰኞ ነሐሴ አሥራ ስድስት ቀን ተነሥታ ዕለቱን ዐርጋለች።

ቶማስ በወቅቱ አልነበረም፤ ከሀገረ ስብከቱ ከሕንድ(ሕንደኬ) በደመነ ተጭኖ ሲመጣ እመቤታችን ስታርግ አገኛት። ከደመናው ሊወድቅ ነበረ።

እጅግ አዝኖ እመቤቴ ሆይ ቀድሞ ጌታዬ ልጅሽ ከትንሣኤው ለየኝ አሁን ደግሞ አንቺም ልትለይኝ ነበረ አላት።

አይዞህ ዕርገቴን ያየህ አንተ ብቻ ነህ፤ ጓደኞችህ ሐዋርያት አላዩም ለእነርሱም የማረጌን ነገር አንተ ንገራቸው አለችው። እንዲያምኑህም ይኸው ሰበኔን እንካ አሳያቸው ብላ ሰደደችው።

ቶማስም ሐዋርያትን የእመቤታችን ነገር ጠየቃቸው፣ ቀበርናት አሉት፤ ሞት በጥር ነሐሴ መቃብር እንዴት ይሆና? አላቸው።

እነርሱም አጥበን ገንዘን የቀበርናትን እኛን ካላመንክ ማንን ልታምን ነው? ከዚህ ቀደምም የልጇን ማረግ አላምን ብለህ በመጠራጠርህ እና ካላየሁ አላምንም ብለህ እጅህን ከተወጋው ጎኑ ሰደህ እጅህ ተኮማተረ። አሁንስ ምን ፈልገህ ነው የምትጠራጠረው ብሎ ቅዱስ ጴጥሮስ ጠየቀ።

ጓደኞቹም እንዲያምን ከመቃብሩ ስፍራ ወስደው ጉድጓዱን ቆፍረው አስከሬኗን ሊያሳዩት ባሉ እንደ ልጇ ከመቃብር የለችም። ሐዋርያት ከመቃብር አስከሬኗን ቢያጡ ደነገጡ።

ቶማስም አታምኑኝም ብዬ እንጂ ስታርግ አግኝቻታለሉ ለባልንጀሮቹ የእመቤታችንን የማረግ ነገር ነገራቸው። እንዲያምኑትም ሰበኗን ሰጣቸው። እነርሱም ገንዘው የቀበሩትን ሰበኗን ቢያዩ አመኑ፤ ለበረከት ይሆናቸውም ዘንድ ሰበኗን ተካፍለው ድውይ ሲፈውሱበት፣ ሙት ሲያስነሱበት ኑረዋል።

ሞት በጥር ነሐሴ መቃብር።

ቶማስ ማረጓን ብቻውን አይቶ እኛ ሳናይ እንቀራለን ብለው በዓመቱ በነሐሴ አንድ ሱባኤ ገቡ። ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነሐሴ አስራ ስድስት እመቤታችንን መንበር፣ ቅዱስ ጴጥሮስን ተራዳኢ ካህን፣ እስጢፋኖስን ዲያቆን አድርጎ ቆርቦ አቁርቧቸዋል። እርሷንም አቆረባት።

እኛም በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የምንገኝ ክርስቲያኖች የሐዋርያትን ፈለግ ተከትለን ሱባኤ ገብተን ተገለጭልን እንላታለን። የበቁትን እየተገለጠች ታነጋግራቸዋለች። የኔ አይነቱን ሐጢያተኛ በበረከት እጆቿ ሕይወታችንን፣ ሥራችንን፣ ቤተሰባችንን፣ ወዘተ ትባርካለች።

ማርያም ማለት መርህ ለመንግሥተ ሰማይ ማለት ነው። ምእመናንን እየመራች ገነት መንግሥተ ሰማያት ታገባለችና።

አንድም ፍጽምት ማለት ነው። ለጊዜው መልክ ከደም ግባት አስተባብራ ይዛ ተገኝታለች። ፍጻሜው ግን ንጽሐ ልቡና አንድ አድርጋ ይዛ ተገኝታለችና።

አንድም ጸጋ ወሀብት ማለት ነው። ለጊዜው ለናት ለአባቷ ጸጋ ሀብት ሁና ተሰጥታለች። ፍጻሜው ግን ለሁላችን ተሰጥታለችና። አንድም ልዕልት ማለት ነው አርአያ ማለት ልዑል ማለት እንደሆነ። እመቤታችንንም መትሕተ ፈጣሪ መልዕልተ ፍጡራን ይላታልና። ተፈሥሒ ቤተ ይሁዳ ወተሐሠዪ ቤተ እስራኤል ተለአኪተ እግዚአብሔር ወሰብእ ማኅበረ መሃይምናን ወሕዝብ ማለት ነው።

አንድም ማሪሃም ማለት እግዝእትነ ብዙኃን ማለት ነው። አብርሃም ማለት አበ ብዙኃን ማለት እንደሆነ። ያንም በዕብራይስጥ እንጂ ይለዋል ብሎ ማርያም ማለት ቅሉ እግዝእተ ብዙኃን ማለት ነው።

ይቆየን።

አሜን








ማክሰኞ 25 ሜይ 2021

የጌታ ቃል ትዝ አለው

 " የጌታ ቃል ትዝ አለው " የሉቃስ ወንጌል 22፥61

በደረሰ ረታ

ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስን ክርስቶስን " ሌሎች ቢክዱህ እንኳን እኔ አልክድህም " ብሎት ነበረና ጌታም " ዶሮ ሳይጮህ ሶስት ጊዜ ትክደኛለህ " አለው።

ጊዜው ሲደርስ ጌታን ያዙት ወደ ሊቀካህናቱ ቤትም ወሰዱት

• ጴጥሮስም ርቆ ይከተለው ነበር።
• ጴጥሮስ በመካከላቸው ተቀመጠ።
• ይህ ደግሞ ከእርሱ ጋር ነበረ አለች።
• አንቺ ሴት፥ አላውቀውም ብሎ ካደ።
• አንተ ደግሞ ከእነርሱ ወገን ነህ፡ አለው።
• ጴጥሮስ ግን፡— አንተ ሰው፥ እኔ አይደለሁም፡ አለ።
• ሌላው አስረግጦ፡— እርሱ የገሊላ ሰው ነውና በእውነት ይህ ደግሞ ከእርሱ ጋር ነበረ፡ አለ።
• ጴጥሮስ ግን፡— አንተ ሰው፥ የምትለውን አላውቅም፡ አለ።
• ያን ጊዜም ገና ሲናገር ዶሮ ጮኸ።
• ጌታም ዘወር ብሎ ጴጥሮስን ተመለከተው፤
• ጴጥሮስም፡— ዛሬ ዶሮ ሳይጮኽ ሦስት ጊዜ ትክደኛለህ እንዳለው የጌታ ቃል ትዝ አለው።
• ጴጥሮስም ወደ ውጭ ወጥቶ ምርር ብሎ አለቀሰ።
የቅዱስ ጴጥሮስ አቋም ከችኩልነቱ የተነሳ ወላዋይ ይመስላል፤ ችኩልነቱ እና ባለማገናዘብ የሚመልሳቸው መልስ ከፍቅር የመነጨ ነው።

መጠራጠር እና ክህደቱ የተፈጠረው ግን በፍርሃት፣ ከነበረበት ስፍራ፣ ከወቅታዊ ሁኔታው የተነሳ ነበር።

1. ጌታን ሲይዙት ርቆት መከተሉ
2. ሲበርደው እሳት ለመሞቅ ጌታን ከያዙት ወገን ከመካከላቸው መቀመጡ
3. የጌታን ወደዚህ ዓለም የመምጣት ዓላማ በአግባቡ ሳይለይ የልብ መሻቱ
እነዚህ ተደማምረው ቅዱስ ጴጥሮስ መጀመሪያ ጌታን አላውቀው፣ ቀጥሎ ራሱን ክዶ አይደለሁም፣ በመጨረሻም ጌታን ሊክደው እና አላውቀውም እንዲል አድርጎታል።

ከዘረኛ ጋር ስንውል ዘረኛ፣ ከነፍሰ ገዳይ ጋር ስንውል ነፍሰ ገዳይ፣ ከመንፈሳዊ ጋር ስንውል መንፈሳዊ እንሆናለን። ወፍጮ ቤት የዋለ አይደለም የገባ ሰው ዱቄት ሳይነካው አይወጣምና።

" ቃሌ ከሚያልፍ ሰማይና ምድር ቢያልፍ ይቀላል " ያለ አምላካችን ያለው ቃል ተፈጸመ። ዶሮ ሳይጮኽ ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታን ሶስቴ ካደው።

ጌታም ዘወር ብሎ ጴጥሮስን ተመለከተው።

ጴጥሮስም የጌታ ቃል ትዝ አለው፦ ።" ዶሮ ሳይጮኽ ሶስት ጊዜ ትክደኛለህ "

ጴጥሮስም ወደ ውጪ ወጥቶ (ከወንበዴዎቹ ተለይቶ፣ ጌታን ሊገሉት ከሚፈልጉት አጠገብ ርቆ፣ እሳት ከሚሞቅበት ቦታ ተነስቶ ) ምርር ብሎ አለቀሰ።

የቅዱስ ጴጥሮስ መራር ለቅሶ የንሰሐ ለቅሶ ነበረ።

እኛስ?

ከቅዱስ ጴጥሮስ የሕይወት ተሞክሮ ምን ተማርን?

ጌታን በቅርበት ነው የምንከተለው ወይንስ በርቀት?

ውሎአችን ከነማን ጋር ነው?

አውቀን አምነን ነው እየተከተልነው ያለነው፣ በስሜት ነው፣ ከቤተሰቦቻችን ስለወረስን ነው፣ ወይንስ እንዴት ነው?

አሁናዊ ማንነታችን ምን ይመስላል?

ብዙዎቻችን የቅዱስ ጴጦሮስ አይነት ሕይወት ያለን ይመስለኛል፤ መመላለስ ነገር ግን መራር የንሰሐ ሕይወት የሌለን። እንደዛ ከሆነ እንመለስ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የሰማነው የጌታ ቃል ትዝ ይበለን።

አካሄዳችንን እናቅና ( ቤተክርስቲያን መሄድ የምንፈራ፣ ማስቀደስ የምንጠላ፣ መጾም የማንችል፣ የጸሎት ሕይወት የሌለን፣ ማመን የማይታይብን፣ ውሎና አዳራችን ከማይመስሉን ጋር የሆነ፣ ከማያምኑት ጋር ወዳጅነት የመሰረትን ) እንመለስ።

ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታውን እንዲክድ ያደረገው፦
መፍራቱ፣
ከማያምኑት ጋር መቀመጡ፣
ጽኑ እምነት አለመኖሩ፣
ወዘተ ናቸው ለመካድ እና መሪር እንባን እንዲያነባ ያደረጉት።

ስለዚህ እኛም ፍርሃትን የሚያርቅ ጽኑ ፍቅር እንዲኖረን ጌታን ቀርበን እንወቀው። ከማያምኑት ጋር ውሎአችንን አናድርግ፣ ( ከላም ጋር የዋለች ጊደር ምን ተምራ ትመጣለች እንዲባል) ውሎአችንን እናስተካክል።

አንዳንዶቻችን በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አዳኝነት፣ አምላክነት፣ አማላጅ አለመሆኑን፣ ማመናችንን፣ ክርስቲያን መሆናችንን ለመደበቅ እንጥራለን፣ የአንገት ማኅተማችንን እንደብቃለን፣ መጾማችንን ሳይቀር እንዋሻለን። ( የዘፈን ዳርዳሩ ... እንደሚባለው እንዳይሆን እፈራለሁ። )

በጌታ ቃል ራሳችንን እንመልከት። አንዳንዶቻችን ታሪክ ቀመስ እንሆናለን በልጅነቴ ሰንበት ተማሪ ነበርኩ፣ ዘማሪ ነበርኩ፣ ዲያቆን ነበርኩ፣ ቆራቢ ነበርኩ፣ መምህር/ አባ እገሌን አውቀዋለሁ፣ የቄስ ልጅ ነኝ ወዘተ እንላለን። አሁን የት ነን? እንደ ቅዱስ ጴጥሮስ ራሳችንን እንይ። እሳት ሐጢያትን እየሞቅን፣ ጌታን አሳልፈው ከሰጡ፣ ከሸጡ፣ ከገደሉ ጋር ነን? ወይስ ቃሉ ከሚነገርበት አትሮኑስ ስር ነን?

በጌታ ቃል ራሳችንን ካየነው ምንም ጥያቄ የለውም በድለናል። ( ሁሉ በደለ እንዲል የአምላካችን ቃል። ) ክደናል የሚያስብል ደረጃ ላይ ነን። እንደ ቅዱስ ጴጥሮስ ፈጥኖ የሚመለስ ልብ፣ የሚጸጸት ልብ፣ ወደ ንሰሐ የሚመለስ ልብ ካለን ንሰሐ እንግባ፣ አምርረን እናልቅስ፣ ያሳለፍነው ዘመን ይበቃናል እንበል።

የቀማን መልሰን፣ የበደልን ክሰን ወደ ንሰሐ ሕይወት እንገስግስ።

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምህረት ዐይኑ ይመልከተን።

አሜን።
ይቆየን።

መልካም የሕማማት ሳምንት ይሁንላችሁ።
❤❤######################❤❤

የእለት ተለት ጽሑፎቼን ለመከታተል ከዚህ በታች ባሉት ሁሉ እገኛለሁና ይከታተሉኝ። ከተመቸዎት ለሌሎች ያጋሩት።
My Facebook page link (በፌስቡክ ገጽ እንገናኝ)

https://www.facebook.com/deresse2020/

Main facebook account (ዋናው የፌስ ቡክ ገጼ ይቀላቀሉት)

https://www.facebook.com/DeresseReta

Follow me through telegeram (በቴሌግራም ሊከታተሉኝ ከፈቀዱ) ሁሉም ምልከታዬን የማጋራባቸው ማህበራዊ ድረ ገጾች ናቸው።

https://t.me/deressereta

ከአሥር አመት በላይ ከ50ሺ በላይ አንባቢዎች ያሉት መጦመሪያም አለ።

www.deressereta.blogspot.com

https://anchor.fm/deresse-reta/episodes/ep-ev5j5o

ሥራን አውቆ መሥራት

 ሥራን አውቆ መስራት


አንድ ሰው በቅርስ ጥበቃ ተቋም በጥበቃ አገልግሎት ተቀጥሮ እየሰራ ሳለ አንድ ቀን በቅርስ ማዕከሉ ውስጥ ሲንቀሳቀስ ብዙ ዘመናትን (1500ዓመታት) ያስቆጠረ ብርጭቆ ሰበረ።

ተቆጣጣሪው በጣም ተበሳጩ ተቆጡ ጥበቃው ምን እንደሚያበሳጫቸው ግራ በመጋባት ጠየቀ።

ኃላፊው እንዴ ብርጭቆኮ ነው የሰበርከው ብርጭቆው ደግሞ 1500 ዓመት ያስቆጠረ ትልቅ ቅርስ ነው አሉት።
ጥበቃውም ግራ ከመጋባት ውስጥ ወጥቶ ዘና በማለት እንደውም እንዲህ ያረጀ ብርጭቆ እዚህ ምን ይሰራል። እንደውም በአዲስ እተካዋለሁ አይጨነቁ በማለት ሊያረጋጋቸው ሞከረ።

ሰውየውም እጅግ ተበሳጩ። ቁጣቸው ጨመረ።

የሥራ ኃላፊውን ያስቆጣቸው ጥበቃውን ያረጋጋው ጉዳይ ምንድነው?

ጥበቃው ቅርስን ያህል ነገረ ሰብሮ እንዲህ ያረጋጋው ምን አይነት የጤና ሁኔታ ላይ ቢሆን ነው? ትሉ ይሆናል።

እስኪ ስለ እነዚህ ሁለት ሰወች በማውራት ጊዜ ከምናባክን ስለ እያንዳንዳችን እናስብ።

እኛ ምን አይነት ሰወች ነን?

ቁጡ?

ግዴለሽ?

ዝምተኛ?

እስኪ ምን ያስቆጣናል? ምንስ ዝም ያስብለናል? ግዴለሽ የሚያስደርገንስ ምንድን ነው?

ግድየለሽነት የጤናማነት ምልክት አይሆንም ሲወድቅም፣ ሲሰበርም፣ ሲጠፋም ግዴለሽ ከሆንን ጥቅሙ አልገባንም አልያም ችግር አለ።

አንዳንዶች ምናልባት ተስፋ ከመቁረጥ ግድየለሽ ሊሆኑ ይችላሉ። የፈለጉትን ከማጣት፣ በጣም የተማመኑበት ነገር ሲከዳቸው፣ ቃል ሲታጠፍባቸው፣ አምነው ሲከዱ ወዘተ ለግድየለሽነት ምንጭ ሊሆን ይችላል።

ምን ያስቆጣናል?

በተለምዶ እውነተኛ ሰው እውነቱን በምሬት ሲናገር ቁጡ ይባላል። ሌሎች ደግሞ " የሌባ አይነደረቅ መልሶ ልብ አድርቅ " እንዲሉ ጥፋታቸውን ለመደበቅ ይቆጣሉ። ጥቂቶች ደግሞ የግንባራቸው ሥጋ ቅርጽ (መሸብሸብ/ ኮስተር እንደ ማለት) ቁጡ ያስብላቸዋል።

እኔን መሰሎች ደግሞ ስራ ሲበላሽ እና ያለ አግባብ ሲሰራ በተለይ እንደ ቅርስ ጥበቃው ሰራተኛ ለደሞዝ ብቻ ገብተው በሚወጡ፤ ነገር ግን የሚሰሩት ሥራ ዓላማው ካልገባቸው ሥራቸውን በአግባቡ ካልተወጡት ያስቆጣል።

ዝምተኞችን ስንመለከት በአጭሩ ለመፈረጅ ቢያስቸግርም ሥራው ቢሰራ ባይሰራ፣ ቢበላሽ ባይበላሽ ምንም የማይመስላቸው "ያው በገሌ ነው" ብለው እንደ ድመት የሚያስቡ። ተናግሬ ሰው ከሚቀየመኝ ዝም ብዬ ተመሳስዬ አልኖርም ብለው የሚያስቡ ናቸው። እንደዚህ አይነት ለኔ ልዝብ ነው።

ለነገሩ ሁሉም ነገር ስለተናገሩት፣ ዝም ስላሉት አይፈታም አንዳንዴ ሲናገሩ የሚፈታ እንዳለ ሁሉ ዝም ሲሉት የሚፈታም አለና።

እኛ እንደ ተቋም እንደ አገር የተሰጠንን ሥራ የምንሰራው እንዴት ነው? እንደ ጥበቃው ሳይገባን ነው ወይስ እንደ ቅርስ ጥበቃ መስሪያ ቤት ኃላፊ በያገባኛል፣ በኔነት፣ ሥራው ገብቶን ነው?

ከትንሣኤ ማግስት

 የትንሣኤ ማግስት ቀናት

በደረሰ ረታ

ሰኞ ፦ ማዕዶት መሻገር ማለፍ በሲኦል ወደ ገነት በጨለማ ወደ ብርሃን የመሻገራችን ነፍሳት ከሲኦል የመውጣታቸው መታሰቢያ ነው። ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ የመምጣቱ አላማ ይኸው ነውና።

በባህሪው ሞት በመንግሥቱ ሽረት የሌለበት አምላክ የሞተው ለዚህ ነውና።

በዚህ በትንሣኤ ማግሥት ሰኞ በዚህ ዕለት በፋሲካችን በክርስቶስ ትንሣኤ ከድቅድቅ ጨለማ ወደ ሚደነቅ ብርሃን፣ ከሞት ወደ ሕይወት፣ ከሲኦል ወደ ገነት፣ ከሃሳር ወደ ክብር መሻገራችንን እናስባለን፡፡


ማግሰኞ፦ ማግስተ ሰኞ ቶማስ ሲባል ቶማስ ጌታን አይቶ ማመኑ ጌታዬ አምላኬ ብሎ መመሥከሩ

እንደምናውቀው ቶማስ በጌታችንም ሆነ በእመቤታችን ትንሣኤ ወቅት በአገልግሎት ምክንያት አልነበረም ወንድሞቹ ሐዋርያት ነበሩ ስለ ትንሣኤዋ የነገሩት ነገር ግን አላመነም። በጌታ ትንሣኤ ጌታን ቢጠራጠር እርሱ ስለመሆኑ ጌታ ማረጋገጫ የሰጠው ሲሰቀል የተወጋ ጎኑን እንዲያይ ነበረ። እጁን ወደ ተቸነከረበት ቢሰደው ጣቶቹ እሳት እንዳየ ጎማ ተኮማተሩበት። አምኖም መሰከረ። ዮሐ. 20፡27-29

በዚህ እለት ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ አለማመናችንን እንዲረዳ፣ አምነንም እንድንመሰክር እንዲረዳን እናስበዋለን።

ረቡዕ፦ አልአዛር ሲባል ጌታ አልአዛርን ከሞት እንዳስነሳው እናስባለን።

አልአዛርን ከሞት እንዳስነሳው ስናስብ ክርስቶስ የሞትን ስልጣን የሻረ የሕይወት ራስ፤ የመቃብርን ሥርዓት ያጠፋ ትንሣኤ፡ ድልም ያረገ ዘለአለማዊ ንጉሥ መሆኑን እንመሰክራለን፡፡

በዚህ ወቅት ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያውያን በብዙ ጭንቅና መከራ፣ በሞትና በሕይወት መካከል ስለምንገኝ፣ ኢትዮጵያዊ ማንነታችን እንደ ጉም በንኖ እየጠፋ ስለሆነ ጌታችን ለእኛም ትንሣኤ ልቡና እንዲያድለን እንለምነዋለን።


ሐሙስ፦ አዳም ሐሙስ ይባላል ለአዳም የሰጠው ተስፋና የተገባለት ኪዳን እንደተፈጸመ አዳምና ልጆቹ ነጻ እንደወጣን ይታሰብበታል።

በበለስ ምክንያት ከገነት እንደወጡ ሁሉ የአለም መድኀኒት ጌታችን ለአለመ ድህነት ከወጣንበት ገነት እንመለስ ዘንድ ከአምስት ቀን ተኩል በኋላ ለአዳም በገባው ቃል መሠረት አድኖናልና።

አርብ ፦ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ይባላል ቤተ ክርስቲያን በክርስቶስ ሞትና ትንሳኤ መመስረቷ ይሰበካል።

በዕለት አርብ ቤተክርስቲያን በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ስለመመስረቷ ይሰበካል፡፡ ክርስቶስ ስለ እርሱ ራሱን አሳልፎ ሰጥቶ ቤዛ ሆኖ በደሙ አንጽቶ በትንሣኤው ድል ሰጥቶ ቤተክርስቲያንን እንዳከበራት ይነገራል፡፡

ቤተክርስቲያን ስንል ሕንፃውን ሳይሆን አማኞችን ነው፤ ክርስቶስ ለሕንፃ አልሞተምና፡፡

ቅዳሜ፦ ቅዱሳት አንስት ሲባል የጌታን አካል ሽቱ ለመቀባት ጨለማ አቋርጠው ወደ መቃብር መምጣታቸው፣ ትንሳኤውን ቀድመው ማየታቸው ይሰበክባታል።

እሁድ፦ ዳግም ትንሳኤ ሲባል ለደቀ መዛሙርቱ ለ3ተኛ ጊዜ መገለጡንና ሰላምን መስበኩ ይሰበካል።

ማጠቃለያ

እንደ ክርስቲያን በአብይ ጾም ወቅት የምናሳየው መንፈሳዊ ማንነት ፍሬ የሚያፈራበት ነው። ከአብይ ጾም በኋላ ከትንሣኤው ማግሥት በቤተክርስቲያን ምሥጢር ብዙ መታሰቢያ ነገሮች አሉት አንዱ ሐምሳው ቀናት ከጾም የምንከለከልበትና አርብ እና ረቡዕ ሳይቀር የፍስክ ምግቦችን የምንመገብበት ነው።

ከዚህ በቀረው ከላይ የዘረዘርናቸው ምሥጢራትን ቤተክርስቲያን ለመጀመሪያው ሳምንት ስያሜ ሰጥታ አመሥጥራ ታስተምራለች።

እኔም ከብዙ በጥቂቱ፣ ከረጅም በአጭሩ፣ አምልቼ አስፍቼ ሳይሆን በማይም አቅሜ አቅርቤያለሁ።

እንደ ክርስትናችን የሁለት ወር መንፈሳዊ ተግባራችን የሚያፈራበት ነው። ጾም፣ ጸሎታችን፣ ስግደት፣ ምጽዋታችን፣ መውደቅ መነሳታችን ያበቃለት ሳይሆን በእምነት የዘራነው መንፈሳዊ ዘር አብቦ የሚያፈራበት ነው።

ነገር ግን አብዛኞቻችን መንፈሳዊነት ያለቀ ሥጋዊነት የተጀመረ እናስመስለዋለን። ፋሲካ ሲሆን ሥጋዊነት እንዲሰለጥንብን አይደለም።

ጾም እና ንሰሐ ገብቶ ቀኖና መቀበል ቢቀር ሌሎች ተግባራት አይቀሩም። ስለዚህ የትንሣኤ ማግሥት የልቡና ትንሣኤ እንዲሆንልን እመኛለሁ።

ይቆየን።
አሜን።

ጦማሩን ስለጎበኙ አመሰግናለሁ!

መልካም ነገርን ለሌሎች ማጋራት ባህላችን እናድርግ፤ ላልደረሰዉ በማጋራት ድርሻችንን እንወጣ፡፡

ትቶ እና ችሎ

  ትቶ እና ችሎ ብጹእ ወቅዱስ አቡነ መርቆርዮስ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ በደረሰ ረታ ብጹዕነታቸው ለሶስት አሥርት አመታት እኛ በማናውቀው እግዚአብሔር በሚያውቀው በብዙ መከራ በብዙ ፈተና ውስጥ ነው ያሳለፉት። ...