ዓርብ 26 ማርች 2021

የጾም ምግብ ቤቶች

 የጾም ምግብ ቤቶች


በየከተማችን የኢትዮጵያን ቤተክርስቲያን የአጽዋማት ጊዜ ጠብቀው ምግብ ቤቶች በአዲስ መልክ ማስታወቂያ መስራት የተለመደ ነው።


አንዱን ብንመለከት የአብይ ጾምን ምክንያት በማድረግ የጾም ቡፌ፣ በየአይነቱ፣ ዓሣ አዘጋጅተናል። የምትል ትገኝበታለች። 


ማስታወቂያዎቹ ለጾም እና ጸዋሚ "ተጨንቀው" ምግብ እንደ ማዘጋጀታቸው ጥራጥሬ፣ ሽንብራ፣ ደረቅ ቂጣ አያዘጋጁም። ዝግጅቱ ለጾም ሳይሆን ለመብል ነውና።


ፍትሐ ነገሥት ስለ አጽዋማት በሚናገረው አንቀጹ አንቀጽ 15 ላይ በ572ኛው ቁጥር ላይ " በእነዚህ በታዘዙት ጾሞች ከቀኑ እስከ ዘጠኝ ሰአት ድረስ ይጹም ከዓሣ በቀር ሥጋ አይብሉባቸው። " ይላል።


ግእዙ እንዲህ ተብሎ ተጽፏል፦" ... ወኢይብልዑ ቦሙ ሥጋ ዘእንበለ ዓሣ ..." እዚህ ጋር ሊቃውንቱ እንደሚነግሩን "ዘእንበለ" ፍችው ብዙ ከመሆኑ የተነሳ ሲያጨቃጭቅ ቆይቷል። ቤተክርስቲያኒቱ ለዚህ መፍትሔ ይሆን ዘንድ ከመጽሐፍ ጠቅሳ ዓሣ የሥጋ ዘር ነውና። ደምም አለውና ጾም እንደሆነ በሲኖዶስ ደንግጋለች።


ፍትሐ ነገሥትም በዚሁ አንቀጽ ቁጥር 584 ላይ " በጾም ምክንያት ጠብ ክርክር ቢሆን መጾም ይገባል። ከመብላት በጣም ይሻላል።" ይለናል። 


ነገር ግን ጸዋሚው የቅድስት ቤተክርስቲያን ልጅ ራሱ ለምግብ ሲቀመጥ ዓሣ አልጾምም ሲል ይደመጣል። ለነፍሱ ሊያደላ በሚገባው ወቅት ለሥጋው ያደላል።


"ከዓሣ በቀር ሥጋ አይብሉባቸው።" በሚለው ቃል ዓሣን አልጾምም የሚለው "ጸዋሚ" ከፍ ብሎ " ከቀኑ እስከ ዘጠኝ ሰአት ድረስ ይጹሙ " የሚለውን አያነበውም፤። አይተገብረውም።


" ጾምስ በሕግ ውስጥ በታወቀው ጊዜ የሰው ከምግብ መከልከል ነው በደሉን ለማስተሰረይ ዋጋውን ለማብዛት እርሱን ወዶ ሕግን ለሠራለት እየታዘዘ የፈቲውን ኀይል ያደክም ዘንድ ለነባቢት ነፍስም ትታዘዝ ዘንድ " የተሰራ መንፈሳዊ ተግባር እንደመሆኑ መጠን በጾም ወቅት መከልከል ከሚገባን ነገር ሁሉ ልንከለከል ይገባናል፣ በደላችንን ለማስተስረይ ንሰሐ ገብተንም ልንጾም ይገባል፣ ወደን ፈቅደን ሕግንም ለሰራልን ልንታዘዝ ይገባል፣ ሥጋችንንም ለነፍሳችን ልናስገዛም ይገባል።


ጾም ከምግብ መክልከል ሥጋን ማድከም ነፍስን ማለምለም እስከሆነ ድረስ ምግብ ቤቶቻችን በአንጻሩ ምነው በምግብ ማስታወቂያ ለዚያውም ለመጾም በማይጋብዙ የምግብ ዝርዝሮች ጠብ እርግፍ አሉ?


የምግብ ቤቱን አነሳን እንጂ ከወትሮው በተሻለ በየሁላችን ቤት ከፍስኩ ጊዜ ይልቅ የምግብ አይነቱ በጾም ወቅት አይደለምን? ከዚህ ምን እናተርፋለን? ወይንስ እንዲሁ እንዘጭ እንዘጭ ነው?


መጾም ይገባልና ከመብላትም በጣም ይሻላልና ጾመን በረከትን እናግኝ፣ በደላችንንም እናስቀር፣ ስንጾም ብልቶቻችን ሁሉ (ዓይን፣ ጆሮ፣እግር፣ አንደበት፣ወዘተ) ይጹሙ። 


የጾም ምግብ ቤቶችም በስመ ጾም ከመነገድ ቢታቀቡ መልካም ነው፤ እኛም ስንመገብ በማካካሻ መልክ በሚመስል ባንመገብ መልካም ነው።


ስለ አጽዋማት ያለን አመለካከት ይቀየር የቄስ፣ የመነኩሴ፣ የሕጻናት፣ የሚባል ጾም የለም። እድሜው ሰባት አመት የሞላው የጤና እክል እና በንሰሐ አባቱ በኩል በተለያዩ ምክንያት ከሚፈቀድ በቀር ሰባቱም ጾሞች ሊጾሙ ይገባቸዋል።


" ከዚህ ከታዘዘው አብልጦ የጾመ ግን ዋጋው ይበዛለታል። " እንዲል።


አብዝተን ጾመን የበረከቱ ተሳታፊ ለመሆን ያብቃን። ጾሙ የሐጥያት መደምሰሻ፣ የዲያብሎስ ድል መንሻ፣ የመንግሥተ ሰማያት መውረሻ ያድርግልን።

አሜን።

ይቆየን።


@deressereta


comment እና subscribe ማድረግ አይርሱ

እነዚህን ነቢያት እኔ አላክኋቸውም

 " እነዚህን ነቢያት እኔ አላክኋቸውም "


ትንቢተ ኤርሚያስ 23 : ከቁጥር 9 ጀምሮ ብናነብ እግዚአብሔር በሐሰተኞቹ በሰማሪያ ነቢያት ምን ያህል እንደተማረረ እንመለከታለን። እነዚህን ነቢያት እኔ አላክኋቸውም እስኪል ድረስ።


ወዳጄ ብዙ ሰው ያውቅህ ይሆናል፤ ታዋቂነትህም ከአገር አገር የናኘ ሊሆን ይችል ይሆናል። ብዙ ተከታዮችም ይኖርህ ይሆናል። በዚህም የተነሳ ክብርህ ጥግ ደርሶ ሊሆን ይችላል።


ነገሮች ሁሉ ተቃንተውልህ የትናንት ሕይወትህ ተቀይሮ ሊሆን ይችላል። የመርገም አንደበትህ የምርቃት፣ የውሸት አንደበትህ የእውነት የሆነውን ቃል ትጠቅስበት ይሆናል፣ የድህነት ታሪክህ በባለጸግነት፣ ማይምነትህ በአዋቂነት ሥም ተተክቶልህ ሊሆን ይችላል፣ የትናንቱ እግረኛ ዛሬ የዘመናዊ መኪና ባለቤት ሆነህ ሊሆን ይችላል፣ በአጠቃላይ ታሪክህ ተቀይሯል።


ስለ እውነት አንተ ተቀይረሃል? 


ባለጸጋ ስትባል ነፍስህን አላጎደልካትም?


ለሌሎች የእግዚአብሔርን ቃል እንደ ወተት ስትግት አንተ ግን ቃሉን አልተጠማህምን?


ምድራውያን ሰወች ሲያከብሩህ ዋጋህን በምድር ስትቀበል በሰማይ ያለውን የአባትህን ዋጋ አልተነጠክም?


ነብይ ነኝ ስትል፣ ሐዋሪያ ነኝ ስትል፣ ወንጌላዊ ነኝ ስትል፣ አገልጋይ ነኝ ስትል፣ አጥማቂ ነኝ ስትል፣ ባህታዊ ነኝ ስትል፣ ወዘተ ብዙዎች ሁሉን ትተው ተከትለውህ አደባባዮችህ ደምቀው መድረኮችህ ጠጠር መጣያ እንኳን ጠፍቶ ሊሆን ይችላል። ወዳጄ በእግዚአብሔር ዘንድ እንደ አለመታወቅ አሳፋሪ ነገር የለም።


እግዚአብሔር በሚያውቅህ ልክ እንጂ ዋጋህን የምትቀበለው በታዋቂነትህ ልክ አይደለም።መድረክህ ስትይዝ የእግዚአብሔርን ቃል ጠንቅቀህ ማወቅህ እንጂ ታዋቂነትህ ለአድናቆትህ ሽፋን እንጂ የሚሆንህ ለመዳንህ ምክንያት አይሆንህም።


እነዚህን ነቢያት እኔ አልላኳቸውም እንደመባል አሳፋሪ ነገር የለም። አንተ ከየትኛው ነህ?


ወዳጄ አንተ የምትከተለው "አገልጋይ" ከየትኛው ወገን ነው? ተከታዮቹ ስለበዙ መድረኩ ስለደመቀ፣ ድምጹ ነጎድጓዳማ ስለሆነ፣ የልብህን መሻት ስለሚነግርህ፣ ስለማይገስጽህ፣ ወይንስ የእግዚአብሔር አገልጋይ ስለሆነ ነው?


• 2ኛ ቆሮንቶስ 11 : 13

" እንደ እነዚህ ያሉ ሰዎች የክርስቶስን ሐዋርያት እንዲመስሉ ራሳቸውን እየለወጡ፥ ውሸተኞች ሐዋርያትና ተንኮለኞች ሠራተኞች ናቸውና። "

ስለሚልባቸው በእነርሱ ላይ ያለው እናንተ እየተከተላችሁት ያለው መንፈስ የትኛው እንደሆነ መርምሩ " መንፈስን ሁሉ አትመኑ "ይላልና።

• 2ኛ ጢሞቴዎስ 3 : 1- 6

ነብያትን ነን እያሉ ምእመናንን የሚያስጨንቁ፣ ሐብትና ንብረትን የሚነጥቁ፣ ሴቶችን ከክብራቸው የሚያነውሩ፣ ቃለ እግዚአብሔርን ቁጭ ብለው ሳይማሩ ቆመው የሚያስተምሩ፣ ርኩስ መንፈስ የሚጫወትባቸው ናቸው።


ገንዘብን ከመውደዳቸው የተነሳ የማያደርጉት ነገር የለም፤ ትእቢተኞች እና ተሳዳቢዎች ናቸው። ክብራቸው በነውራቸው ሐሳባቸው ሁሉ ምድራዊና ብልጭልጩ አለም የሆነ። ጽድቅን በምድራዊ ስኬታቸው የሚያወዳድሩ ከንቱዎች ናቸው።


የእግዚአብሔርም ቃል ከነዚህ ራቁ ይለናል። ተከታዮቻቸው ግን ብዙ ናቸውና የተቀሩትም የተከታዮቻቸውን ብዛት ተመልክተው ይከተሏቸዋል። 


ጠማማ ትውልድ ምልክትን ይሻልና 'ድንቅ ተአምር' እናያለን፣ 'ፈውስ' እናገኛለን፣ በማለት በሐሰት ትርክታቸው ተታለው እዚያው ይቀራሉና ከነዚህ ደግሙ ራቁ ለማለት እወዳለሁ።


" ነገር ግን በመጨረሻው ቀን የሚያስጨንቅ ዘመን እንዲመጣ ይህን እወቅ። ሰዎች ራሳቸውን የሚወዱ ይሆናሉና፥ ገንዘብን የሚወዱ፥ ትምክህተኞች፥ ትዕቢተኞች፥ ተሳዳቢዎች፥ ለወላጆቻቸው የማይታዘዙ፥ የማያመሰግኑ፥ ቅድስና የሌላቸው፥ ፍቅር የሌላቸው፥ ዕርቅን የማይሰሙ፥ ሐሜተኞች፥ ራሳቸውን የማይገዙ፥ ጨካኞች፥ መልካም የሆነውን የማይወዱ፥ ከዳተኞች፥ ችኩሎች፥ በትዕቢት የተነፉ፥ ከእግዚአብሔር ይልቅ ተድላን የሚወዱ ይሆናሉ፤ የአምልኮት መልክ አላቸው ኃይሉን ግን ክደዋል፤ ከእነዚህ ደግሞ ራቅ። "


ሐሰተኛ ነቢያት እንደመኖራቸው መጠን እውነተኞች መኖራቸው እሙን ነው። ቃሉም ስለ እውነተኞቹ ነቢያት ሲናገር እናያለን ኤርሚያስ 1 : 5 እና ሕዝቅኤል 3 : 17 እንዲሁም የሐዋርያት ሥራ 9 : 15 ላይ ይመሰክርላቸዋል።


ከእናታቸው ማህጸን ጀምሮ የተመረጡ እንዳሉ የተለያየ አገልገሎትም እንደሰጣቸው ለሕቡም ጠባቂ እንዳደረጋቸው እናያለን።


ነቢዩ ኤርሚያስ ግን በእግዚአብሔር ተገብቶ እንዲህ እያለ ይናገራል።


" እኔ ሳልልካቸው እነዚህ ነቢያት ሮጡ፤ እኔም ሳልነግራቸው ትንቢትን ተናገሩ። በምክሬ ግን ቢቆሙ ኖሮ፥ ለሕዝቤ ቃሌን ባሰሙ ነበር፥ ከክፉም መንገዳቸው ከሥራቸውም ክፋት በመለሱአቸው ነበር። አለምሁ አለምሁ እያሉ በስሜ ሐሰትን የሚናገሩትን የነቢያትን ነገር ሰምቻለሁ። " 


ቃሉ እነዚህን ራሳቸውን ነቢያት ነን ባዮችን እግዚአብሔር እንደማያውቃቸው ያስረግጥልናል።


ስለዚህ እግዚአብሔር ቅር ከተሰኘበት መንገድ እንድንመለስ ሰውንም ከመከተል እንድንታቀብ በሐሰተኞቹም እንዳንታለል አደራ እላለሁ።


ይቆየን።


@deressereta

እግዚአብሔር ያዘዘኝን አደርጋለሁ

 "እግዚአብሔር ያዘዘኝን አደርጋለሁ እንጂ እኔ አዝዛለሁን?"


ሀብተ መርገም እና ሀብተ በረከት የተሰጠው በለአም ለባላቅ የመለሰው ምላሽ ነበረ።


እስራኤል ከግብጽ ሲወጡ አሕዛብን ድል እየነሱ ሲመጡ በባላቅ ወልደ ሶፎር አገር አጠገብ በሞዓብ ሜዳ በሰፈሩ ጊዜ የእስራኤላውያንን ጥንተ ታሪክ ያውቅ ነበረና እጅግ ፈራ።


ፈርቶም አልቀረ በአሞራውያን ላይ ያደረሱት በርሱና በሕዝቡ እንዳይደርስ በለአምን ና እና ርገምልኝ አለው።


በለአምም እስራኤላውያን የእግዚአብሔር ሰወች እንደሆኑ የተባረኩም ሕዝብ እንደሆኑ ያውቅ ነበረና፣ እግዚአብሔርም አትርገማቸው ብሎታልና ላይረግማቸው ላይሄድ ወሰነ። 


ባላቅም ከአንዴም ሁለቴ ከጥሩ ገንዘብ ጋር ሰው ላከበት ሆኖም በለአም ሳይመጣ ቀረ፤ በመጨረሻም እግዚአብሔር በራእይ ለበለአም እንዲህ አለው " መሔዱን ሒድ ነገር ግን እግዚአብሔር የገለጠልህን ተናገር እንጂ አትራገም" አለው።


እንደሄደም እስራኤላውያንን ከአንዴም ሶስቴ መረቃቸው፥ ባላቅም ተቆጣ። "ርገምልኝ አልኩህ እንጂ መርቅልኝ አልኩህን?" አለው።


"እግዚአብሔር የገለጸልኝን እናገራለሁ እንጂ ሌላ ምን ላደርግ እችላለሁ?" ብሎ በለአም መለሰለት።


በማግስቱም እንዲሁ ሆነ ሰባት ላም፣ ሰባት ዳንግሌ ሠዋለት። በለዓምም እንደ ልማዱ ያሟርት ጀመረ። ነገር ግን ዛሬም መራገም አልተቻለውም።


መጽሐፍም እንዲህ ታሪኩን ያስነብበናል፦ " እግዚአብሔር እንደ ሰው ሐሰት አይናገርም፣ በሠራውም ሥራ አይጸጸትም እኔ እስራኤልን እንድመርቅ ትእዛዝ ተቀብያለሁና በያዕቆብ ክፋት አላይበትም። እግዚአብሔር አምላክ ከእርሱ ጋራ ነውና። በያዕቆብ ላይ አስማት የለም፣ በእስራኤልም ላይ ሟርተኝነት አይቻልም። ይህ ሕዝብ እንደ አንበሳ ደቦል ነው። ያንበሳ ደቦል የሰበሰውን ሥጋውን ሳይበላ፣ ደሙን ሳይጠጣ እንዳይመለስ ይህ ሕዝብም አሕዛብን ሳያጠፋ አይመለስም" ይለናል 


ባላቅም ያሰበው ባይሳካ ያላሰበው እንዲሆንበት አልፈለገምና  በተስፋ መቁረጥ ውስጥ " መራገም ቢቀር እንኳን ባይሆን መመረቁን አትተውምን? ይህን ሕዝብ ለምን ትመርቀዋለህ?" አለው።


በርእሳችን እንዳነሳነው በለአም መለሰለት፥ " እግዚአብሔር ያዘዘኝን አደርጋለሁ እንጂ እኔ አዝዛለሁን?" አለው።


ድንቅ መልስ ነው።


ይህ ታሪክ በበለአምና በባላቅ መካከል፣ በእስራኤላውያን እና በባላቅ አገር ሰወች መካከል የሆነ የተመዘገበ ቢሆንም ቅሉ የእግዚአብሔር ቃል፣ የእግዚአብሔር ፈቃድ፣ ግን ቦታ የማይገድበው ጊዜ የማይሽረው ነውና እራሳችንን እንመልከትበት።


እኛ የማንን ፈቃድ እናደርጋለን? የሥጋን ፈቃድ ነው የነፍስን ፈቃድ እንፈጽማለን? በገንዘብ እንገዛለን ለእግዚአብሔር እንገዛለን? እንመርቃለን ወይንስ እንረግማለን?


አለማችን እንዴት ሰነበተች? ብለን በእግዚአብሔር መንፈስ ብንቃኘው  በውኑ የእግዚአብሔርን ሕዝብ የሚሳደብ፣ የእግዚአብሔርን አገልጋይ ካህናትን እና በቤቱ የሚመላለሱትን፣ እግዚአብሔር የመረጣቸውን እና የቀባቸውን የሚያንጓጥጥ ነው የሞላው ወይንስ የሚመርቃቸው?


የባላቃዊያን ሀሳብ የፈለገውን ቢሆንም የእግዚአብሔርን ፈቃድ መሻር አልተቻለውም። እግዚአብሔር የመረጣቸውን ማንም አይቃወማቸውምና። 



ኢትዮጵያ እና ኢትዮጽያዊያንም እንደዚሁ ናቸው፤። የማንም ሰልፍ አያሸንፋቸውም። የማንም ሟርት እና እርግማን አይደርስባቸውም። አንድነታቸውና ህብረታቸውም የኢትዮጵያን ጉዞ አይገታም። እግዚአብሔር ከርሷና ከሕዝቦቿ ጋር ነውና።


እንደ ፈቃዱ ተመላልሰን የእግዚአብሔር ሕዝቦች እንደተባልን ጸንተን ቆይተን እግዚአብሔር አጥር ቅጥር ይሁነን። ከጠላቶቻችን ይጠብቀን፣ የተቃጣብንን ይመክትልን፣ በመርገም ፈንታ ይመርቀን፣ መውጣት መግባታችንን በአባታዊ አይኑ ይከታተልልን።


የጠላቶቻችንን ዓይን ጨለማ ጉልበታቸውን ቄጠማ ያድርግልን።


በእግዚአብሔር ማመናችን መዘባበቻ ሳንሆን መጽናኛ ይሁነን።


የአባቶቻችን በረከታቸው ጥርጥር የሌለባት ተዋህዶ እምነታቸው በረከቷ ይደርብን።


የተጀመረውን ጾም ሥጋችንን ገዝተን፣ ነፍሳችንን አበርትተን ጠላት ዲያቢሎስን ድል የምንነሳበት የእግዚአብሔርን መንግሥት የምንወርስበት ያድርግልን።


@deressereta

እንተወው

 "እንተወው"


መጋቢ ሐኪስ እሸቱ ሁሌም በጨው እንደተቀመመ ቃላቸው ሁሌም ይጥመኛል።


እንዲህ ይላሉ፦ "እንተወው ... ካልተውንው እና የሆነብንን፣ እየሆነ ያለውን፣ ሊሆን ያለውን ካሰብን አይደለም ከሰው ጋር ያለን ጉዳይ ይቅርና ትዳራችንን እስክንፈታ ድረስ የሚሄድ ጉዳይ ነው ይላሉ።" 


እውነት ነው ካልተውነው በቀር ስለ አገራችን ፖለቲካ እና ፖለቲከኞች፣ ስለ አገራችን እምነቶች እና በእምነቱ ስም ስለሚተውኑ ሰወች፣ የኑሮ ሁኔታ እና ኑሮውን ስለሚዘውሩ ሰወች፣ ስለ ሶሻል ሚዲያው እና በሶሻል ሚዲያው እንጀራቸውን ስለሚጋግሩ ሰወች፣ ወዘተረፈ የምናውቀውን እንናገር ካልን ጓደኝነታችን አይደለም ትዳራችን ይፈርሳል።


 መንደራችን፣ ብሔራችን፣ ቤተእምነታችን፣ ቡድናችን፣ ፓርቲያችን፣ ወዘተ ይፈርሳል። 


ከመጋቢ ሐዲስ እሸቱ አለማየሁ በተማርኩት መሠረት ስለምታውቅ፣ መረጃው ስላለህ፣ ከሁነኛ ሰው ስለሰማህ፣ አትንገር ብለው ስለነገሩህ፣ ... ሁሉ ነገር አይነገርም።


አንተ የደረሰብህ ጉዳይ ፀሐይ የሞቀው አገር ያወቀው ምስክር ጥራ ብትባል አገር ምድሩ ግልብጥ ብሎ ስለሚመሰክርልህ በሕግ ፊት ፍትህ ስለምታገኝ ሁሉ ነገር አይወራም።


መረጃ ማስረጃ አቅርበህ፣ ጠበቃ አቁመህ መርታት ስለምትችል ሁሉ ነገር አይወራም።


አንዳንዴ ጊዜ የሚፈታው፣ አንዳንዴ ለምጣዱ ሲባል አይጧን እንደምታልፋት ሁሉ ዝም ብለህ ማለፍ ትተህ የምታልፈው ነገር እንዳለ መተው ግድ የሆነበት ጊዜ እንዳለ ልብ በል።


@deressereta

ማክሰኞ 22 ዲሴምበር 2020

የዳሰሱትም ሁሉ ዳኑ

 "የልብሱንም ጫፍ ብቻ ሊዳስሱ ይለምኑት ነበር፤ የዳሰሱትም ሁሉ ዳኑ።" 

/ማቴ 14፣36/
ደረሰ ረታ
13/04/2013ዓ.ም
$$$$$$$$$=====
በዓለም ላይ ብዙ ሐኪሞችና ብዙ ባለ መድኃኒቶች አሉ፡፡ ሐኪሞቹ መድኃኒት ያዝዛሉ እንጂ ራሳቸው መድኃኒት አይሆኑም፡፡

ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ሐኪምም መድኃኒትም ነው፡፡
እሱ የሥጋና የነፍስ መድኃኒት ነው፡፡ ሥጋ በቊስል፣ ነፍስ በኃጢአት ሲታመሙ ገዳዩን ገድሎ የሚያድነው መድኃኒት ኢየሱስ ክርስቶስ የድንግል ማርያም ልጅ ብቻ ነው፡!!

ሕክምናው ሲያድን ሲፈውስ ጠባሳ አያስቀርም።
ሲያድን ቀስ ብለህ አይደለም የምታገግመው አልጋህን ተሸክመህ ነው የምትሄደው። አስታማሚዎችህ ለርሱ ሲነግሩት ነው አንተ እቤት ሆነህ ከበሽታህ የምትገላገለው። እመን እንጂ ሲምርህ የጠሉህ ሁሉ ናቸው ጠብ እርግፍ የሚሉልህ፣ የገፉህ ያገለሉህ ሁሉ መንገድ ይመሩሃል፣ መንገድ ይለቁልሃል፣ በወንበራቸው ያስቀምጡሃል። ጠረንህን አጥፍቶ የማይታመን መአዛ ያውድሃል።

በእጁ መዳን ከእርሱ ወዲያ አዳኝ ከእርሱ መድኃኒት እንደሌለ ካመንክ እንኳንስ ዳሰኸው ጨርቁን ነክተህ ጥላው ሲያርፍብህ ስሙን ስተጠራ ትድናለህ።

ድንቅ አይበልህ እንኳን እርሱ በእርሱ የሚያምኑ ለሥሙ የሚገዙ እርሱ የሚያደርገውን ከርሱም በላይ ያደርጉ ዘንድ ስልጣን ተሰጥቷቸዋልና። ቅዱሳኑም ያድናሉ በጨርቃቸው እራፊ/ቁራጭ እና በጥላቸው ሳይቀር።

እነርሱ ስሙን ጠርተው ''በኢየሱስ ስም'' ሲፈውሱ አጋንንትን ሲያሳድዱ እርሱ ግን በሃይሉ እና በስልጣኑ በእርሱ ፈቃድ በአባቱ በአብ ፈቃድ በመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ ይህን ያደርጋል።

በዚህ የመጽሐፍ ክፍል ጌታችን መደኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብዙዎችን እያዘነላቸው አድኗቸዋል። አንደኛው ከደቀመዛሙርቱ አንዱ የሆነውን ቅዱስ ጴጥሮስን ሲሆን ሌላኛዎቹ የጌንሴሬጥ ሰዎችን ነበረ። የመጀመሪያ ሰው ቅዱስ ጴጥሮስ የእጁን ተአምራት የቃሉ ትምህርት የተከታተለ ብዙ ልምድ የነበረው ሲሆን የጌንሴሬጥ ሰዎች ይህ እድል ከዚህ ቀደም አልነበራቸውም። ይህንንም እድል ያገኙት ከታንኳ ወርዶ ወደ መንደራቸው ገብቶ ባገኙት ጊዜ ነበረ።

እነዚህንም ከመፈወሱ አስቀድሞ ከቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ቀብር መልስ ብዙዎችን እንደፈወሰ መጽሐፍ ይናገራል።በዚሁ ምእራፍ ቁጥር 14 ላይ ''ወጥቶም ብዙ ሕዝብ አየና አዘነላቸው ድውዮቻቸውንም ፈወሰ።'' ይለናል።

እነዚህ የጌንሴሬጥ ሰወች ማን እንደሆነ ባወቁ ጊዜ በአከባቢው ባሉ በሽተኞች ዘንድ ሁሉ ሰው ላኩ የታመሙትንም ሁሉ በአንድ ሰበሰቧቸው።

ከባንኮክ፣ ከአውሮፓ፣ ከአሜሪካ፣ ከኤሸያ እውቅ የጤና ባለሙያዎች ቡድን ስለመጣ፤ አልያም የኩላሊት፣ የልብ፣ የዲስክ መንሸራተት፣ የውስጥ ደዌ እስፔሻሊስት ቡድን ስለመጣ ብለው አልነበረም የሰበሰቧቸው በደዌ ዳኛ በአልጋ ቁራኛ የተያዙትን ሁሉ እንጂ።ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በበሽታ ላይ ሳይሆን በመፈወስ ላይ ስፔሻላይዝ ያደረገ ነውና።

የተሰበሰቡት ሁሉ፦''የልብሱንም ጫፍ ብቻ ሊዳስሱ ይለምኑት ነበር፤ '' በእርሱ ዘንድ የካርድ የከፈለ የመድኃኒት መግዣ ያለው ጥሩ ዘመድ ያለው ሳይሆን የሚድነው ሁሉም ነው። ለዚህም ነው ማቴዎስ ''የዳሰሱትም ሁሉ ዳኑ'' ያለን።

በዓለማችን፣ በአህጉራችን፣ በአገራችን፣ በከተማችን፣ በመንደራችን፣ በቤታችን ሥንት ሰው አለ በደዌ የተያዘ? ሥንት ሰው አለ መዳን የሚገባው? የጌታን መምጣት ወደ እኛ መቅረብ ሰምቶ ወጥቶ አይቶ ማንነቱን ተረድቶ መፈወሰ፣ መዳን ያለበት፤ ጌታ በደጅ ቆሟል ሁላችንም ከማዳኑ እንሳተፍ።

ጥቂት የማይባሉ አዳኙን አምላክ (ሎቱ ስብሐት) ለስም አጠራሩ ክብር ይግባውና እንደ ፍጡር እያዩት አማላጅ ይሉታል።እንደ ጌንሴሬጥ መንደር ሰዎች ማንነቱን የምንለይበትን አእምሮውን ለብዎውን ፈጣሪ ያድለን።

ወደ ጌንሴሬጥ ከመግባቱ አስቀድሞ ቅዱስ ጴጥሮስንና የተቀሩትን ደቀመዛሙርት አግኝቷቸው ነበረ።

"ሕዝቡንም አሰናብቶ ይጸልይ ዘንድ ብቻውን ወደ ተራራ ወጣ። በመሸም ጊዜ ብቻውን በዚያ ነበረ።
ታንኳይቱም አሁን በባሕር መካከል ሳለች፥ ነፋስ ከወደ ፊት ነበርና በማዕበል ትጨነቅ ነበር።ከሌሊቱም በአራተኛው ክፍል ኢየሱስ በባሕር ላይ እየሄደ ወደ እነርሱ መጣ።ደቀ መዛሙርቱም በባሕር ላይ ሲሄድ ባዩት ጊዜ፡— ምትሐት ነው፡ ብለው ታወኩ፥ በፍርሃትም ጮኹ።ወዲያውም ኢየሱስ ተናገራቸውና፡አይዞአችሁ፥ እኔ ነኝ፤ አትፍሩ፡ አላቸው። ጴጥሮስም መልሶ፡— ጌታ ሆይ፥ አንተስ ከሆንህ በውኃው ላይ ወደ አንተ እንድመጣ እዘዘኝ፡ አለው። እርሱም፡— ና፡ አለው። ጴጥሮስም ከታንኳይቱ ወርዶ ወደ ኢየሱስ ሊደርስ በውኃው ላይ ሄደ።ነገር ግን የነፋሱን ኃይል አይቶ ፈራ፥ ሊሰጥምም በጀመረ ጊዜ፡— ጌታ ሆይ፥ አድነኝ፡ ብሎ ጮኸ። ወዲያውም ኢየሱስ እጁን ዘርግቶ ያዘውና፡— አንተ እምነት የጎደለህ፥ ስለምን ተጠራጠርህ? አለው።
ወደ ታንኳይቱም በወጡ ጊዜ ነፋሱ ተወ። በታንኳይቱም የነበሩት፡— በእውነት የእግዚአብሔር ልጅ ነህ፡ ብለው ሰገዱለት።ተሻግረውም ወደ ጌንሴሬጥ ምድር መጡ።"

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የለመኑት ፈቃዳቸውን እንደፈጸመላቸው ቅዱስ ጴጥሮስ ማሳያ ነው በባህሩ ላይ እንዲራመድ ፈቅዶለታልና፤ ለተራቡት በልተው ጠግበው እስኪተርፋቸው መግቧቸዋል። ማእበሉን ጸጥ አድርጓል። ከዚህ በኃላ ነው የእግዚአብሔር ልጅነቱን ሲያምኑ ማዳኑን ያሳያቸው፤ የዳሰሱትም ሁሉ የዳኑት።

እኛ የአዲስ ኪዳን ትውልድ ሁላችን በአባቶቻችን በኩል ኢየሱስ ክርስቶስን አይተነዋል፣ ዳሰነዋል፣ አብረን በልተን ጠጥተናል፣ ስንቶቻችን መዳን ተደሮጎልናል?

የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ እንዳወቁ የልብሱን ጫፍ ብቻ ሊዳስሱ ይለምኑት ነበረ፤ እግዚአብሔር ዛሬ በአካለ ሥጋ በመካከላችን ቢመላለስ/ ለጸሎት በፊቱ ስንቆም የምንለምነው ምን ይሆን?

መዳን?

ብርና ወርቅ?

ቤትና መኪና?

ስልጣን?

ረጅም እድሜ?

ወይስ ... ምን ይሆን ልንለምነው የምንከጅለው?

ጌታን የአምስት ገበያ ያህል ሰው ይከተለው ነበረ ይላል ቅዱስ መጽሐፍ ነገር ግን ከ120 ቤተሰብ ውጭ ያለው አብዛኛው ገሚሱ ውብ ነበረና ደም ግባቱን ለማየት፣ ገሚሱ ደግሞ የእጁን በረከት እና ተአምራት ለመካፈል እና ለማድነቅ፣ የተቀሩትም ከቃሉ ትምህርት ስህተት ለመቃረም ነበረ።

እኛስ፥
• ክርስቲያን የመሆናችን ዋናው ዓላማ ምንድነው ?
• ለምንድንነው የምንከተለው?
• ግባችን ምንድነው ?
• አሁን የት ነው ያለነው?
• ከክርስትና ዓላማችን አንጻር አካሄዳችን እንዴት ነው?
• እያንዳንዳችን አሁን በዚህ ሰአት በፊቱ ለፍርድ ብንጠራ ምን ይለን ይሆን? ኑ እናንት የአባቴ ብሩካን የምንባል ነን? ወይስ,... ካልሆነ እስክንጠራ ምን እያደረግን ነው? (የንስሐ ፍሬ እናፍራ)
የእግዚአብሔር ልጅ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ (እግዚአብሔር ወልድ) ማዕበሉን ጸጥ ያድርግልን፤ ከውስጥ ከውጭ የሚንጠንን የፍርሃት ማዕበል ቀጥ ያድርግልን። በደዌ ዳኛ በአልጋ ቁራኝነት የተያዙትን ይፈውስልን፤ በዘረኝነት ደዌ በጽንፈኝነት ደዌ ከመመታት እግዚአብሔር ይጠብቀን። በክርስትና ሕይወታችን መጡ ሄዱ፣ ነበሩ የሉም፣ አመኑ ካዱ ከመባል ይሰውረን። ማመናችን፣ እርሱን መከተላችን ቸርነቱ ተጨምሮበት ጽድቅ ሆኖ ይቆጠርልን። እረኛው እንደተመታበት መንጋ ከመሆን ይጠብቀን።

በእዝነ ልቡናችን አይተነዋል፣ ሰምተነዋል፣ ዳሰነዋልና መዳን ይሁንልን።
በቀረው ዘመናችን ንሰሐ ገብተን ለዘለዓለም የማያስጠማውንና የማያስርበውን ሥጋውና ደሙን ተመግበን ለርስቱ ወራሾች ለመሆን ያብቃን።
ይቆየን።
@ deressereta


እሑድ 29 ኖቬምበር 2020

ቢቻላችሁ ከሰው ሁሉ ጋር በሠላም ኑሩ

 ቢቻላችሁ ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ

#######################

ደረሰ ረታ

ክፍል አንድ


የሰው ልጅ በምድራዊ አኗኗሩ ከሰው ጋር ሲኖር አኗኗሩን የሚለካበት ሶስት ዋና ዋና ሥፍራዎች አሉት።

1. በመኖሪያ ቤት እና አካባቢው

2. በመሥሪያ ቤት

3. በቤተክርስቲያን

ከነዚህ የአኗኗር ዘይቤ የወጣ ማንነት የለንም። ምናልባት እውነተኛዎች በረኸኛ መናኒ ባህታውያን ካልሆኑ በቀር፤ የከተማ ባሕታውያንን ሳይጨምር።


ከላይ ለተጠቀሱት እንደ ሰው የምንኖርባቸው ሥፍራዎች ዋና መሰረቱ መቻቻልና መከባበር ናቸው ከዚህ የወጣ አላማ የለውም።


በጥቂቱ ለመዳሰስ ከመጽሐፍ ቅዱስ ባሻገር ሁለት መጻሕፍትን ዋቢ አድርገን ዳሰሳችንን እንቀጥላለን። "ክርስትና በማኀበራዊ ኑሮ" ኅሩይ ስሜ እና ዳዊት ደስታ ያዙጋጇቸው እንዲሁም "በኢትዮጵያ የሃይማኖት መቻቻል አለን?" በብጹዕ አባኑ ሳሙኤል የተዘጋጁ።


መልካም አኗኗር ለመልካም አስተዳደር ትልቅ ሚና ስለሚጫወት አሰናስለን እንመለከታለን።


የሰው ልጅ ከ22ቱ ሥነ ፍጥረት የሚለይበት አንዱና ዋነኛው ነገር በሕግ እና በሥርአት መኖሩ እና አንዱ የሌላኛውን መብት እና ነጻነት አክብሮ መኖሩ ነው።


ከሌላው ዓለም ኢትዮጵያውያንን ለየት የሚያደርገን ባህሪይ እና ባህል አለን። ባህላችን እንግዳ ተቀባይ ሕጋችን ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ ሰውን አክባሪ መሆናችን ነው።


ለነዚህም ተግባራችን እንደ ምሳሌ በቀዳሚነት የምንመለከተው "ኢትዮጵያውያን የሰውን ሰብአዊ መብት በመጠበቅ አንፃር በመልካም አስተዳደር ሂደት በ70 ዓ.ም በጥጦስ አማካኝነት የኢየሩሳሌም ቤተ መቅደስ ሲፈርስና ኢየሩሳሌም ስትወረር በርካታ አይሁዳውያን ፈላሻዎች ኢትዮጵያ ውስጥ መጥተው ኖረው ምንም እንኳን ኢትዮጵያ የክርስትናን ሃይማኖት ገና በ34 ዓ.ም በኢትዮጵያዊው ጃንደረባ አማካኝነት ብትቀበልም (የሐዋርያት ሥራ 8:29) አይሁድ ክርስቶስን የሰቀሉ ናቸው በማለት ማረፊያ አልተከለከሉም።" 


የሰው ልጅን አክባሪነቱ ከመጽሐፍ ቅዱስ አስተምሮ የመነጨ ነው፦ የራሱን ፈቃድ ሲፈጽም የሌላውን ወገኑንም ሆነ ባለጋራውን (ጠላቱን) ጨምሮ ህሊና ጠብቆ የሚኖር ነው። 1ኛ ቆሮንቶስ 8:11 " ሰዎች በአንተ ላይ ሊያደርጉብህ የማትፈልገውን ነገር እንዲሁ በባልንጀራህ ላይ አትፈጽም ሰዎች ሊያደርጉላችሁ የምትሹትን በሙሉ እናንተም እንዲሁ አድርጉላቸው" በሚል መርህ የሚመራ ነው።


ከሕግም አንጻር የእያንዳንዱን ግለሰብ ተፈጥሯዊ እና መሠረታዊ የሆኑትን መብቶች ያከብራል። ለማስከበርም ይጥራል። እነዚህም፦

1. ፖለቲካዊ ነጻነት

2. ማህበራዊ ነጻነት

3. ኢኮኖሚያዊ ነጻነት ናቸው።

ከሕግ አግባብ እነዚህን ሶስት ነጻነቶች በጠንካራ መሠረት ላይ ከታነጹ ሕዝብም አገርም አትናወጽምና።


ለክርስቲያኖች ቅድስት ቤተክርስቲያን ከልደተ ክርስቶስ አስቀድሞ ከሙሴ ሕግ ጀምሮ እስከ አዲስ ኪዳን ሕግ ድረስ ትምህርቷ ፍቅር፣ ሠላም፣አንድነት፣እኩልነት ነው። "ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ" በሚል አስተምሮ ታንጻለች።


ከዚህ በመነሳት የሌሎች አገራት ዜጎችና መሪዎች እምነት ተከታዮች ሳይቀር ይሰደዱባታል፤ ይጠለሉባታልም። የእስልምና እምነት ተከታይ ወገኖቻችን፣ የፖለቲካ መሪው ኒንሰን ማንዴላ፣ ማህተመ ጋንዲ፣ የተለያዩ አገራት ስደተኞች ማሳያዎች ናቸው። በግንባራችን እንጂ በጀርባችን ጥይት አይመታንም ያሉ ጀግኖች አባቶቻችን ይህችን ድንቅ አገር እስከ ሙሉ ክብሯ አስረክበውናል። እኛስ?


ዛሬ ከላይ የጠቅስናቸው ተግባራትና መገለጫችን እየቀጨጩ ይገኛሉ። እኛ ዘመን ጋር ሲደርሱ ለምን ይህ ሆነ?


ዘመኑን ካየን የዘመነ፣ የሰለጠነ፣ በእውቀት የመጠቅንበት፣ በሳይንስና ቴክኖሎጂ የታገዝንበት ሲሆን ደካሞች ነን።


• ከባቢያዊ ግጭቶች በርክተዋል

• ሽብራዊ አመጽ በተለያዩ ሥፍራ ይቀሰቀሳል

• የጦር መሣሪያ ዝውውር በርክቷል

• ዓለም አቀፍ ይዘት ያላቸው በሽታዎች/ወረርሽኞች ተበራክተዋል።

ነገር ግን ይህንን ማስቀረት አልቻልንም። ለምን?


ዲሞክራሲ የብዙሃን የበላይነት የሚረጋገጥበት የአናሳዎች መብቶች የሚከበርበት ሥርዓት ሲሆን ሥልጣንን መሰረት በማድረግ አናሳዎች የበላይነት እየወሰዱ የሚገኙበት ሁኔታ ላይ እንገኛለን። በፖለቲካ ሴራ የብሔር ግጭት፣ የሃይማኖት ግጭት፣ እየተከሰተ ይገኛል። ሲፈተሽ ችግሩ የመልካም የማኀበራዊ ኑሮ አኗኗር ችግር/ውስንነት እንደሆነ ይታመናል። ይህም ተጽዕኖ በመልካም አስተዳደር እጦት ላይ ጠባሳውን ያሳርፋል ብሎም የፍርድ መጓደልን የድሃ መበደልን ያስከትላል። ይህ ሆኖ ሲገኝ እንኳን የዲሞክራሲን መኖር ማረጋገጥ ይቅርና ወጥቶ መግባት በስጋት ይሆናል። እኩልነት ቀርቶ የጥቂቶች የበላይነት ይሰፍናል። የብሔረሰብ እኩልነት፣ የእምነት ተቋማት እኩልነት፣ የባህል እኩልነት፣ የፖለቲካ እኩልነት፣ ኢኮኖሚያዊ እኩልነት፣ ማህበራዊ እኩልነት፣ የአስተዳደር እኩልነት አይኖርም። ልማትና ሠላም አይኖርም።


ስለዚህ ቅድስት ቤተክርስቲያን እና ምእመናን በአንድነት በሃይማኖታዊ እና በማሕበራዊ ተግባራት በብቃት ልትወጣ ይገባታል። ከፖለቲካ አስተዳደር ውጭ የሆነ የራሷ አስተዳደር ሊኖራት ይገባል። ይህ ሊሆን የሚችለው ደግሞ፦

• ራሷ በክርስቶስ ሠላም ውስጥ መኖርዋን ስታረጋግጥ

• መልካም አስተዳደር በውስጧ ሲጎለብት

• የውስጥ ችግሮችዋን በራሷ መፍታት ስትችል፣መከባበር፣ መደማመጥ ሲኖር፣

• ቤተክርስቲያኒቱ ያለባትን ኃላፊነት በግልጽ በማጤን በውስጧ ተሰግስገው ሰማያዊ ሳይሆን ምድራዊ ዓላማ ይዘው የሚጓዙትን ጠርጎ ሲያስወጣ 

• ቤተክርስቲያንን የመጠበቅ ግዴታ የምእመኑም በመሆኑ በክርስትና እምነት አስተምሮ የታነጸ ሲሆንና ተሳትፎአቸውን ይበልጥ በማጎልበት የአሠራር ግልጽነትን በማስፈን ወዘተ ብቻ የሚሆን ነው።

ቤተክርስቲያን ችግሮቿን በራሷ አቅም መፍታት ስትችል መልካም አስተዳደር ይሰፍናል፤ መንፈሳዊነት ይጸናል።


"የእግዚአብሔር ጸጋ እንደ ተሰጠኝ መጠን እንደ ብልሃተኛ የአናጺ አለቃ መሠረትን መሠረትሁ፥ ሌላውም በላዩ ያንጻል። እያንዳንዱ ግን በእርሱ ላይ እንዴት እንዲያንጽ ይጠንቀቅ።" 1ኛ ቆሮንቶስ 3:10


እኛም እንደ ምእመን እንዴት በጥንቃቄ መኖር እንዳለብን እንመለከታለን።

ክፍል ሁለት ይቀጥላል


@deressereta


እኔን ለማግኘት ጽሁፎቼን ለመከታተል ከዚህ በታች የተጠቀሱት ሁሉ ወደ'ኔ ይመሩዎታል።


My Facebook page link (በፌስቡክ ገጽ እንገናኝ)


https://www.facebook.com/deresse2020/


Main facebook account (ዋናው የፌስ ቡክ ገጼ ይቀላቀሉት)


https://www.facebook.com/DeresseReta


Follow me through telegeram (በቴሌግራም ሊከታተሉኝ ከፈቀዱ) ሁሉም ምልከታዬን የማጋራባቸው ማህበራዊ ድረ ገጾች ናቸው።

ሰኞ 23 ኖቬምበር 2020

በአባቴ ቤት እንጀራ የሚተርፋቸው አገልጋዮች ስንት ናቸው?

 በአባቴ ቤት እንጀራ የሚተርፋቸው አገልጋዮች ስንት ናቸው?

ሉቃስ 15: 17

ጌታችን መድኋኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ምድር በተመላለሰበት በዘመነ ሥጋዌው ለሶስት ዓመት ከሶስት ወር አስተምሯል።

እርሱም በሚያስተምርበት ወቅት የአምስት ገበያ ያሕል ሕዝብ ይከተለው ነበር ብሎ መጽሐፍ ይነግረናል።

ከነዚህ የቃሉን ትምህርት ከሚማሩት ከእጁ በረከት ከሚሳተፉት መካከል ገሚሱ ሃጥያተኞች ስለነበሩ ሊከሱት ይከተሉት በነበሩት መካከል ተቀባይነትን አላገኘም ፤ እጅግም አስነቀፈው። እንዴት ሃጢያተኞችን ሰብስቦ ያስተምራል ብለው አሙት። ወንጀሉት።

ክብር ይግባውና ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የነርሱን ትችት ወደ ጎን በመተው ይልቅስ መድሃኒት የሚያስፈልገው ለጤነኞች ሳይሆን ለበሽተኞች እንደሆነ በመንገር ከክፋታቸው ይመለሱ ዘንድ አስተማራቸው። እኔ ሐጥአንን ልጠራ መጣሁ እንጂ ጻድቃንን ልጠራ አልመጣሁም እንዲል ከሃጢያተኞች ጋር ዋለ። እነርሱም አጉረመረሙ። በማጉረምረማቸው ምክንያት ሶስት ምክንያታዊ የሆነ ትምህርት በምሳሌ አስተማረ።

፩ኛ. አንድ ሰው መቶ በጎች ነበሩት ቀኑን ሙሉ በለመለመ መስክ እያሰማራ ከምንጭ ውሃ እያጠጣ ዋለ ሲመሽም ወደ በረታቸው ያጉራቸው ዘንድ ወደ ቤቱ ተመለሰ። ከመሸ ከደከመውም በኋላ አንደኛው በግ እንደጠፋበትም ተረዳ ዘጠና ዘጠኙን በበረት ቆልፎባቸው በጨለማ አንዱን በግ ፍለጋ ወጣ። ያንን በግ እሲኪያገኝ ድረስ በከባድ ድካም ውስጥ ሆኖ ፈለገው። አገኘውም። እጅግም ደስ አለው። ጎረቤቶቹንም ጠርቶ አንዱ በጌ ጠፍቶ ነበር ተገኝቷል ከኔ ጋርም ደስ ይበላችሁ አላቸው።

፪ኛ. አንዲት ሴት አሥር ሳንቲሞች (ድሪም) ነበሯት ከአሥሩ ሳንቲሞች አንዱ ጠፋባት መብራት አብርታ ፈለገችው፣ የቤቱንም ቆሻሻ ጠርጋ ወደ አንድ ጥግ ሰበሰበች ፈለገችው አገኘችውም እርሷም እንደ ባለ በጉ ጎረቤቶቿን ጠርታ አንድ ድሪም ጠፍቶብኝ ነበር አገኘሁት ከኔ ጋር ደስ ይበላችሁ አለቻቸው።

፫ኛ. አንድ ባለጸጋ ሰው ሁለት ወንድ ልጆች ነበሩት ይህ ሰው የሃብቱ ወራሾች እነዚህ ልጆች ብቻ ነበሩ፤ ይሁን እንጂ ሐብት የሚወረሰው አባትየው ሲሞት ነው። ትንሹ ልጅ ከአባቱ የሚደርሰውን ሐብት ንብረት ተመኘ አባቱንም ቢያይ ቢያይ አይሞትም እጅግም ቸኮለ። ስለዚህ ወደ አባቱ በመሄድ የሚደርሰውን አንድ ሶስተኛውን ይሰጠው ዘንድ ጠየቀ አባቱም ኩፍሎ ሰጠው። ሐብቱንም ይዞ ወደ አንድ እሩቅ አገር ሄደ። በልቶ ጠጥቶበት ከጋለሞታዎችም ጋር አባክኖት በአጭር ጊዜ ጨረሰው።

ገንዘቡ ሲያልቅ ጓደኞቹም ከአጠገቡ አንድ በአንድ እየሸሹት ብቻውን ቀረ። ሀብቱም አልቆ ባዶ እጁን ቀረ፣ ተራበ፣ ተጠማ፤ መጠለያም አጣ። ወቅቱም በአገሩ ድርቅ ተከስቶ ነበርና ረሐብ ሆነ። ያስጠጋው ዘንድ ወደ አንድ ሰው ዘንድ ሄደ። እርሱም አስጠጋው ሰውየው ላስጠጋበት ዋጋ ይሆነው ዘንድ አሳማዎቹን እንዲጠብቅለት አደረገው።

አሳማ እጅግ አስጠሊታ ከመሆኑ የተነሳ እስራኤላውያን አሳማ መጠበቅ አይወዱም። የነካው ይረክሳል፣ ሥጋውንም አይበሉትም። ይህ የባለጸጋ ሰው ወጣት ልጅ ውሎና አዳሩ እጅግ በሚገማ የአሳማ በረት ውስጥ ሆነ። ወቅቱ ድርቅ እና ረሐብ የነበረበት ወቅት ስለሆነ እጅግ ከመራቡ የተነሳ አሳማው ከሚበላው ይመገብ ዘንድ ይመኝ ነበር።
ርሐብና እና ጽም እጅግ ጸናበት። ችግርም ጸናበት።
በስተ መጨረሻ ወደ ልቡም ተመለሰ። እንዲህም አለ፦ በአባቴ ቤት እንጀራ የሚተርፋቸው አገልጋዮች ስንት ናቸው? ተነስቼ ወደ አባቴ ቤት እሄዳለሁ አባቴ ሆይ የሚገባኝን ሁሉ ወስጄ ሄጃለሁ ከእንግዲህ ልጅህ ልባል አይገባኝም ከአገልጋዮችህ እንደ አንዱ አድርገኝ እለዋለሁ። ብሎ ወደ አባቱ ዘንድ ሄደ። አባቱም በርቀት ተመለከተው እጅግም አዘነለት ወደ እርሱም ሮጦ አቀፈና ሳመው።
ልጁም አባቴ ሆይ ልጅህ ልባል አይገባኝም አለው።
አባትም ከሁሉ የሚበልጠውን ልብስ አምጡና አልብሱት፣ ለእግሩ ጫማ ስጡት፣ የሰባውን ፊሪዳ አምጡና እረዱለት እንብላ እንጠጣ ደስም ይበለን። ልጄ ሙቶ ነበር ሕያው ሆኗል፣ ጠፍቶ ነበር ተገኝቷል፤ አለ።
እቤት የነበረው፣ ከአባቱ ሐብት ንብረት ያልተካፈለው ትልቅ ልጅ እርሻ ዉሎ ወደ ቤት ሲመጣ ከቤታቸው ቅጽር ድምጽ ሰማ፣ ያልተለመደ ድምጽ ነው የዘፈን ድምጽ፣ የደስታ ድምጽ የምስራች የያዘ ድምጽ፣ እኛ ቤት ምን ተፈጠረ? ምንስ ክስተት ተከሰት? እኔ ከቤት ከወጣሁ እኔ የማላውቀው ነገር ምንስ ተፈጠረ ብሎ ጠየቀ፤ ከጎረቤትም ልጅ መጣና ወንድምህ ነው አለው።

ወንድሜ ምን ሆነ?
ወንድሜስ ከዚህ የት አለ? ብሎ ጠየቀ።

የጠፋው ወንድምህ ተገኝቷል፤ አባትህም ተደስቷል። ለወንድምህ መምጣት በቤታችሁ ትልቅ ደስታ ሆኗል። አባትህም ትልቁን ፊሪዳ ለወንድምህ አርዶለታል። አዲስ ልብስም አልብሶታል። ለጣቱም ቀለበት አጥልቆለታል ብሎ ወሬውን አደረሰው።

ወንድሙም እጅግ አዘነ፣ እኔ በዚህ ቤት ስኖር ሥጥር ሥግር አንዳች ቀን ትልቅ እና የሰባ ፊሪዳ አይደለም ግለግል እንኳን ታርዶልኝ አያውቅም፣ አዲስ ልብስ እና የጣት ቀለበት አልተገዛልኝም። ሐብት ንብረቱን ተካፍሎ ቤቱን ጥሎ የሄደን ልጅ ተመልሶ መቀበሉ ስለምን ነው በማለት አኮረፈ ወደ ቤትም አልገባም አለ።

አባቱም ስለ ትልቁ ልጅ ተጨነቀ ሊያግባባውም ሞከረ። ስለ ጠፋው ልጁ/ወንድሙ መገኘት ሊነግረው ሞከረ።

ትልቅ ልጅ፦ ልጅህ ሲመጣ የሰባውን ፍሪዳ አረድክለት፣ ለጣቱም ቀለበት አጠለክለት፣ አዲስ ልብስም እንዳለበስከው ሰማሁ ... እኔ እስከ ዛሬ እንደ ባሪያ ሳገለግልህ ነበር አንድም ቀን ለእኔ እና ጓደኞቼ አንዲት ጠቦት አላደረክም ገንዘቡን ከጋለሞታዎች ጋር ሲበትን ለኖረው ልጅህ እንዴት እንደዚህ ታደርግ ዘንድ ልብህ ፈቀደ አለው።

አባትም ልጄ አንተ እስከ ዛሬ ከኔ ጋር ነበርክ የእኔ የሆነው ሁሉ ያንተ ነበር፤ ነገር ግን ይህ ወንድምህ ( ትልቅ ልጅ ወንድሙን ስለ ተናደደበት አባቱን ልጅ አለው አባት ግን ወንድም በማለት አስታወሰው) ሞቶ ነበር ሕያው ስለሆነ ጠፍቶ ነበር ስለተገኘ ደስ ሊለን ሐሴትም ልናደርግ ይገባል አለው።

ከላይ በተጠቀሱት ምሳሌዎች የጠፉ ሶስት ነገሮችን ተመልክተናል።
1. በመጀመሪያ በግ ጠፋ
2. በመቀጠል ድሪም (ሳንቲም) ጠፋ
3. በስተ መጨረሻ ሰው ነው የጠፋው
እግዚአብሔር በሉቃስ ወንጌል ምእራፍ 15 በመጽሐፍ ቅዱስ የሚገኙትን ሁሉን ጠቅልሎ ሊይዝ በሚችል መልኩ ያስተማረበት የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ነው። እዚህ የተጠቀሱት ምሳሌዎች ሳይቀር በጣም ወርቃማ ምሳሌዎች ናቸው።

ይህ የትምህርት ክፍል ከመደነቁ ባሻገር በሕይወታችን ውስጥ የሚያሳየን ትልቅ ምሥጢር አለ። ይኸውም አንድ ክርስቲያን ከቤተክርስቲያን እንዴት አድርጎ እንደሚጠፋ፣ ሕይወቱ እንዴት እንደሚቅበዘበዝ፣ እግዚአብሔር እንዴት እንደሚፈልገን፣ እንዴትስ ወደ እግዚአብሔር ቤት እንደምንመለስ ቁልጭ አድርጎ ያሳየናል። (ጽሑፉ ረዘመ እኔ ረጅም ጽሑም አልወድም የምትል ከሆነ ከዚህ ምሥጢር አትሳተፍም)

በምሳሌው በመጀመሪያ የጠፋው እንስሳ ነው፣ በመቀጠል የጠፋው እቃ ሲሆን በመጨረሻም የጠፋው ሰው ነው።

• ሰወች ስንጠፋ ሰው ሆኖ የማይበድል እንጨት ሆኖ የማይጨስ የለም እያልን እንጠፋለን።
• አንዳንዴ ከሰውነት ክብር ዝቅ ብለን የእንስሳ ተግባር ስንከውን እንገኛለን። (አውሬያዊ ጭካኔ ይታይብናል።)
• አንዳንዴ ከእንስሳት ዝቅ ብለን እቃ የምንሆንበት አጋጣሚ አለ። እንስሳት በዘር አይጣሉም እኛ ግን ከነርሱ አንሰን በዘር እንጣላለን። አንበሳ ምን ቢከፋ ምን ቢርበው አንበሳን አይበላም እኛ ግን እርስ በርስ እንበላላለን። የማንጠቅም ርካሽ የምንሆንበት ጊዜ አለ።
እግዚአብሔር በነዚህ ምሳሌ እንደምንመለከተው ሊያስተምረን የፈለገው እንደ እንስሳም ብትጠፉ እፈልጋችኋለሁ፣ እንደ እቃም ብትጠፉ እፈልጋችኋለሁ፣ እንደ ሰውም ብትጠፉ እፈልጋችኋለሁ ሲል ነው። አንዳንዴ ከሰውነት ክብር ወርደን እንደ እንስሳ የምንሆንበት ጊዜ አለና። " ሰው ክቡር ሆና ሳለ እንስሳትን መሰለ" እንዲል። ከእንስሳም ዝቅ ብለን በእቃ ልክ ስንገኝ እንደሚፈልገን ያጠይቃል።

በጠፉት ሶስት ምሳሌዎች በመጀመሪው ላይ ፈላጊው እረኛ ነው፣ ሁለተኛ ላይ እናት ነው፣ በሶስተኛው ላይ አባት ነው።

የሁላችን አባትም እናትም የሆነ እግዚአብሔር አምላካችን ነው። "አባታችን ሆይ " በሉ ብሎ እንዳስተማረን። ሊቃውንቱም እግዚአብሔር እናት እና አባት ብቻ ሳይሆን አያታችንም ነው ይሉናል።

ለዚህም ምሳሌ ሲጠቅሱ እንዲህ ይላሉ፦

እግዚአብሔር ራሱን በብዙ ምሳሌ እንዲመስል (በዶሮ በወፍ እየመሰለ እንዲያስተምር) ዶሮ ጫጩቶቿን ከእቅፎቿ በታች እንድትሰበስብ እንዲሁ የአለሙ መድህን እግዚአብሔር እኛን ይሰበስበናል።

ዶሮ ለጫጩት እናትም አያትም እንደሆነች እርሱ እናታችንም አያታችንም ነው። ምድራዊ እናት እና አባት በዋልንበት አይዉሉም በአደርንበት አያድሩም። እግዚአብሔር ግን በዋልንበት የሚውል ባደርንበት የሚያድር መልካም አባታችን/እረኛችን ነው። " እግዚአብሔር እረኛዬ ነው የሚያሳጣኝ የለም በለመለመ መስክ ያሳድረኛል በእረፍት ዉሃ ዘንድ ይመራኛል" እንዲል

እረኛ በጎቹን ቀን ከጠበቀ ሌሊት ይተኛል፣ እግዚአብሔር ግን እኛን ሲጠብቅ አይተኛም። "ሕዝቤን የሚጠብቅ አያንቀላፋም" ይላልና።

እረኛ በጉን ጠብቆ ካሳደገ በኋላ አርዶ ይበላዋል አልያም አርደው ለሚበሉት አሳልፎ ይሸጠዋል። እረኛችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ስለ መልካም እረኝነቱ በሰላሳ ብር ስለ በደላችን ተሸጠ። ተላልፎ ተሰጠ። ኢየሱስ ክርስቶስ በጎቹ የሸጡት እረኛ ነው።

እረኛው በጎቹን አርዶ ሲበላ የእኛን እረኛ ግን እኛ ተሰልፈን በቤተክርስቲያን ምሥጢር አርደን እንበላዋለን። የእረኛ ፍቅር እስከ ማረድ ነው። የእኛ እረኛ ግን ነፍሱን ስለ በጎቹ አሳልፎ እስከ መስጠት ነው።

ነገር በምሳሌ እንዲሉ ምሳሌው እንዲህ ነው፥

እረኛው እግዚአብሔር ነው
መቶ በጎች የተባሉት ሰውና መላእክት ናቸው።
አንድ በግ ጠፋ የተባለው ሰው ነው ዘጠና ዘጠኙ ነገደ መላእክት ናቸው።

ይሕ ምሳሌ የማዳኑን ሥራ ነው የሚያሳየን።

እኛ ሰዎች እንዴት ከቤተክርስቲያን እንጠፋለን ካልን፥

1ኛ. እንደ በግ ነው፦ በግ የሚጠፋው አውቆ አይደለም። የሚበላው ሣር የሚጠጣው ውሃ ፈልጎ የፊት የፊቱን ብቻ እያየ ሳያስበው ነው። እኛም ከቤተክርስቲያን ርቀን የሄድነው፣ ጠፍተን የሰነበትነው እንዲሁ እንደ በጉ ነው ሳናውቅ እንደምንጠፋ ሳናውቅ/ የጸናን ስለሚመስለን/የቆምን ስለሚመስለን ነው።

በጉ ስለሚበላ ስለሚጠጣ ሲል እንደ ጠፋው እኛም በእንጀራ ጉዳይ ከቤተክርስቲያን የጠፋን አለን። (ቢዚ ነኝ፣ ሥራ ይበዛብኛል፣ አይመቸኝም፣ እቤት ስገባ ይመሻል፣ ጠዋት ከቤት የምወጣው በሌሊት ነው፣ ቅዳሜና እሁድ ይደክመኛል፣ ማህበራዊ ጉዳይ አለብኝ፣ ቤተሰብ አስተዳዳሪ ነኝ፣ ልጅ አሳድጋለሁ ወዘተ እያልን በሰበብ ጠፍተናል። ከአንዱ ሥራ ሌላ ሥራ፣ ከአንዱ ትምህርት ሌላ ትምህርት እያልን ላንመለስ ሄደናል።)

የዚህ በግ ሳር መብላት ውሃ መጠጣት ክፋት የለውም ዋናው ችግር ከበረቱ መራቁ እንጂ። የኛም ችግር ሥራ መሥራታችን፣ ትምህርት መማራችን፣ ቢዚ መሆናችን አይደለም። ከቤተክርስቲያን መራቃችን እንጂ። በጉ ከበረት እየራቀ ሲሄድ ተኩላ ይበላዋል ወይም ሌባ ይሰርቀዋል የእኛም ከቤተክርስቲያን ያርቀናል ወይም በመናፍቃን ያስነጥቀናል/ያስክደናል፤ አልያም በዲያቢሎስ እንጠቀጥቃለን።

በጉ ሲጠፋበት እስኪያገኘው ድረስ ፈለገው፤ ሲያገኘውም እጅግ ደስ አለው አንስቶም በትከሻው ተሸከመው ይላል እግዚአብሔር አንድ አዳም ቢበድል ቢጠፋ እስኪያገኘው ድረስ እጅግ አሰልቺ በሆነ ትእግስት በሚጨርስ ፍለጋ ውስጥ አገኘው። ከቤቱ የጠፋን እኛንም እግዚአብሔር እስኪደክመው ሳይሆን እስኪያገኘን ድረስ ይፈልገናል። ለዚህም ነው በቃሉ ብርሃንነት ሊፈልገን በአደባባዩ አልገኝ ስንለው በማህበራዊ ሚድያ ሳይቀር ቃሉ እንዲነገረን ያደረገው። ለዚህኮ ነው ወደ እርሱ መሄድ ሲገባን ወደኛ የመጣው። እምቢ አሻፈረኝ ስንለው በመሰልቸት ሳይተው ወደ በረቱ እስክንመለስ ድረስ እየፈለገን ያለው።

አስቀድመን እንዳየነው የጠፋው በግ ሲገኝ በቤቱ ደስታ ሆነ በትከሻውም ተሸክሞ ወደ ቤቱ ወሰደው ሳያውቅ ነውና የጠፋውና። እኛንም የአለም መድሃኒት ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቤቱ ስንመለስ በዘጠና ዘጠኙ ነገደ መላእክት ዘንድ ደስታ ይሆናል ሳናውቅ ነውና የጠፋነው።

አውቆ ከመጥፋት ይሰውረን።

አሁን በዚህ ሰአት ይህን ቃል እንድናነብ ያደረገን፣ በቤቱ የሰበሰበን፣ በቤቱ እንድንኖር ያደረገን እኛ ፈቅደን መጥተን አይደለም እርሱ በፍቅር በትከሻው ተሸክሞን አምጥቶን እንጂ። ይኸን ጊዜ ከጽሁፍ ርዝመት ያልጨረሱት አሉ። አንተ እየጨረስክ ያለኸው በፍቅር በደስታ በትከሻው ተሸክሞህ ስለመጣ ነው እንጂ አንተ ከቃሉ ፍቅር ስላለህ አንተ ስለምትሻል አይደለም። እኛማ አለም እንዴት ሰነበተች?፣ የፖለቲካው ጡዘት የት ደረሰ?፣ ዋንጫውን ማን በላ?፣ ወዘተ የሚለው ሚድያ ላይ ነበርን። አሁን እዚህ የተገኘነው መርጠን አይደለም ተመርጠን እንጂ። ፈቅደን አይደለም ተፈቅዶልን እንጂ።
እኔኮ እፈልጋለሁ ለመምጣት ግን አይመራኝም እንላለን ዛሬ መርቶ ያመጣን እግዚአብሔር ነው የኛ ብርታት አይደለም። " በምህረትህ ብዛት ወደ ቤትህ እገባለሁ" እንዲል። እየፈለጉ ያልመጡትን እግዚአብሔር ያምጣልን። የመጣነውን በቤቱ ያለነውን አያርቀን።ያጽናን።

ክፍል ሁሉት ይቆየን።

ጦማሩን ስለጎበኙ አመሰግናለሁ!

መልካም ነገርን ለሌሎች ማጋራት ባህላችን እናድርግ፤ ላልደረሰዉ በማጋራት ድርሻችንን እንወጣ፡፡

የቀኝ ዐይን - ድንግል ማርያም

  የቀኝ ዐይን - ድንግል ማርያም   ( በዲ / ን ብርሃኑ አድማስ ) አፍጣኒተ ረድኤት ማርያም በጊዜ   ምንዳቤ ወአጸባ ለዐይን እምቀራንባ፤ አንቲ ውእቱ ረዳኢተ ያዕቆብ በቤተ ላባ፤ በኩ...